የጳውሎስ የግል ምስክርነት፣ ዕቅዶችና ሰላምታ (ሮሜ 15፡14-16፡27)

፩. የጳውሎስ የግል ምስክርነትና ዕቅዶች (ሮሜ 15፡14-33)

የውይይት ጥያቄ፡- ሮሜ 15፡14-33 አንብብ። ሀ) ጳውሎስ ስለ ራሱ የሰጠው መግለጫ ለሮሜ ሰዎች መልእክት የጻፈበትን ሁኔታ የሚያስረዳው እንዴት ነው? ለ) ጳውሎስ ስለ ወደፊት አገልግሎቱ ምን አለ?

ሰዎችንና አሳባቸውን በተሳሳተ መንገድ መረዳቱ ቀላል ነው። ብዙዎቻችን ከሰዎች ቃላት በስተጀርባ የተደበቁትን ፍላጎቶችን እየፈለግን በተሳሳተ መንገድ እንተረጉማለን። ከዚህም የተነሣ በማያስፈልግ መቀያየም ውስጥ እንገባለን። ጳውሎስ በአካል የማያውቁት የሮሜ ምእመናን ትምህርቱን በተሳሳተ መንገድ እንዳይረዱት ሰግቶ ነበር። ስለሆነም፥ ጳውሎስ በግልጽና ራሱን ዝቅ አድርጎ አሳቡን ይነግራቸዋል።

ሀ. ጳውሎስ የሮሜን ክርስቲያኖች ድነት (ደኅንነት) ማግኘትና በመንፈሳዊ ባሕርያት የታጀበ ሕይወት መምራታቸውን እንደማይጠራጠር ገልጾአል። መልእክቱን የጻፈላቸው እንደ «የአሕዛብ ሐዋርያነቱ» ኃላፊነቱን ለመወጣት ነበር። ጳውሎስ አሕዛብ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ስለማግኘታቸው ጉዳይ በግልጽ የጻፈው አሳብ የአይሁድ ክርስቲያኖችን ሊያስቀይም እንደሚችል በመገንዘቡ፥ ያስተማረውን ነገር በግልጽ ሊነግራቸው ፈለገ። እግዚአብሔር ለአሕዛብ መልካሙን የምሥራች የማካፈልን ልዩ አገልግሎት ሰጥቶታል። ጳውሎስም የአሕዛብ አማኞችን እንደ ቅዱስ መሥዋዕት በማቅረብ እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት ፈለገ።

ለ. የጳውሎስ ሸክም በቀዳሚነት ለአሕዛብ የክርስቶስን ወንጌል መስበክ ነበር። በቀዳሚነት ለማገልገል የፈለገው ደግሞ ከዚህ በፊት ወንጌል ባልተሰበከባቸው አካባቢዎች ነበር። ለዚህም ነበር ጳውሎስ እስከዚህ ጊዜ ድረስ ወደ ሮም ለአገልግሎት ያልሄደው። እግዚአብሔር ጳውሎስ ወንጌሉን ከኢየሩሳሌም ወደ ኤልሪቆም (በሰሜን መቄዶንያ ውስጥ የምትገኝና አሁን በአልባኒያና ዩጎዝላቪያ ውስጥ ያለች ከተማ) በመውሰድ ጥሪውን ከፍጻሜ እንዲያደርስ ረድቶታል። እግዚአብሔር በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ተአምራትን እንዲሠራ በማድረግ የጳውሎስን አገልግሎት አጽድቋል።

ሐ. ወንጌሉ ባልተሰበከባቸው አካባቢዎች የማገልገል ጥሪው ከሮም ወደ ምዕራባዊ ጫፍ (ስፔይን) እየወሰደው ነበር። ይህን አገልግሎት በሚያካሂድበት ጊዜ እግረ መንገዱን የሮሜ ክርስቲያኖችን ለማየት ሲወጥን የነበረውን የረዥም ጊዜ ፍላጎቱን ለማሟላት አሰበ። ጳውሎስ በሮሜ ለተወሰነ ጊዜ ከቆየ በኋላ ክርስቲያኖቹ ወንጌሉን በማሰራጨቱ ረገድ አብረውት እንደሚሠሩ ተስፋ አደረገ። ይህም ለምሥራቃዊ የሮም ክፍል ወንጌሉን በመስበኩ በኩል የፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን ያበረከተችውን አስተዋጽኦ የሚመስል ነበር (ፊልጵ. 4፡10-18)።

