Site icon

ወንጌሉ የአማኞችን አኗኗር ይለውጣል (ሮሜ 12፡1-21)

ጥሩነሽ በቅርቡ በክርስቶስ አምናለች። መንፈስ ቅዱስ ኃጢአተኛ እንደሆነችና ይቅርታ ልታገኝ የምትችልበት ብቸኛው መንገድ ለኃጢአት በሞተው በክርስቶስ በማመን መሆኑን ለልቧ መስክሮላታል። ጥሩነሽም በኃጢአተኝነት ስሜት ተሞልታና እግዚአብሔር ለእርሷ ስላለው ፍቅር ተደንቃ ክርስቶስ ለኃጢአቷ የሞተ አዳኝዋና ጌታዋ እንደሆነ አመነች። በዚህ ጊዜ ሰላም ልቧን ሞላው። የእግዚአብሔር ልጅ ሆነች።

ነገር ግን ከዚህ በኋላ ማድረግ ያለባት ነገር ምንድን ነው? አሁን ልጁ ከሆነች በኋላ እግዚአብሔር ምን እንድታደርግ ይፈልጋል? ሕይወቷ እንዴት ሊለወጥ ይገባል? ክርስቲያኖችን ስትጠይቅ ሁሉም ከመጠጥ፥ ከሲጋራ፥ ከጫት፥ ከዘፈን ወደ ፊልም ቤት ከመሄድ፥ ወዘተ… መታቀብ እንዳለባት ይነግሯታል። ሌሎች ክርስቲያኖች ደግሞ ዋናው መዳኗ እንደሆነ በመግለጽ ደስ ያላትን ሁሉ ልታደርግ እንደምትችል ይነግሯታል። በእነዚህ የአሳብ ግጭቶች ግራ የተጋባችው ጥሩነሽ ብዙም ሳይቆይ ለእግዚአብሔር የነበራትን ፍቅር አጣች።

የወንጌሉ ተግባራዊ አካል የሆነውን ጉዳይ ብዙውን ጊዜ አናነሣውም። ይህም አዳዲስ ክርስቲያኖች እንደ እግዚአሔር ልጆች እንዴት መመላለስ እንዳለባቸው አለማብራራታችን ነው። ክርስቶስ እርሱን ለመከተል ከመወሰናችን በፊት የደቀ መዝሙርነትን ዋጋ መተመን እንዳለብን ተናግሯል (ሉቃስ 14፡25-33)። ነገር ግን እኛ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት በክርስቶስ ለማመን የሚፈልጉ ሰዎች ካመኑ በኋላ ምን እንደሚጠበቅባቸው አናብራራላቸውም። ምናልባትም ብዙዎቹ አማኞቻችን ፈጥነው ወደ ዓለም ከሚመለሱባቸው ምክንያቶች አንዱ ይሄ ሳይሆን አይቀርም።

ጳውሎስ የሮም ክርስቲያኖች ከእግዚአብሔር ቁጣ ለመዳን ወይም መንግሥተ ሰማይ በሚደርሱበት ጊዜ የኋላ ኋላ ድነትን (ደኅንነትን) እንደሚጎናጸፉ የተስፋ ቃል ለማግኘት ብቻ ሳይሆን፥ የዳኑት እግዚአብሔርን ለማገልገል እንደሆነ ገልጾአል። ሮሜ 12-16 በሮሜ ውስጥ ያለውን ሁለተኛ አጠቃላይ ክፍል ይይዛል፡፡ ሮሜ 1-11 የድነት ምንነት ያብራራል። ከሮሜ 12-16 ጳውሎስ ድነት የአንድን ሰው አጠቃላይ ሕይወት እንዴት እንደሚለውጥና ተግባራዊ ለውጦችንም እንደሚያስከትል ያብራራል። ክርስቶስን የሕይወታችን ሁሉ ጌታ ማድረግ ማለት ምን ማለት ነው?

