Site icon

የገላትያ መልእክት ልዩ ባሕርያት፣ መዋቅር፣ እና አስተዋጽኦ

  1. የገላትያ መልእክት ምናልባትም ጳውሎስ ከጻፋቸው እጅግ ጠንካራና ቁጡ ደብዳቤዎች ሁሉ ሳይልቅ አይቀርም። ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች ወንጌሉን ለመመስከር ሲል በድንጋይ ከተወገረና ከሞት አፋፍ ላይ ከተረፈ በኋላ እውነተኛውን ወንጌል ትተው የሐሰት ትምህርቶችን በመከተል ላይ መሆናቸውን መስማቱ በጥልቀት አቆሰለው። ከሌሎች የጳውሎስ መልእክቶች በተቃራኒ፥ በገላትያ መልእክት ውስጥ ምንም ዓይነት የማበረታቻና የምስጋና ቃላት አልተካተቱም። ጳውሎስ የመልእክቱ ጸሐፊ መሆኑን ከነገራቸው በኋላ በቀጥታ ወደ ተግሣጽ አምርቷል። ጳውሎስ እንደ «የማታስተውሉ» (ገላ. 3፡1)፥ «አዚም የተደረገባችሁ» (ገላ. 3፡1፥ «የተረገማችሁ» (ገላ. 1፡8-9)፥ «የሚያውኩአችሁ ይቆረጡ» (ገላ. 5፡12)፥ ወዘተ… የሚሉ ጠንካራ አገላለጾችን ሰንዝሮባቸዋል። ለገላትያ ሰዎች የነበረው ፍቅርና መገደድ፥ እንዲሁም ለወንጌሉ እውነት የነበረው ጽኑ ስሜት ወደ ስሕተት ከሚነዳቸው ከማንኛውም ነገር ጋር እንዲታገል አድርጎታል።
  2. ይህ የጳውሎስ የመጀመሪያው መልእክት ነበር። ለረዣዥም መልእክቶች ቅድሚያ በመሰጠቱ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ ከገላትያ ቀደም ብለው ከሰፈሩት የሮሜና፥ የ1ኛና 2ኛ ቆሮንቶስ መልእክቶች በፊት ነበር የተጻፈው።
  3. ስለ ሰው ድነት (ደኅንነት) ወይም አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ ግንኙነት ስለሚመሠርትበት ሁኔታ የሚያስተምሩ በመሆናቸው የገላትያና የሮሜ መልእክቶች ተመሳሳይነት ይታይባቸዋል። ነገር ግን የሮሜ መልእክት ነገረ መለኮታዊውን እውነት እንደ የክፍል ውስጥ ትምህርት ሲያቀርብ፥ ገላትያ በመጋቢነት ላይ በማተኮር ጠንካራ አገላለጾችን ይጠቀማል። ለዚህም ምክንያቱ የወንጌሉ ጠላቶች የእግዚአብሔርን መንጋ ማጥቃታቸውና ክርስቲያኖችን ለአደጋ ማጋለጣቸው ነበር።

የገላትያ መልእክት መዋቅር

አብዛኛዎቹ የጳውሎስ አጫጭር መልእክቶች ሁለት መሠረታዊ ክፍሎችን ያካትታሉ። በመጀመሪያ፥ ጳውሎስ ቁልፍ ነገረ መለኮታዊ እውነቶችን የሚያቀርብባቸው ክፍሎች አሉ። ብዙዎቻችን ስለ እውነት አጥልቀን ለማሰብ አንፈልግም። አምልኮ ፥ ምስጋና ወይም አገልግሎት ደስ ያሰኘናል። ጳውሎስ ግን ሁልጊዜም ትክክለኛ አምልኮና ተግባራት በትክክለኛ እውቀት ላይ እንዲመሠረቱ አጥብቆ ይመክራል። የምናምነው አሳብ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ካልሆነ እግዚአብሔር እንደሚፈልገው ልናመልክና ልናገለግል አንችልም። ገላትያ 1-4 በቀዳሚነት የመሠረተ እምነት ትምህርቶችን ያቀርባል። ጳውሎስ ሰዎች በሚያከናውኗቸው ተግባራት ሳይሆን በክርስቶስ በማመናቸው ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ ግንኙነት እንደሚኖራቸው ያብራራል።

የውይይት ጥያቄ ሀ) ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ የሐሰት አስተማሪዎች የሚቃወሟቸውን አንዳንድ መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮዎች ዘርዝር። በእነዚህ ጉዳዮች ላይ ግልጽ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ግንዛቤ ማግኘት ለምን ያስፈልጋል? ለ) ብዙ ክርስቲያኖች እውነትን ችላ እያሉ እንደ አምልኮ ባሉት ሌሎች ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩት ለምንድን ነው? ሐ) አምልኳቸውና ተግባራቸው እንደ እግዚአብሔር ቃልና ፈቃድ ይሆን ዘንድ ክርስቲያኖች ሁሉ በእውነት ላይ እንደ ተመሠረቱ መሪዎች በምን ሊያረጋግጡ ይችላሉ?

ሁለተኛው የጳውሎስ መልእክት ዓቢይ ክፍል በተግባራዊ ጉዳዮች ላይ ያተኩራል። ይህም እንደ ክርስቲያኖች እንዴት ሊመላለሱ እንደሚገባ የሚያሳይ ነው። ጳውሎስ በተግባር እስካልተገለጠ ድረስ እምነት ዋጋ እንደ ሌለው ያስረዳል። በ1ኛ ቆሮንቶስ 8፡1 ላይ እንደ ገለጸው እውቀት ያስታብያል። የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት እያውቁ ተግባራዊ አለማድረጉ ለክርስቲያኖች አደገኛ ነው። በዘመናችን ያሉት ክርስቲያኖች አምልኮን እየወደዱ በሥራ ቦታና በትምህርት ቤት የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ተግባራዊ አያደርጉም። ገላትያ 5-6 እግዚአብሔርን በሚያስደስት መንገድ ስለ መመላለስ ተግባራዊ ጉዳዮችን ያነሣል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እውነትን በማወቅና በአምልኮ መሳተፍ ቀላል ሆኖ ሳለ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ማኅበረሰቡን በሚለውጥ መልኩ ተግባራዊ ማድረግ ከባድ የሚሆንባቸውን መንገዶች ግለጽ። ለ) ክርስቲያኖች በማኅበራዊ ሕይወታቸው፥ በሥራ፥ ከመንግሥት ወይም ከድሆች ጋር ባላቸው ዝምድና ተግባራዊ የማያደርጓቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች ምን ምንድን ናቸው? ሐ) ሰዎች እምነታቸውን በኅብረተሰቡ ውስጥ በተግባር እንዲያሳዩ ለመርዳት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ምን ድርሻ ሊኖራቸው ይገባል?

የገላትያ መልእክት አስተዋጽኦ

  1. መግቢያ (ገላ. 1፡1-10)
  2. ጳውሎስ ወንጌሉ ከእግዚአብሔር እንደ መነጨና ሌሎችም ሐዋርያት እንዳጸደቁት ይናገራል (ገላ. 1፡1-2፡10)

ሀ. ጳውሎስ ወንጌሉን በመገለጥ በቀጥታ ከእግዚአብሔር ተቀበለ (ገላ. 1፡11-12)።

ለ. ጳውሎስ ወንጌሉን ከኢየሩሳሌም ሐዋርያት እንዳልተቀበለ ያስረዳል (ገላ. 1፡13-24)።

ሐ. የኢየሩሳሌም ሐዋርያት የጳውሎስን ወንጌል አጽድቀዋል (ገላ. 2፡1-10)።

  1. ጴጥሮስ በአንጾኪያ ስለ ወንጌሉ የተሳሳተ ግንዛቤ የሚፈጥር ተግባር በመፈጸሙ ጳውሎስ ተጋፈጠው (ገላ. 2፡11-21)።
  2. ጳውሎስ ድነት (ደኅንነት) ሕግን በመጠበቅ ሳይሆን በክርስቶስ በማመን እንደሚገኝ ገልጾአል (ገላ. 3-4)።

ሀ. ድነት (ደኅንነት) በእምነት እንደሚገኝ የሚያሳይ ከገላትያ ክርስቲያኖች ልምምድ የተወሰደ ማረጋገጫ (ገላ. 3፡1-5)።

ለ. ድነት (ደኅንነት) በእምነት እንደሚገኝ የሚያሳይ የብሉይ ኪዳን ማረጋገጥ (ገላ. 3፡6-4፡31)።

  1. ጳውሎስ የእምነት ሕይወት ምን እንደሚመስል ያብራራል (ገላ. 5፡1-6፡10)።

ሀ. የእምነት ሕይወት ለንጽሕናና ሌሎችን ለማገልገል የሚያስችል ነጻነት ያስገኛል (ገላ. 5፡1-15)።

ለ. የእምነት ሕይወት የኃጢአት ተፈጥሯችንን የሚያሸንፍና የመንፈስ ፍሬን የሚያፈራ መንፈስ ቅዱስን ያስገኛል (ገላ. 5፡16-6፡10)።

  1. መደምደሚያ (ገላ. 6፡11-18)

Exit mobile version