Site icon

አንድ መሪ ምእመናን የጸሎት ሰዎች እንዲሆኑ ያስተምራል (1ኛ ጢሞ.2፡1-8)

የቤተ ክርስቲያን መሪ ለራሱ ሕይወት ብቻ ሳይሆን፥ የጠቅላላዋን ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቶች ለማሳደግ ከእግዚአብሔር ዘንድ ኃላፊነትን የተቀበለ ሰው ነው። ጳውሎስ እግዚአብሔርን የሚፈራ የቤተ ክርስቲያን መሪ በጥንቃቄ ሊያከናውናቸው የሚገባውን አንዳንድ የአገልግሎት ክፍሎች ጠቃቅሷል። ይህም የክርስቶስ አካል እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድና በማኅበረሰብ ውስጥም መልካም ምስክርነትን በሚያንጸባርቅ መልኩ እንድትንቀሳቀስ ያስችላል። ጳውሎስ ብዙ ነገሮችን ማካተት ቢችልም፥ በሚከተሉት ነጥቦች ላይ ብቻ ያተኩራል።

የእግዚአብሔር ሕዝብ የሚጸልይ ሕዝብ ሊሆን ይገባል። ጸሎት ለተቀደሰ አኗኗር ኃይልን ይሰጣል። ጸሎት በሆነ ምሥጢራዊ መንገድ የእግዚአብሔር ኃይል በቤተ ክርስቲያንና በማኅበረሰባችን ውስጥ እንዲሠራ ያንቀሳቅሰዋል። ጳውሎስ በተጨማሪም የክርስቲያኖች የጸሎት አመለካከት ወይም ባህሪ ወሳኝ እንደሆነ ይናገራል። ይህም የጸሎት አመለካከት አማኞች በሚጠይቁት ነገር ውስጥ የሚታይ ነው። እንደ ብዙዎቻችን የኤፌሶን ክርስቲያኖች የራስ ወዳድነት ጸሎቶችን ይጸልዩ እንደነበር አይጠረጠርም። «ጌታ ሆይ፥ ባርከኝ»፥ «ጌታ ሆይ፥ ቤተ ክርስቲያናችንን ባርክ» የሚለው ነበር የዘወትር ጸሎታቸው ጳውሎስ ክርስቲያኖች ከቤተ ክርስቲያኖች ውጪ ላሉት ዓለማውያንና ለሌሎች ክርስቲያኖችም መጸለይ እንዳለባቸው ለጢሞቴዎስ አስረድቷል። ክርስቲያኖች ለመንግሥት መሪዎችም መጸለይ አለባቸው። እንደ ዛሬዎቹ የመንግሥት መሪዎች ሁሉ በጳውሎስ ዘመን የነበሩት ባለሥልጣናትም ስደትን በክርስቲያኖች ላይ ያመጡ ነበር። ጳውሎስ ይህን መልእክት የጻፈው ለሁለት ዓመታት በሮም እስር ቤት ውስጥ ቆይቶ እንደተፈታ ነበር። ከጥቂት ጊዜያት በኋላ ደግሞ ተመልሶ ይታሠርና በሮማውያን ይገደል ነበር። ይሁን እንጂ ጳውሎስ ክርስቲያኖች የመንግሥት ባለሥልጣናትን እንደ ጠላት በመቁጠር እንዳይጠሏቸው መክሯል። አሳዳጆችም ቢሆኑ ይህን ማድረጉ ተገቢ አልነበረም። ለምን? ሁለት ጉልህ ምክንያቶች ሊጠቀሱ ይችላሉ። የመጀመሪያው፥ መንግሥት መሪዎች በማኅበረሰብ ውስጥ መረጋጋትን ለማምጣት እግዚአብሔር የሚጠቀምባቸው መሠረታዊ መሣሪያዎች ናቸው። የመረጋጋት መኖር ደግሞ ክርስቲያኖች ፈሪሃ እግዚአብሔርን የተላበሰ የቅድስና ሕይወት እንዲኖሩ ይረዳቸዋል። ሁለተኛ፥ የተረጋጋ መንግሥት በሚኖርበት ጊዜ ወንጌል በቀላሉ ሊስፋፋ ይችላል። እግዚአብሔር ሰዎች ሁሉ የክርስቶስን ወንጌል ሰምተው እንዲድኑ ይፈልጋል፡፡ ልጆቹም ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔርና በሰው መካከል ብቸኛው አማላጅ እንደሆነ እንዲናገሩ ይፈልጋል። ከሌሎች ሃይማኖቶች የሚመጣ ምንም ዓይነት ተስፋ ሊኖር አይችልም። ይህም ማለት እያንዳንዱ ቤተ ክርስቲያን ለሰዎች ሁሉ ወንጌልን የምትሰብክበት መንገድ እንዲከፈትላት መጸለይ አለባት ማለት ነው። እግዚአብሔር ጸሎታችንን የሚመልስበት ዋናው መንገድ ደግሞ እንደ ጳውሎስ ያሉትን ሰዎች በመጥራትና መልካሙን የምስራች ላልዳኑት ሰዎች እንዲያውጁ በመላክ ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የቤተ ክርስቲያንህን ተለምዷዊ ጸሎቶች አጢን። እነዚህ ጸሎቶች በቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ ናቸው? ወይስ ከቤተ ክርስቲያን ውጪ ያሉትንና የመንግሥት ባለሥልጣናትን የሚያካትቱ ናቸው? ለ) ቤተ ክርስቲያንህ ለመንግሥት ባለሥልጣናት የምትጸልየው ምን ያህል ነው? ሐ) ቤተ ክርስቲያንህ በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገኙና ወንጌልን ላልሰሙ የተለያዩ የሕዝብ ቡድኖች (ለምሳሌ፥ ለሙስሊሞች፥ ለዘላኖች፥ ወዘተ…) የምትጸልየው ምን ያህል ነው? መ) ይህ ስለ ጸሎት የተሰጠው ትምህርት ቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ ተቀባይነትን እንዲያገኝ ምን ልታደርግ ትችላለህ?

ጳውሎስ አማኞች ከተቀደሰ ሕይወት የመነጨ ጸሎት እንዲያቀርቡ ያሳስባቸዋል። ዋናው ነገር በጸሎታችን ውስጥ የምንጠቀምባቸው ቃላት፥ ድምፃችንን ምን ያህል ከፍ ማድረጋችን ወይም በክርስቶስ ስም እያልን መደጋገማችን ላይሆን፥ ንጹሐን መሆናችን ነው። ጳውሎስ በምንጸልይበት ጊዜ እጆቻችን ንጹሐን ሊሆኑ እንደሚገባ ይናገራል። (አይሁዶች ብዙውን ጊዜ በሚጸልዩበት ወቅት እጆቻቸውን ወደ ሰማይ ያነሱ ነበር።) በሚጸልይ ሰው ሕይወት ውስጥም ሆነ በአማኞች መካከል ንስሐ ያልተገባ ኃጢአት፥ ክፍፍል፥ ቁጣና ክርክር ሊኖር አይገባም። እነዚህ ነገሮች የጸሎትን ውጤታማነት ይቀንሳሉና።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version