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አማኝ ከሆንህበት ጊዜ ጀምሮ ሕይወትህ የተለወጠው እንዴት ነው? ለ) ሮሜ 12-13 እንብብ። ክርስቶስ የሕይወታችን ጌታ በሚሆንበት ጊዜ የሚለወጡትን ዐበይት የሕይወታችንን ክፍሎች ዘርዝር። ሐ) ሮሜ 12፡1-2ን በቃልህ አጥና። የእግዚአብሔር ልጆች ከሆንን በኋላ የሕይወታችን ዓላማ ምን እንደሚሆን እብራራ።

  1. አማኞች ሙሉ ሕይወታቸውን እንደ መሥዋዕት ለእግዚአብሔር ያቀርባሉ (ሮሜ 12፡1-2)

ጳውሎስ ይህን የሮሜ መልእክት ሁለተኛ ክፍል የሚጀምረው «እንግዲህ» በማለት ነው። «እንግዲህ» የሚለው ቃል ቀደም ሲል በተነገረው አሳብ ላይ ተመሥርቶ ድምዳሜ የሚሰጥ ስለሆነ፥ ይህን ቃል በምንመለከትበት ጊዜ ሁሉ ምንን እንደሚያመለክት ለመረዳት መሞከር አለብን። በዚህ ስፍራ ጳውሎስ ከሮሜ 1-11 ያቀረበውን ትምህርት ለማመልከት የሚፈልግ ይመስላል። እግዚአብሔር በምሕረቱ ልጁ ለኃጢአታችን እንዲሞት በማድረግ፥ ከኃጢአት ኃይል ነፃ በማውጣት፥ የኋላ ኋላ ደኅንነታችንን በማረጋገጥ፥ እንዲሁም ምንም ነገር ከእርሱ ፍቅር ሊለየን እንደማይችል የተስፋ ቃል በመስጠት በሚያስደንቅ መንገድ ስላዳነን፥ ከእግዚአብሔርና ከሰዎች ጋር የሚኖረን ግንኙነት መለወጥ አለበት። አኗኗራችንም መለወጥ አለበት። ጳውሎስ በዚህ ክፍል ክርስቲያኖች ሊያደርጓቸው ስለሚገቧቸው ወይም ስለማይገቧቸው ነገሮች ብዙ መመሪያ አለመስጠቱ አስገራሚ ነው። ጳውሎስ ስለ መጠጥ፥ ዕጽ፥ ወዘተ… አይጠቅስም። ለእግዚአብሔር ስለሚኖሩን አመለካከቶችና በክርስቲያኖች መካከል የሚታዩትን ግንኙነቶች በመሳሰሉት ጥልቅ ጉዳዮች ላይ ነበር ትኩረት የሰጠው። ሕይወታችን የሚለወጠው እንዴት ነው? ጳውሎስ ልናደርጋቸው የሚገቡንን አያሌ ነገሮች ይጠቃቅሳል።

ሀ. ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ሕያው፥ ቅዱስም መሥዋዕት አድርጋችሁ ለእግዚአብሔር አቅርቡ። እግዚአብሔር ልጁን እንደ መሥዋዕት ለእኛ ሰጥቶናል። እኛ ደግሞ ራሳችንን ለእግዚአብሔር መልስን እንሰጠዋለን። በብሉይ ኪዳን የሚቃጠል መሥዋዕትንና የኃጢአት መሥዋዕትን የመሳሰሉ ብዙ የመሥዋዕት ዓይነቶች ነበሩ። ጳውሎስ ለእግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ የመሰጠትን አሳብ ለማመልከት እንስሳው ሙሉ በሙሉ ስለሚቃጠልበት የሚቃጠል መሥዋዕት ነበር የሚናገረው። ጳውሎስ ሁለንተናችንን ለእግዚአብሔር መልሰን መስጠት እንዳለብን ያስረዳል። ነገር ግን ለእግዚአብሔር የምናቀርበው መሥዋዕት ከኃጢአት የተለየ ቅዱስ መሆን አለበት። እግዚአብሔርን የምናስደስተው በዚህ መልኩ ነው። ለእግዚአብሔር የምናቀርበውን የመጨረሻ አምልኮ የምንገልጸው እንደዚህ ነው። ብዙውን ጊዜ ስለ አምልኮ ስናስብ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለምንዘምራቸው መዝሙሮች፥ የቃለ እግዚአብሔር ስብከት፥ ወዘተ እናስባለን። ስሜታችንን በብዛት ካንጸባረቅን ፍሬያማ አምልኮ ያካሄድን ይመስለናል። ጳውሎስ ግን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ አምልኮ የሚጀምረው ራሳችንን ሙሉ በሙሉ ለእርሱ በመስጠት እንደሆነ ያስተምራል። ለእግዚአብሔር ክብር የተቀደሰ ሕይወት መኖር አለብን።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔርን በትክክል አምልኬአለሁ ብለህ ያሰብከው መቼ ነው? የዚያን ጊዜ አምልኮ ለአንተ ልዩ የሆነው በምን ምክንያት ነው? ለ) ለእግዚአብሔር የተሰጠና የተቀደሰ ሕይወት መምራት ለእውነተኛ አምልኮ ምን ያህል አስፈላጊ ነው? ሐ) ብዙ ክርስቲያኖች ወደ ቤተ ክርስቲያን ከመምጣታቸው በፊት ስለዚህ በአምልኮ ውስጥ የመጀመሪያው እርምጃ ስለሆነው ጉዳይ የማያስቡት ለምንድን ነው? መ) ብዙ ክርስቲያኖች በዕለተ ሰንበት ሕይወታቸውን ለእግዚአብሔር አሳልፈው ሳይሰጡ ለማምለክ የሚፈልጉ ይመስልሃል? መልስህን አብራራ።