መ. ጳውሎስ ወደ ሮሜ ከመሄዱ በፊት የመቄዶንያ (ሰሜን ግሪክ) እና አካይያ (ደቡብ ግሪክ) አሕዛብ ክርስቲያኖች ለድሀ የአይሁድ ክርስቲያኖች ያወጡትን ስጦታ ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዞ ነበር። በአካል ባንተዋወቅም እንኳን የክርስቶስ አካል ክፍሎች የሆንን ሁሉ እርስ በርሳችን ልንረዳዳ ይገባናል። የአይሁድ ክርስቲያኖች ለአሕዛብ ክርስቲያኖች መንፈሳዊ በረከትን ስላመጡ፥ በአሕዛብ ክርስቲያኖች የገንዘብ ችግር ለደረሰባቸው አይሁዳውያን ድሆች እርዳታ መሰጠቱ ተገቢ ነበር።

ሠ. ጳውሎስ የሮሜ ክርስቲያኖች እንዲጸልዩለት ጠየቀ። ለሌሎች መጻለይ በአገልግሎታቸው ውስጥ ከምንሳተፍባቸው መንገዶች አንዱ መንገድ ነው። የጳውሎስ ጭንቀት ምን ነበር? በመጀመሪያ፥ በኢየሩሳሌም ሊያጠፉት ስለሚፈልጉ የማያምኑ አይሁዶች ያስብ ነበር። ሁለተኛ፥ በኢየሩሳሌም የሚገኙ አይሁዳውያን ክርስቲያኖች በአሕዛብ ክርስቲያኖች ላይ መጥፎ ስሜት ይዘው የሚያመጣላቸውን ስጦታ ላለመቀበል እንዳይወስኑ ሰግቶ ነበር።

የውይይት ጥያቄ፡- ሮሜ 16ን አንብብ። በዚህ የሰላምታ ምዕራፍ ውስጥ የሚገኙትን ለየት ያሉ ነገሮች ዘርዝር።

፪. ጳውሎስ በሮሜ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለሚያውቃቸው ሰዎች ያቀረበው ሰላምታ (ሮሜ 16)

ጳውሎስ በሮሜ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለሚያውቃቸው ሰዎች ሰላምታ በማቅረብ መልእክቱን ይደመድማል። እንዲህ ዓይነት ረዥም የሰላምታ ዝርዝር በጳውሎስ ጽሑፎች ውስጥ ያልተለመደ በመሆኑ፥ ምሁራን ጳውሎስ በአካል ባይጎበኛቸውም የሮሜን ክርስቲያኖች እንደሚያውቃቸው ለማሳየት እየሞከረ ነበር ይላሉ። ነገር ግን በሮሜ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከነበሩት ብዙ ሰዎች ጋር ጥልቅ ግላዊ ወዳጅነት ነበረው።

ሀ. ፌቤን ከቆሮንቶስ ከተማ 8 ኪሎ ሜትሮች ያህል ወጣ ብላ በምትገኝ የክንክራኦስ ከተማ የምትኖር ክርስቲያን ነበረች። የጳውሎስን መልእክት ወደ ሮም ያደረሰችው እርሷው ነበረች። ጳውሎስ እንደ ዲያቆንና ልዩ የክርስቶስ አገልጋይ እንዲቀበሏት ጠይቋቸዋል።

