Site icon

ጳውሎስ ወንጌሉ ከእግዚአብሔር እንደ መጣና በሐዋርያት እንደ ጸደቀ ያሳያል (ገላ. 1፡11-2፡10)።

የሐሰት አስተማሪዎቹ ጳውሎስ እውነተኛ ሐዋርያ እንዳልሆነ፥ መልእክቱም አንድም ራሱ የፈጠረው አሊያም ወደ እርሱ በሚተላለፍበት ጊዜ እንደ ተበረዘ በመግለጽ ይከስሱት ነበር። ምናልባትም ደግሞ በኢየሩሳሌም የሚገኙ ሐዋርያት በማይቀበሉት መንገድ እንደ ለወጠው ገልጸው ነበር። ጳውሎስ ንጹሑን ወንጌል የሚያስተምር እውነተኛ ሐዋርያ መሆኑን በመግለጽ ለዚህ ክስ ምላሽ ለመስጠት ፈለገ። ሐዋርያት እንኳን ትምህርቱን አጽድቀውለት ነበር። ስለሆነም፥ ጳውሎስ እግዚአብሔር ለሐዋርያነት ከጠራው ጊዜ አንሥቶ ለገላትያ ሰዎች እስከሚጽፍበት ጊዜ ድረስ ያሳለፈውን ሕይወት ጠቅለል አድርጎ አቅርቧል። የጳውሎስ ክርክር በሦስት ዐበይት ነጥቦች ላይ የተመሠረተ ነበር።

  1. ጳውሎስ የወንጌል መልእክቱን ከክርስቶስ በቀጥታ በመገለጥ ተቀብሏል (ገላ 1፡11-12)። ጳውሎስ ክርስቶስ በምድር ላይ በነበረበት ጊዜ ባይከተለውም በተአምራዊ መንገድ ከሞት ከተነሣው ክርስቶስ ጋር ተገናኝቶ የወንጌሉን መልእክት ተቀብሏል። ስለሆነም የሐሰት አስተማሪዎች ከሚሉት በተቃራኒ ጳውሎስ መልእክቱን አልፈጠረውም። ወይም የተበረዘ መልእክት አልተቀበለም።
  2. ጳውሎስ ወንጌሉን ከሐዋርያት ሊቀበል እንደማይችል ያብራራል (ገላ. 13-24)። ከክርስቶስ ጋር ከመገናኘቱ በፊት ጳውሎስ እንደ ሐሰተኛ አስተማሪዎቹ ለብሉይ ኪዳን ቀናዒ ነበር። ለዚህም ነበር ቤተ ክርስቲያንን ያሳደደው፡፡ ስለዚህ፥ ጳውሎስ እንደ የሐሰት አስተማሪዎቹ ሁሉ ሕግጋትን ስለመከተል ጽኑ አቋም ይዞ ነበር ያደገው። ነገር ግን ጳውሎስ በእግዚአብሔር ተጠራ፤ ክርስቶስም ራሱን ገለጠለት። ጳውሎስ ይህን ሲል በደማስቆ መንገድ ከክርስቶስ ጋር ስለተገናኘበት ራእይ መናገሩ ነበር። ጳውሎስ ድነትን (ደኅንነትን) ካገኘ በኋላ የሐዋርያት ደቀ መዝሙር ለመሆን ወደ ኢየሩሳሌም አልሄደም። ነገር ግን ወደ ዓረቢያ ከሄደ በኋላ ወደ ደማስቆ በመመለስ ድነት (ደኅንነት) በእምነት ብቻ እንደሚገኝ የሚያስረጻውን ወንጌል ሰበከ። ጳውሎስ በመጨረሻው ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዞ ከጴጥሮስና የክርስቶስ ወንድም ከሆነው ያዕቆብ ጋር ምሥጢራዊ ስብሰባ ያደረገው ደኅንነቱን ካገኘ ከሦስት ዓመታት በኋላ ነበር። ከዚያ ከየትኛቹም ሐዋርያት ርቆ ወደ ሶርያና ኪልቅያ አውራጃዎች ሄደ። ይህም ጳውሎስ በኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን እንዳይታወቅ አድርጎታል። ስለ ተአምራዊ ለውጡ ከመስማታቸው በቀር ሌላ የሚያውቁት ነገር አልነበረም። ይህም ጳውሎስ መልእክቱን ከሐዋርያት እንዳላገኘ ያሳያል።
  3. ጳውሎስ የኢየሩሳሌም ሐዋርያትን ድጋፍ አግኝቷል (ገላ. 2፡1-10)። ጳውሎስ ምናልባትም ድነትን (ደኅንነትን) ካገኘ ከ14 ዓመታት በኋላ ኢየሩሳሌምን እንደገና የጎበኘ ይመስላል። ምንም እንኳ አንዳንድ ምሁራን ይህ ጉብኝት በኢየሩሳሌም ጉባኤ ወቅት የተደረገ መሆኑን ቢናገሩም (የሐዋ. 15)፥ ጳውሎስ የሄደው በኢየሩሳሌም ረሃብ በተነሣ ጊዜ የርዳታ ገንዘብ ለማድረስ ይመስላል (የሐዋ. 11፡27-30)። ከዚያ በኋላ ጳውሎስ ከሁሉም የቤተ ክርስቲያን መሪዎችና ሐዋርያት ጋር በግል ተገናኘ፡፡ ቲቶንም ይዞ ነበር የመጣው። ቲቶ ያልተገረዘ አሕዛብ ክርስቲያን ነበር። ጳውሎስ ድነት (ደኅንነት) እንደ ግርዛት ባሉት ውጫዊ ነገሮች ሳይሆን በክርስቶስ ሞት በማመን ብቻ እንደሚገኝ ስለሚያስረዳው ትምህርቱ ለአይሁድ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች አብራርቷል። እነዚህ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ጳውሎስ ልዩ የአሕዛብ ሐዋርያ መሆኑን ተገንዝበው እውቅና ሰጡት። ለመልእክቱ እውቅና በመስጠት ቲቶን እንዲገረዝ ሳያስገድዱ ቀሩ። የጠየቁት ነገር ቢኖር እምነታቸውን በሥራ ላይ የማያውሉትን እነዚህን ክርስቲያኖች ለችግረኞች በመስጠት ከእግዚአብሔር ጋር ያላቸውን ግንኙነት እንዲያሳዩ ጳውሎስ እንዲያስተምራቸው ነበር። ስለሆነም፥ ጳውሎስ ወደ ገላትያ አብያተ ክርስቲያናት ሄዶ ወንጌሉን በሰበከ ጊዜ የቤተ ክርስቲያን መሪዎችና የኢየሩሳሌም ሐዋርያት የከለከሉትን ትምህርት አልነበረም ያስተማረው። ነገር ግን መሪዎቹና ሐዋርያቱ አሕዛብ ሳይገረዙ ወይም ብሉይ ኪዳንን ሳይጠብቁ በእምነት ሊድኑ እንደሚችሉ የሚያስረጻውን ትምህርት አጽድቀው ነበር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version