ለ. በልባችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ። ጳውሎስ እነዚህ ክርስቲያኖች ማንን መምሰል እንዳለባቸው ጥብቅ ውሳኔ እንዲያደርጉ ያዝዛቸዋል። በአንዱ በኩል ዓለም አለች። ዓለም ደግሞ የገንዘብን ዋስትና፥ ክብርን፥ ተወዳጅነትን፥ ለግል ጥቅም የሚውልን ትምህርት፥ ወዘተ… ትፈልጋለች። በሌላ በኩል፥ በሙሉ ልባቸው እግዚአብሔርን ለማስደሰት የሚፈልጉ ሰዎች አሉ። ይህ መንገድ ደግሞ ራስን የማዋረድ፥ እግዚአብሔርን የመታዘዝ፥ ሌሎችን የመውደድ፥ የመመስከር፥ ወዘተ… አቅጣጫ ነው። ጳውሎስ በየቀኑ አስተሳሰባችንን የተቆጣጠረው የዓለም መንገድ እንዲገዛን ከመፍቀዱ ይልቅ የእግዚአብሔርን መንገድ ልንመርጥ እንደሚገባ ገልጾአል። ሐዋርያው ዮሐንስም የዓለም አሳብ እንዲገዛን መፍቀድ እንደሌለብን አስተምሯል (1ኛ ዮሐ 2፡15-17)።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ከዓለም የሚመጡትንና ክርስቲያኖች ሊለውጧቸው የሚገባቸውን ነገሮች፥ በተለይም ዓለማዊ አመለካከቶች ዘርዝር። ለ) ቤተ ክርስቲያንህ አዳዲስ አማኞች እነዚህን አመለካከቶች እንዲቀይሩ የምታስተምረው እንዴት ነው?

ነገር ግን እነዚህን ከዓለም የወረስናቸውን አመለካከቶች ልንለውጥ የምንችለው እንዴት ነው? ጳውሎስ ለውጡ የሚመጣው በጸሎት ወይም ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ብቻ እንዳልሆነ አመልክቷል። እነዚህ ነገሮች አስፈላጊዎች ቢሆኑም በዋናነት ለውጥ የሚመጣው አእምሯችንን በማደስ ነው። በአሳባችን ውስጥ ያለው ጉዳይ አስፈላጊ ነው ብለን ያሰብነው ነው። በሕይወታችን ተግባራዊ የምናደርገውም ይህንኑ የምናስበውን ጉዳይ ነው። ስለሆነም፥ አስተሳሰባችንን ብንለውጥና ከመጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ ጋር ብናዛምድ፥ ተግባራችንም እንደሚለወጥ ጳውሎስ አብራርቷል።