ለ. ጳውሎስ ለሚከተሉት ወገኖችም ልዩ ሰላምታ ልኮላቸዋል (ሮሜ 16፡1-16)።

  1. ወደ ሮም ለተመለሱት ጵርስቅላና አቂላ፡- እነዚህ ልዩ የጳውሎስ ወዳጆች ሕይወታቸውን ከአደጋ ላይ እየጣሉ ሁልጊዜም ከጳውሎስ ጎን የቆሙ ሲሆን፥ ለግሪክና ለትንሹ እስያ አብያተ ክርስቲያናት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርገዋል። እንደ ጳውሎስ ያሉት ታላላቅ ወንጌላውያን ተግባራቸውን የሚወጡት ብቻቸውን አልነበረም። እግዚአብሔር ሁልጊዜም ወንጌላውያንን የሚረዱ ሰዎችን ያመጣል። ያለ እነዚህ ወገኖች እገዛ ቤተ ክርስቲያን ልታድግ አትችልም። ወንጌሉን በማሰራጨቱ ረገድ እግዚአብሔር አቂላና ጵርስቅላን በከፍተኛ ደረጃ ተጠቅሞባቸዋል። አሁንም እንኳ እግዚአብሔር እየተጠቀመባቸው ነበር። ምንም እንኳ የሙሉ ጊዜ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ያልነበሩ በድንኳን ሰፊነት የሚተዳደሩ ቢሆኑም፥ እግዚአብሔር መንግሥቱን ለማስፋፋት ተጠቅሞባቸዋል። በሮም በቤታቸው ውስጥ የቤተ ክርስቲያን አምልኮ ይካሄድ ነበር።
  2. አጤኔጦን ኤፌሶን በምትገኝበት የእስያ አውራጃ የመጀመሪያው አማኝ ነበር። ማርያ ለሮሜ ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ዕድገት ተግታ ትሠራ ነበር።
  3. አንዲራኒቆንና ዩልያን ምናልባትም የጳውሎስ ዘመዶች የሆኑ ባልና ሚስት ሳይሆኑ አይቀሩም። ከጳውሎስ ጋር ታስረው የነበሩ ሲሆኑ፥ ሐዋርያት ተብለው ተጠርተዋል። ምሁራን ጳውሎስ በዚህ ስፍራ ምን ማለቱ እንደሆነ ይከራከራሉ። እነዚህ ሁለት ሰዎች «ዘመዶቹ» የሆኑት አይሁዶች በመሆናቸው ነው ወይስ የጳውሎስ የሩቅ ዘመዶች ይሆኑ? ከጳውሎስ ጋር አብረውት የታሰሩት የት ነበር? ስማቸው በሐዋርያት ሥራ ውስጥ አልተጠቀሰም። ጳውሎስ ሐዋርያት ብሎ ሲጠራቸው ምን ማለቱ ነው? ምናልባትም ጳውሎስ የቃሉን ሰፊ ትርጉም በመውሰድ እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን ምሥረታ እንደተጠቀመባቸው መግለጹ ይሆናል። እነዚህ ሁለቱ ከእግዚአብሔር ዘንድ ይህንን ስጦታ ተቀብለው ነበር (ሴቷ ዩልያ «ሐዋርያ» እንደተባለች ልብ በል)
  4. ኢሩባኖን፥ ጵልያጦን፥ ስንጣክን፥ ኤጤሌን የሚሉት ስሞች ሁሉ በሮም ቤተ መንግሥት ውስጥ የታወቁ የባሪያዎች ስሞች ነበሩ። ይህም ወንጌሉ በኔሮ ቤተ መንግሥት እንዴት ሥር ሰድዶ እንደገባ ሊያሳይ ይችላል። ጳውሎስ በኋላ ታስሮ ሳለ ለኔሮ የግል ጠባቂዎች መስክሮላቸዋል (ፊልጵ. 1፡13)።
  5. አርስጣባሉስ ምናልባትም የታላቁ የሄሮድስ የልጅ ልጅና የሄሮድስ አግሪጳ ቀዳማዊ ወንድም ሳይሆን አይቀርም። ይህም ወንጌሉ ወደ ቤተ መንግሥቱ ባለሥልጣናትም እንደደረሰ ያሳያል።
  6. ፕሮፊሞና፥ ጢሮፊሞሳ (ምናልባትም እኅትማማቾች) እና ጠርሲዳ ለጌታ ባበረከቱት አገልግሎት የሚታወቁ ሴቶች ነበሩ።)

ሐ. ጳውሎስ እነዚህ ክርስቲያኖች የሐሰት ትምህርትን እንዳያምኑ ያስጠነቅቃል (ሮሜ 16፡17-20)። ቤተ ክርስቲያንን የሚከፋፍል ትምህርት ከሚያስተምሩ ሰዎች መራቅ ያስፈልጋቸው ነበር። ይህ ዛሬ ለእኛም ጥሩ ማስጠንቀቂያ ነው። በጳውሎስ ዘመን የሐሰት አስተማሪዎች እንደነበሩ ሁሉ፥ በዘመናችንም አሉ። የሐሰት አስተማሪዎችን እንዴት ለይተን እናውቃለን? ቀዳሚው መለያ ክብሩን ማን እንደሚወስድ ማጤን ነው። አንዳንድ ሰዎች አንደበተ ርቱዕ ሆነው በመቅረብ ብዙዎችን ቢያታልሉም፥ ራሳቸውን እንጂ ክርስቶስን አያከብሩም። አንዳንድ ጊዜ አስተማሪዎች በሌሎች ኪሳራ ባለጸጋ ይሆናሉ። ክርስቲያኖች ራሳቸውን መጠበቅ ያለባቸው እንዴት ነው? ከእንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ጋር ግንኙነት ወይም ኅብረትን ባለመፍጠር ነው። ጳውሎስ በክርስቲያናዊ አንድነት ላይ አጽንኦት ሰጥቷል። ነገር ግን አንድነትና ኅብረት ሊያደርጉ የሚገባቸው እግዚአብሔርን ለማክበር የሚፈልጉ ሰዎች ናቸው። ክርስቲያኖች ነን እያሉ አንድነትን የሚያሰናክሉና የሐሰት ትምህርትን የሚያስፋፉ ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን ኅብረት ውጭ መሆን አለባቸው። አለበለዚያ ከእንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ጋር ኅብረት ማድረጉ ለእነርሱ የተሳሳተ ሃሳብ ረዳት መሆን ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ቤተ ክርስቲያንህን የሚያስቸግሩትን አንዳንድ የሐሰት አስተማሪዎች ዘርዝር። ለ) ሌሎች ክርስቲያኖችና ሽማግሌዎች እንዴት እየተቀበሏቸው ነው? ሐ) ጳውሎስ እነዚህን የሐሰት አስተማሪዎች እንዴት እንድንቀበላቸው የሚፈልግ ይመስልሃል? መ) ዛሬ ያንን ለማድረግ የማንፈልገው ለምንድን ነው?

መ. ጳውሎስ ሰላምታ ያስተላልፋል (ሮሜ 16፡21-24)።

  1. ጢሞቴዎስ ወንጌሉን በማሰራጨቱ በኩል የጳውሎስ ረዳትና የሥራ ባልደረባ።
  2. ሉቂዮስ፥ ኢያሶን፥ ሱሲጴጥሮስ- ምናልባትም የቆሮንቶስና የመቄዶኒያ አብያተ ክርስቲያናት ዐበይት መሪዎች ሳይሆኑ አይቀሩም (የሐዋ. 17፡5-9፤ 20፡4)።
  3. ጤርጥዮስ፥ የጳውሎስን መልእክት ጸሐፊ።
  4. የቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን መሪና ብዙውን ጊዜ ታይተስ ጆስትስ በመባል የሚታወቀው ጋይዮስ (የሐዋ. 18፡7፤ 1ኛ ቆሮ. 1፡14)።
  5. በቆሮንቶስ መንገዶች ጨምሮ ብዙ ጉዳዮችን የሚያስፈጽም ቁልፍ የፖለቲካ መሪ የሆነው ኤርስጦስ። ኤርስጦስ አማኝ መሆኑ አያጠራጥርም።

ሠ. ጳውሎስ መልእክቱን በቡራኬ ይደመድማል (ሮሜ 16፡25-27)። የሮሜ መልእክት በወንጌል ላይ ያማከለ መጽሐፍ ነው። የወንጌሉም አሳብ በዚህ የማጠቃለያ ቡራኬ ላይ ያማክላል። ክርስቶስ እስከመጣበት ጊዜ ድረስ ከሰዎች በምሥጢርነት ተሰውሮ የነበረው ወንጌል አሁን ተገልጧል። የእግዚአብሔር ፍላጎት ሰዎች በክርስቶስ አምነው የታዛዥነትን ሕይወት እንዲመሩ ነበር። የሮሜን ክርስቲያኖች በዚህ ወንጌል የሚመሠርታቸው ደግሞ እግዚአብሔር ነበር። የጳውሎስ ትልቁ ፍላጎት የእግዚአብሔር ለዘላለም መክበር ነበር።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ዛሬ እግዚአብሔርን የምናስከብርባቸውን መንገዶች ዘርዝር። ለ) ይህ እንዴት የሕይወታችን ዋነኛ ዓላማ መሆን እንዳለበት ግለጽ። ሐ) በምታደርገው ነገር ሁሉ ለእግዚአብሔር ክብርን እያመጣህለት እንደሆነ በጸሎት ጠይቀው። ዛሬ ለእርሱ ክብር ለመኖር ራስህን እንደገና አሳልፈህ ስጥ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

3 thoughts on “የጳውሎስ የግል ምስክርነት፣ ዕቅዶችና ሰላምታ (ሮሜ 15፡14-16፡27)”

    1. ወንድሜ አዱኛ፣

      በመጀመሪያ ለዝግጅት ክፍላችን ስለጻፍክልን አመሰግናለሁ፡፡ የወንጌል በድረ ገጽ አገልግሎት ዌብ ሳይት (https://ethiopiansite.com/) በርካታ መንፈሳዊ ጽሑፎችን የያዘ ሳይት ነው፡፡ በዌብ ሳይቱ የድነት (የደኅንነት) ትምሕርቶች (https://goo.gl/fDtBXd)፣ የደቀ መዝሙር ማሰልጠኛ ማኑዋሎች (https://goo.gl/26UzGK)፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መሳሪያዎች (https://goo.gl/Eou24Y)፣ ለተለያዩ ጥያቄዎች መልስ የሚሰጡ አጫጭር የጥናት ጽሑፎች (https://goo.gl/UWbZjw)፣ ወዘተ ተካተዋል፡፡ እንግዲህ እንደ ምርጫህ ሊንኮቹን በመጫን ጥናትህን ማካሄድ ትችላለህ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የግል ጥያቄዎች ቢኖርህ በሚከተለው ኢሜይል ልትልክልኝ ትችላለህ፣ በደስታ ለመርዳት ዝግጁ ነኝ (tsegaewnet@gmail.com)፡፡

      አዳነው ዲሮ
      የወንጌል በድረገጽ አገልግሎት አዘጋጅ

  1. Pingback: የሮሜ መልእክት ጥናት – ወንጌል በድረ-ገፅ አገልግሎት

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading