በኢየሱስና የሃይማኖት መሪዎች መካከል የተካሄደ ክርክር (ማር. 11፡27-12፡40)

ማርቆስ፥ «ክርስቶስ በአይሁድ የሃይማኖት መሪዎች ለምን ተገደለ?» የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ የክርስቶስን ሕይወት የመጨረሻ ቀናትና ክርስቶስ ከሃይማኖት መሪዎች ጋር ያካሄዳቸውን ክርክሮች ገልጾአል። ልማዳቸውንና ሰንበትን ባለመጠበቁ ምክንያት፥ የተጠነሰሰው ጥላቻ እያደገ ሄዶ ወደ መስቀል ሞት አድርሶታል።

ሀ. በካህናት አለቆችና በሸንጎው አባላት የቀረበ ጥያቄ (ማር. 11፡27-12፡12)። የአይሁድ አለቆች ክርስቶስ በድል አድራጊነት ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱና ከቤተ መቅደስ ውስጥ ነጋዴዎችን ማባረሩ መሢሕነቱን እንደሚያመለክት ተገንዝበው ነበር። ነገር ግን ክርስቶስ ይህንን ለማድረግ ሥልጣን ከየት እንዳገኘ ገርሟቸዋል። እነርሱ ሥልጣናቸውን ከየት እንዳገኙ በሚገባ ያውቁ ነበር። ሥልጣናቸው የመጣው ከአሮን የዘር ሐረግ በመሆናቸው ወይም በእውቅ የሃይማኖት ሰውና የተማሩ በመሆናቸው ነበር። ክርስቶስ ግን ሥልጣኑ ከሰማይ እንደ መጣ የሚያስረዱ ተአምራትና ትምህርቶችን አቅርቧል። እግዚአብሔር አብ የነገረውን ብቻ እንደሚያደርግም ገልጾላቸዋል (ዮሐ 56)። ነገር ግን የማወቅ ፍላጎት ስላልነበራቸው፥ ክርስቶስ ጥያቄያቸውን ለመመለስ አልፈለገም። በዚህ ፈንታ፥ የመጥምቁ ዮሐንስ የነቢይነት ሥልጣን ከየት እንደ መጣ ጠየቃቸው። ይህንን ጥያቄ ከመለሱለት፥ እርሱም ጥያቄያቸውን ለመመለስ ተስማማ። ዮሐንስና ክርስቶስ ሥልጣናቸውን ያገኙት ከእግዚአብሔር ነበር። የሃይማኖት መሪዎቹ የክርስቶስን ጥያቄ ለመመለስ ባለመፈለጋቸው፥ እርሱም ጥያቄያቸውን ሳይመልስ ቀረ፡

ክርስቶስ የመሬት ባለቤቱንና የጪሰኞችን ታሪክ በመጠቀም፥ የሃይማኖት መሪዎችን ልብ ከፈተ። ክርስቶስ የሃይማኖት መሪዎች ምን ሊያደርጉበት እንደ ፈለጉና ፍጻሜውም ምን እንደሚሆን ለሕዝቡ ነገራቸው። እግዚአብሔር የአይሁድን ሕዝብ (ኢሳ 5- እስራኤል የእግዚአብሔር ወይን መሆናቸው ተገልጾአል) ለሃይማኖት መሪዎች አደራ ሰጥቷል። መሪዎቹ ቀን ሕዝቡን የእግዚአብሔር ሳይሆኑ የራሳቸው ንብረት በማድረግ እግዚአብሔርን አታለሉ። የእግዚአብሔር መልእክተኞች የነበሩትን ነቢያት የገደሉ ሲሆን፥ አሁን ልጁን ሊገድሉ ነበር። ከዚያስ? በመጀመሪያ፡ እግዚአብሔር በሕዝቡ ላይ የመሪነት ሥልጣን የነበራቸውን ሰዎች ይገድላል። ይህም ሮማውያን ኢየሩሳሌምን ወርረው አብዛኞቹን የሸንጎ አባላት በመግደላቸው ተፈጻሚነትን አግኝቷል። ሁለተኛ፥ ክርስቶስ ሌሎች መሪዎችን ያስነሣል። እነርሱም የእግዚአብሔርን ሕዝብ በፍትሕ የሚመሩ ሐዋርያት ነበሩ። ሦስተኛ፥ ሊቀበሉ ያልፈለጉትና የገደሉት ክርስቶስ፥ የአዲሱ የእግዚአብሔር ሕዝብ መሠረት ይሆናል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እንደ ሰዱቃውያን ሊያስቡና ሊሠሩ የሚችሉት እንዴት ነው? ለ) ይህ ክፍል የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ለእግዚአብሔር ሕዝብ ለሥልጣናቸውና ለሥራቸው ሊኖራቸው ስለሚገባው አመለካከት ምን ማስጠንቀቂያዎችን ይሰጣል?  

ከፈሪሳውያንና ከሄሮድስ የፖለቲካ ቡድን አካላት የቀረበ ጥያቄ (ማር. 12፡13-17)። ማርቆስ፥ ክርስቶስ በሮም መንግሥት ላይ የተነሣ አማፂ አለመሆኑን ለአንባቢዎቹ ያሳያል። ከአብዛኞቹ አይሁዶች በተቃራኒ፥ ክርስቶስ ሕዝቡ ታክስ ባለመክፈል የሮምን መንግሥት ከመደገፍ እንዲታቀብ እያስተማረ አልነበረም። በተጨማሪም፥ ማርቆስ ክርስቲያን ለሁለት መንግሥታት ታማኝነቱን መስጠት እንዳለበት ያብራራል። በመጀመሪያ፥ ምድራዊ የፖለቲካ መንግሥት ነበር። ክርስቶስ ሰዎች በጉልበታቸው ተጠቅመው አብዮትን እንዲያካሂዱ አልሰበከም። ነገር ግን ቀረጣቸውን ለሮም እንዲከፍሉ ነግሯቸዋል። ሁለተኛ፥ እግዚአብሔር የነገሠበት ምድራዊ መንግሥት አለ። ይህንንም መታዘዝ ያሻል። ሁለቱ መንግሥታት በሚጋጭበት ጊዜ፥ ክርስቲያኖች ምድራዊውን ሳይሆን ሰማያዊውን ንጉሥ መታተዝ ይኖርባቸዋል። የክርስቶስ ተከታዮች የሆንን ሁሉ እርሱ የሕይወታችን ንጉሥ እንደሆነ ማስታወስ አለብን። ከዚህ የተነሣ አምልኳችንን፥ ጊዜያችንንና ቁሳዊ ሀብቶቻችንን ጨምሮ፥ በሕይወታችን ሁሉ ላይ መብት እንዳለው መገንዘብ አለብን። ያለን ነገር ሁሉ የእግዚአብሔር ነው።

ከሰዱቃውያን የቀረበ ጥያቄ (ማር. 12፡18-27)። ሰዱቃውያን ጥቅም የሌለው ሥነ መለኮታዊ ክርክር ለመቆስቆስ በመፈለጋቸው፥ ሰባት ባሎችን ስላገባች ሴት ክርስቶስን ጠየቁት። እነዚህ ሰዱቃውያን በትንሣኤ የማያምኑ በመሆናቸው፥ ይህን ያሉት ክርክር ለመቀስቀስ ያህል ብቻ ነበር። ክርስቶስ ሰዱቃውያን ትንሣኤን በመካዳቸው ምን ያህል ከፍተኛ ሥነ መለኮታዊ ስሕተትን እንደ ፈጸሙ አስረድቷቸዋል። እግዚአብሔር የሕያዋን አምላክ ነው በእርሱ የሚያምኑ ሰዎች እንደ አብርሃም፡ ይስሐቅና ያዕቆብ በሥጋ ሊሞቱ ቢችሉም፥ በመንፈስ ግን ሕያዋን ናቸው። ለዚህም ነው እግዚአብሔር የአብርሃም፥ የይስሐቅና የያዕቆብ አምላክ ተብሎ የተጠራው። ስለዚህ፥ ሞትን መፍራት የለብንም። ሞት የህልውናችን ፍጻሜ አይደለም። ሞት መንፈሳችን ሕያው የሚሆንበትን ሌላ ዓይነት ህላዌ ይጀምራል።

መ. ከሃይማኖት ሊቅ የቀረበ ጥያቄ (ማር. 12፡28–34)። ከሕግ የሃይማኖት ሊቃውንት አንዱ የክርስቶስን ጥበብ በተመለከተ ጊዜ፥ ከትእዛዛት መካከል የትኛው እንደሚልቅ ጠየቀው። አይሁዶች በብሉይ ኪዳን ውስጥ 618 መሠረታዊ ሕግጋት እንዳሉ ያምኑ ነበር፡፡ ከእነዚህ ሕግጋት መካከል የትኞቹ «ከባድ» የትኛው ደግሞ «ቀላል» እንደሆነ ለማወቅ ይጥሩ ነበር። ስለዚህ ይህ ሰው ክርስቶስ ከሁሉም በላይ ከባዱ ሕግ የትኛው እንደሆነ እንዲነግረው መጠየቁ ነበር። ክርስቶስ እያንዳንዱ ሃይማኖት አጥባቂ አይሁዳዊ በየጠዋቱና በየማታዊ የሚደግመውን ዘዳግም 6፡4-5 በመጥቀስ መልስ ሰጠው። በዚህ ክፍል፥ ከሕጉ በስተ ጀርባ በእግዚአብሔር ማንነት ላይ ትክክለኛ እምነት አለ። ስለ እግዚአብሔር ያለን አመለካከት የተሳሳተ ከሆነ፥ አንድን ሕግ ለመጠበቅ መሞከሩ ዋጋ የለውም። በመጀመሪያ፥ ቅዱሳት መጻሕፍትን በመጥቀስ ክርስቶስ የሕግጋት ሁሉ መሠረቱ ለእግዚአብሔር ያለን ፍቅር እንደሆነ ተናግሯል። እግዚአብሔርን በሁለንተናችን ብንወደው በልባችን፥ በነፍሳችንና በጉልበታችንን እግዚአብሔርን የሚያስቀይም ተግባር ልንፈጽም አንችልም። ሁለተኛ፥ ከዘሌዋውያን 19፡18 በመጥቀስ ክርስቶስ እግዚአብሔርን ከመወደድ ጋር ሰውን መውደድም ግንኙነት ያለው መሆኑን ገልጾአል። እግዚአብሔር ከእርሱና ከሌሎች ሰዎች ጋር ስላለን ግንኙነት አጥብቆ ስለሚያስብ፥ የመጀመሪያውና ሁለተኛው ትእዛዝ ሊነጣጠሉ አይችሉም።

የውይይት ጥያቄ ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔርን ከመውደድ ሥር የተጠቀሱትን ሕግጋት ዘርዝር። ለ) ሌሎችን እንደ ራሳችን ከመውደድ ሥር የተጠቃለሉትን ሕግጋት ዘርዝር፡ ሐ) እነዚህ ሕግጋት ከአምልኳችን (ከሚቃጠል መሥዋዕት) በላይ አስፈላጊዎች ከሆኑ፥ ዕለተ እሑድ ወደ አምልኮ ስፍራ ከመሄዳችን በፊት ምን ልናደርግ ይገባል?