ራሳችንን ለእግዚአብሔር ክብርና አገልግሎት ሙሉ በሙሉ ስንሰጥና ወደ ተግባር የሚመራን አስተሳሰባችንን ስንለውጥ፥ ይህ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ወደ ማወቅ እንደሚመራን ጳውሎስ ገልጾአል። ብዙ ጊዜ ክርስቲያኖች፥ በተለይም ወጣቶች ለሕይወታቸው የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደሆነ ያስባሉ። ማንን ሊያገቡ፥ ምን ዓይነት ትምህርት ሊማሩ፥ ምን ዓይነት ሥራ ሊይዙ፥ የት አካባቢ ሊኖሩ፥ ወዘተ. እንደሚገባቸው ያብሰለስላሉ። እነዚህ ጠቃሚ ጥያቄዎች ቢሆኑም፥ ጳውሎስ ወደ ሁለተኛ ደረጃነት ዝቅ ያደርጋቸዋል። ከሁሉም የሚበልጠው ጥያቄና ለሁላችንም ግልጽ ሊሆን የሚገባው እጅግ ጠቃሚው የእግዚአብሔር ፈቃድ አካል፥ «ሕይወታችንን የምንመራው ሙሉ በሙሉ ለእግዚአብሔር ተሰጥተን ነው ወይ?» የሚለው ሊሆን ይገባል። ሙሉ ለሙሉ ለእግዚአብሔር ራሳችንን ሰጥተን ስንኖር፥ ፍላጎቶቻችንና እሴቶቻችን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከተገለጹት ጋር አንድ ዓይነት ሲሆኑ፥ አእምሯችን፥ የምናስባቸው ነገሮችና ጠቃሚ ነው ብለን የምናስበው ሁሉ እግዚአብሔር ከሚፈልገው ነገር ጋር ሲጣጣሙ፥ ሌሎች የሚያሳስቡን ነገሮች ሁሉ ግልጽ ይሆኑልናል። ለእግዚአብሔር ክብር የሚኖር ሰው በእግዚአብሔር እየተመራ በሚያልፍበት ሁኔታ ውስጥ ሁሉ የእግዚአብሔር ፈቃድ መልካም፥ ደስ የሚያሰኝና ፍጹም መሆኑን ይገነዘባል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ብዙ ክርስቲያኖች የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ የሚቸገሩባቸውን አንዳንድ ነገሮች ዝርዝር። ለ) ሰውነታችንን መሥዋዕት ማድረግ የእዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ የሚረዳን እንዴት ነው? ሐ) ለእግዚአብሔር ራስን ሙሉ በሙሉ አሳልፎ መስጠት የትዳር ጓደኛን መምረጥ የመሳሰሉትን ነገሮች በሕይወታችን ቀላል የሚያደርገው እንዴት ነው?

  1. እማኞች እግዚአብሔር በሰጣቸው ጸጋ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያገለግላሉ (ሮሜ 12፡3-8)

ዛሬ ወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን ከሚያጋጥማት ችግሮች አንዱ እግዚአብሔር በቀዳሚነት በእኛ ግለሰባዊ ሁኔታ ደስ ይሰኛል የሚል የራስ ወዳድነት ክርስትና ነው። በግል ደኅንነታችን፥ በጸጋ ስጦታዎቻችን፥ በአምልኮ ባርኮታችን፥ ወዘተ ላይ እናተኩራለን። ጳውሎስ ግን ክርስቲያን በዋናነት ሊያተኩር የሚገባው በግል ጉዳይ ላይ ሳይሆን የክርስቶስ አካል በሆነችው ቤተ ክርስቲያን ላይ ሊሆን እንደሚገባ አብራርቷል። ጳውሎስ የሚያስተምራቸው አብዛኞቹ ተግባራዊ ነገሮች እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ እንዴት አብረን ልንኖር እንደሚገባን የሚያሳዩ ናቸው። በዚህ ክፍል ጳውሎስ እያንዳንዱ ክርስቲያን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለማገልገል ሊያስታውሳቸው የሚገባቸውን አራት መሠረታዊ ነገሮች ጠቃቅሷል።

ሀ. ከሌሎች ጋር መዛመድ ማለት የራሳችንን ትክክለኛ ማንነት መገንዘብ ማለት ነው። ከዓለም ከምንማራቸው ነገሮች አንዱ ራሳችንን ከሌሎች ጋር የማወዳደር ዝንባሌ ነው። ስለሆነም ራሳችንን እንደተሻልን የበለጠ የተማርን፥ የበለጠ ስጦታ ያለን አድርገን እንመለከታለን። የዚህ ዓይነቱ አስተሳሰብ ከእግዚአብሔር ሳይሆን ዓለማዊ ነው። ጳውሎስ ማንነታችንንና ግንኙነታችንን እግዚአብሔር በሚያየን መንገድ መገንዘብ እንዳለብን ገልጾአል። በአንድ በኩል ይህ ማለት እግዚአብሔር ምን ያህል እንደወደደን፥ ለእርሱ ምን ያህል አስፈላጊዎች እንደሆንን፥ ከእርሱ ስጦታዎችን እንዳገኘንና ለእርሱ እንደምንጠቅም መገንዘብ ማለት ነው። በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ክርስቲያኖች፥ በተለይም ያልተማሩ ወይም ሴቶች፥ «ለምንም የማልረባ ስለሆንሁ እዚያ ቁጭ ብዬ ልስማ። ለእግዚአብሔር እንደ እገሌና እገሌ አስፈላጊ አይደለሁም» ሊሉ አይችሉም። እንዲህ ዓይነት አስተሳሰብ ለሁላችንም እንዲሞት ልጁን ለላከው እግዚአብሔር ስድብ ነው። ሁላችንም ለእግዚአብሔር አስፈላጊዎች ነን። ይህ እግዚአብሔር የሰጠንን ስጦታዎችና ችሎታዎች አውቀን ለሌሎች ጥቅም መገልገል እንዳለብን ያሳያል። በሌላ በኩል፥ እኛ ከማንም እንደማንሻል መገንዘብ አለብን። የምንኩራራበት ምንም ምክንያት የለንም። ሰዎች ሁሉ፥ ያልተማሩና የተማሩ፥ ወንዶችና ሴቶች፥ ወጣቶችና አረጋውያን ሁሉ በመስቀሉ ሥር እኩል ናቸው። ሁላችንም በጸጋ የዳንን ኃጢአተኞች ነን።

ለ. እያንዳንዱ ክርስቲያን የአንድ አካል ክፍል መሆኑን መገንዘብ ይኖርበታል። ሁላችንም የቤተ ክርስቲያን አካሎች ነን። ዛሬ እንደ ግለሰብ ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው የሚያመልኩ ሰዎች አሉ። እነዚህ ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን ተመልሰው ተግባራቸውን ያከናውናሉ። የቤተ ክርስቲያን አካል ሆነው ለቤተ ክርስቲያን ሕይወት ምንም አስተዋጽኦ አያበረክቱም። ይህ ጳውሎስ ከሚያስተምረው አሳብ ተቃራኒ ነው። ጳውሎስ እያንዳንዱ ግለሰብ የቤተ ክርስቲያን አካል እንደሆነ ያስተምራል። እያንዳንዳችን መንፈስ ቅዱስ በሰጠን ስጦታ ወይም ስጦታዎች አማካኝነት ለአካሉ የምናበረክታቸው ድርሻዎች አሉን። ቤተ ክርስቲያን የሁሉም ክርስቲያን ነች። ሁሉም ክርስቲያን የቤተ ክርስቲያን ሊሆን ይገባል። (መሪዎች ቤተ ክርስቲያንን ስለምናስተዳድር ወይም ስለምንመራ ንብረታችን ናት ብለን እንዳናስብ መጠንቀቅ አለብን። የቤተ ክርስቲያን ዋነኛው ባለቤት እግዚአብሔር ሲሆን፥ የቤተ ክርስቲያን ምእመናን ሁሉ እኩል ድምፅ አላቸው።)

ሐ. አንዳችን ሌላውን እናገለግል ዘንድ እግዚአብሔር ለአማኞች ሁሉ የተለያዩ መንፈሳዊ ስጦታዎችን ሰጥቷል። ሁሉም ስጦታዎች ያሉት ክርስቲያን የለም። ነገር ግን እያንዳንዱ ክርስቲያን ቢያንስ አንድ ስጦታ ተሰጥቶታል። መንፈሳዊ ስጦታ በቀዳሚነት ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት የሚውል ችሎታ ነው። በዛሬው ዓለም ስለ መንፈሳዊ ስጦታዎች ስናስብ አእምሯችን በፍጥነት የሚወነጨፈው እንደ ልሳን፥ ፈውስ፥ ትንቢት፥ ወዘተ… ወዳሉት አስደናቂ ስጦታዎች ነው። ብዙውን ጊዜ እነዚህን መንፈሳዊ ስጦታዎች የምንፈልገው ለራስ ወዳድነት ዓላማ፥ ማለትም ሰዎች በመንፈሳዊነታችን እንዲደነቁ ለማድረግ ነው። ጳውሎስ ግን ብዙ ዓይነት ስጦታዎችና በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ማገልገል የሚቻልባቸው ብዙ መንገዶች እንዳሉ ይነግረናል። ሁሉም አስፈላጊዎች ናቸው።

መ. ዋናው ነገር እግዚአብሔር ለአንድ ክርስቲያን መንፈሳዊ ስጦታ መስጠቱ ወይም ግለሰቡ ስጦታውን መጠቀሙ ብቻ አይደለም። ጳውሎስ ስጦታውን ከምንጠቀምበት ሁኔታ በስተጀርባ ያለው አመለካከታችን አስፈላጊ መሆኑን ያስረዳል። ስለሆነም፥ ትንቢትን በምንናገርበት ጊዜ ከመንፈሳዊ የእምነት ደረጃችን ጋር በተስተካከለ ሁኔታ መሆን አለበት። በችግር ላይ ላሉት በምንሰጥበት ጊዜ በልግስና ልናደርገው ይገባል። አመራራችንም በትጋት የሚካሄድ ሊሆን ይገባዋል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) መንፈሳዊ ስጦታዎችህ ምንድን ናቸው? ለ) በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ እንዴት እየተጠቀምህባቸው ነው? ሐ) አንድ መንፈሳዊ ስጦታ ጥቀስና ይህንኑ ስጦታ እንዴት በተሳሳተ አመለካከት መጠቀም እንደሚቻል ግለጽ። በትክክለኛ አመለካከት መጠቀም የሚቻለውስ እንዴት ነው? እግዚአብሔር ለእርሱ በምንሠራው ሥራ ላይ ብቻ ሳይሆን በሥራው ላይ በነበረን አመለካከት ላይም የሚገደው ለምን ይመስልሃል? መ) ብዙ ምእመናን በአንድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደማገልገል ከቤተ ክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን የሚዟዟሩት ለምን ይመስልሃል? ሠ) በቤተ ክርስቲያንህ ሰዎች መንፈሳዊ ስጦታዎቻቸውን ተግባራዊ ሊያደርጉ የሚችሉባቸውን የአገልግሎት ዓይነቶች ዘርዝር። ሰዎች የበለጠ በአገልግሎት ውስጥ እንዲሳተፉ ልታደርግ የምትችለው እንዴት ነው? ረ) በቤተ ክርስቲያንህ ከሌሎች አማኛች ጋር እኩል አይደለንም የሚል ስሜት ያላቸው ሰዎች አሉ? እነዚህ እነማን ናቸው? የእኩልነት ስሜት እንዲሰማቸው ምን ልታደርግ ትችላለህ?

  1. አማኞች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር የፍቅር ግንኙነት ያደርጋሉ (ሮሜ 12፡9-13)

በአማኞች ማኅበረሰብ ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች በራስ ወዳድነት አንድን ነገር ከሌላው ለመውሰድ የሚፈልጉ ሳይሆኑ፥ እርስ በርሳቸው የሚዋደዱ መሆን አለባቸው። ፍቅር ከራሳችን በላይ ሌላውን ሰው እንድንረዳ ነው የሚፈልገው። እያንዳንዱ ክርስቲያንና ባጠቃላይም የአማኞች አካል ክፋትን በሚጠሉና በጎነትን በሚያስፋፉ፥ ትሑት በሆኑና ከራሳቸው በላይ ሌሎችን ለመጥቀም በሚፈልጉ፥ ወዘተ… ወገኖች የተገነባ እንዲሆን ይሻል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ጳውሎስ በክርስቲያኖች መካከል ስለሚኖረው ግንኙነት የገለጸውን ሃሳብ ከቤተ ክርስቲያንህ ሁኔታ ጋር አነጻጽር፡፡ የቤተ ክርስቲያንህ ጠንካራና ደካማ ጎኖች የትኞቹ ናቸው? ለቤተ ክርስቲያንህ ጳውሎስ በዚህ ክፍል የገለጸውን ባሕርይ እንድታንጸባርቅ ለመርዳት ምን ልታደርግ ትችላለህ?

  1. አማኞች ከክርስቲያኖችም ሆነ ክርስቲያኖች ካልሆኑ ሰዎች ጋር ሰላማዊ ግንኙነት ያደርጋሉ (ሮሜ 12፡14-21)።

ከሰዎች ጋር በሰላም ለመኖር ምንም ያህል ጥረት ብናደርግም፥ በግንኙነቶች ውስጥ ችግሮች ይከሰታሉ። ከአማኞችም ሆነ አማኞች ካልሆኑ ሰዎችም ጋር የግንኙነት ችግሮች ይከሰታሉ። ጳውሎስ ደኅንነታችንን እግዚአብሔርን በሚያስከብር መልኩ ለመኖር ከፈለግን፥ ከማንስማማቸው ሰዎች ጋር ስለሚኖረን አመለካከት መጠንቀቅ እንዳለብን። ግንኙነታችንን የሚመለከቱ አያሌ ትእዛዛትን ሰጥቷል።

ሀ. ከሌሎች ጋር በሰላም ለመኖር ፈልጉ።

ለ. በኩራት ሌሎችን ላለመናቃችሁ እርግጠኞች ሁኑ። በሮም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የነበሩ ብዙ አማኞች ባሮች እንደነበሩ አትዘንጋ። ነገር ግን ጥቂት ባሪያ አሳዳሪዎችም ነበሩ። ጥቂት ምእመናን የተማሩ ሲሆኑ፥ አብዛኞቹ ግን ያልተማሩ ነበሩ። ይህ ልዩነታቸውም አንዳቸው ከሌላቸው እንደሚበልጡ እንዲያስቡ ሊገፋፋቸው ይችላል። ጳውሎስ አንዱ ሰው ለእግዚአብሔር ከሌላው የተሻለ እንዳልሆነ ገልጾአል። ስለሆነም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ኩራት፥ ጎሰኝነት፣ ወዘተ ሊኖሩ አይገባቸውም።

ሐ. ሰዎች በሚቃወሙህ ጊዜ እነርሱን መጥላትና መበቀል እንደሌለብህ እርግጠኛ ሁን። ነገር ግን በጎነታቸውን በመሻት፥ እግዚአብሔር በሕይወታቸው እንዲሠራ በመጠየቅ ባርካቸው። ቅጣታቸውን ለእግዚአብሔር ተወው። የጥላቻንና የክፋትን ዑደት ማስወገድ የሚቻልበት ብቸኛው መንገድ መልካምን ለማድረግ በመወሰን ነው። አንድን ሰው ብንበቀል ራሳችንን፥ ቤተሰባችንን፥ ቤተ ክርስቲያናችንን፥ ማኅበረሰባችንንና አገራችንን የሚያጠፋ የክፋት ዑደት እንቀጥላለን፡፡

የውይይት ጥያቄ፡- ብዙ ቤተ ክርስቲያኖቻችን በመክፋፈል የታወቁ ናቸው። ሀ) ይህ የሆነው ለምንድን ነው? ለ) በቤተ ክርስቲያን ወይም በቤተ እምነትህ ዐቢይ ክፍፍል ከፈጠሩት ነገሮች አንዱን ነቅሰህ አውጣ። ጳውሎስ ባስተማረው መሠረት፥ አለመግባባቶቹን ለማቆም ክርስቲያኖች እንዴት መመላለስ ይኖርባቸዋል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version