የሃይማኖት መሪዎች እነዚህ ሁለት ትእዛዛት ከእግዚአብሔር ጋር የሚደረግ ግንኙነት መሠረት መሆናቸውን ወዲያውኑ ተገነዘቡ። እነዚህ ትእዛዛት እንደ መሥዋዕት፥ መዝሙር፥ ስብከት ወይም የገንዘብ ስጦታ ከመሳሰሉት ውጫዊ የአምልኮ ተግባራት በላይ አስፈላጊዎች ነበሩ። ብዙ ክርስቲያኖች እሑድ ዕለት ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው ሊዘምሩ፥ የመዘምራንን ዜማ ሊሰሙና ስብከት ሊከታተሉ ይወዳሉ። በአዘቦት ቀናት ግን እግዚአብሔርን ከማስከበርና ለእርሱ ያላቸውን ፍቅር ከማንጸባረቅ ይታቀባሉ። ብዙውን ጊዜ ከቤተሰቦቻቸውና ከሌሎችም ጋር ጤናማ ግንኙነት የላቸውም። ክርስቶስ አምልኮ ከእግዚአብሔርና ከሌሎች ሰዎች ጋር ካለን ጤናም ግንኙነት እንደሚጀምር አስተምሯል። እያንዳንዱ የሕይወታችን አካል የእግዚአብሔርን ፈቃድ እስካልተከተለ፥ በፍቅር እስካልተሞላና ከሌሎች ሰዎች ጋር ያለን ግንኙነት ሁሉ ከፍቅር ቁጥጥር ሥር እስካልዋለ ድረስ፥ የትኛውም የአምልኳችን ተግባር እግዚአብሔርን ሊያስደስት አይችልም።

ሠ. ኢየሱስ ለሃይማኖት መሪዎች ያቀረበው ጥያቄ (ማር. 12፡35-40)። የሃይማኖት መሪዎች ሊያጠምዱት ሲሞክሩ ከቆዩ በኋላ፥ ክርስቶስ የሚጠይቅበት ጊዜ ደረሰ። ክርስቶስ ምናልባትም ቀደም ሲል ያላስተዋሉትን ሥነ መለኮታዊ እውነት እንዲገነዘቡ ነበር የፈለገው። በጥያቄውም መሢሑ የዳዊት ልጅ ቢሆንም፥ አምላክ መሆኑን ዳዊት በመዝሙሩ ውስጥ ጌታ እንዳለው በመጥቀስ ገለጸላቸው [መዝ. (119)፡)]።

ክርስቶስ ሕዝቡ የሃይማኖት መሪዎችን ዓይነት አመለካከት እንዳይይዙ አስጠንቅቋል። በራስ እውቀት፥ ሃይማኖትና ክርስቶስን ለማመን ባለመፈለግ መኩራራት አደገኛ ነገር ነው፡፡ የሃይማኖት መሪዎች የሰዎችን ሙገሳ ይፈልጉ ነበር። ለእነርሱ ሃይማኖት በሌሎች ዘንድ የመታወቂያ መሣሪያ ነበር። ሰዎች ወዲያውኑ እንዲለዩዋቸውና እንዲያከብሯቸው በማሰብ ለየት ያሉ ልብሶችን ይለብሳሉ። በሚያመልኩበት ጊዜ በቤተ መቅደሱ ውስጥ የፊተኛውን ስፍራ ይይዛሉ። እነዚህ መሪዎች በሰዎች ፊት ለመታየት ረዣዥም ጸሎቶችን ቢጸልዩም፥ ሌሎችን ሰዎች በተለይም ተስፋ የሌላቸውን መበለቶችና እንደ እነርሱ ዓይነቶችን ከመበደል አልተመለሱም።

የውይይት ጥያቄ ጥያቄ፡- ሀ) እኛም በአለባበሳችን፥ በአቀማመጣችን፥ በአዘማመራችን በአሰባስካችን ወይም በማስተማር ስልታችን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተለይተን ለመታወቅ የምንጥርባቸው አንዳንድ መንገዶች ምንድን ናቸው? ለ) ክርስቶስ ዛሬ በመካከላችን ቢኖር፥ ስለ አመለካከቶቻችንና ኩራታችን የሚሰጠን ማስጠንቀቂያ ምን ይሆን ነበር?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “በኢየሱስና የሃይማኖት መሪዎች መካከል የተካሄደ ክርክር (ማር. 11፡27-12፡40)”

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading