የቤተ ክርስቲያን መሪ፣ ሴቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ምሳሌያዊ ሕይወት እንዲኖሩ መርዳት አለበት (1ኛ ጢሞ. 2፡9-15)

ክርስቶስን መከተል ጸሎታችንን ብቻ ሳይሆን የዕለት ዕለት አኗኗራችንንም ጭምር ይቀይራል። ከእነዚህም መካከል አለባበሳችንና አኳኋናችን ሁለቱ ናቸው። እነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባቦች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙ ክርክር አስነሥተዋል። አንዳንድ አማኞች ጳውሎስ ይህንን ምንባብ የጻፈው በመጀመሪያው ምእተ ዓመት ውስጥ ከነበረችው ቤተ ክርስቲያን አማኞች የተወሰኑት ችግሮች እንደሆነና በተለይም በሴቶች አገልግሎት ላይ የተጣለው እገዳ ከዘመናችን ጋር ቀጥተኛ ተዛማጅነት እንደማይኖረው ይናገራሉ። ሌሎች አማኞች ደግሞ እነዚህ የሴቶችን ሚና የሚመለከቱ ምንባቦች በሁሉም ዘመን በሚኖሩ ክርስቲያኖች ሴቶች ላይ ተፈጻሚነት እንደሚኖራቸው ይናገራሉ። እውነቱ እንግዲህ በእነዚህ ሁለት አክራሪ ጫፎች መካከል እንደሚገኝ ግልጽ ነው።

ይህንን ምንባብ በአዲስ ኪዳን ውስጥ ካሉት ሌሎች ምንባቦች ጋር አዛምዶ መመልከቱ ጠቃሚ ነው። ለምሳሌ ያህል ጳውሎስ በሌላ ስፍራ ሴቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሊጸልዩና ትንቢት ሊናገሩ እንደሚችሉ ይናገራል (1ኛ ቆሮ. 15)፡፡ ስለሆነም ጳውሎስ ሴቶች ሙሉ በሙሉ ዝም እንዲሉና በክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የፍጹም ተገዢነት ስፍራ እንዲኖራቸው እየተናገረ አለመሆኑ ግልጽ ነው። እንዲያውም ጳውሎስ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሴቶችና ወንዶች እኩል መሆናቸውን ያስተምራል (ገላ. 3፡28)፡፡ ስለሆነም እነዚህን ጥቅሶች ብቻ በመውሰድ ሴቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዳያገለግሉ መከላከሉ ተገቢ አይሆንም። በሌላ በኩል፥ ጳውሎስ አዳምንና ሄዋንን የክርክሩ መነሻ መሠረት ማድረጉ እነዚህ እገዳዎች (ወይም የቀረቡት መርሆች) ዓለማቀፋዊና ለሁሉም ዘመን የሚያገለግሉ እንጂ ለጳውሎስ ዘመን ብቻ የታሰቡ እንዳልሆኑ የሚያመለክት ይመስላል።

ጳውሎስ እነዚህን ትእዛዛት የሰጠው ለምን እንደሆነ ማወቁ ይህንን ምንባብ በሚገባ እንድንረዳ ያግዘናል። እነዚህን ትእዛዛት ለመረዳት በኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተከሰቱትን ችግሮች ማወቁ ጠቃሚ ቢሆንም፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ግን ሰፍሮ አንመለከትም። በጳውሎስ ዘመን ሴቶች ምንም ዓይነት መብት አልነበራቸውም። በአመዛኙ የወንዶች ንብረት ተደርገው ይወሰዱ ነበር። አይሁዶች በፈለጉት ጊዜ ሚስቶቻቸውን መፍታት ይችሉ ነበር። አንዳንድ አሕዛብ ሴቶች ቤት ውስጥ እንዲቀመጡና ወደ ውጭ ከወጡም ሁልጊዜም ፊታቸውን እንዲሸፍኑ ያስገድዱ ነበር። በእንዲህ ዓይነቱ ጨቋኝ ማኅበረሰብ ውስጥ ወንጌሉ ሴቶች ከወንዶች ጋር እኩል መሆናቸውን ያስተምር ጀመር። በክርስቶስ አካል ውስጥ ማንም ከማንም አይበልጥም። ምክንያቱ በወንዶችና በሴቶች መካከል ልዩነት የለምና (ገላ. 3፡28)። ሴቶች በክርስቶስ ባመኑ ጊዜ ባገኙት በዚሁ አዲስ ነጻነት ደስ ይሰኙ ጀመር። ይህ ደግሞ ሴቶች አንዳንድ አምልኮን የሚረብሹና የክርስቶስን ስም የሚያሰድቡ አለአግባብ ልምምዶችን እንዲያካሂዱ አደረጋቸው። ይህም ለወንጌሉ እንቅፋት ሆነ። በመሆኑም ጳውሎስ በአያሌ መልእክቶች ውስጥ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሴቶች አገልግሎት ምን መሆን እንዳለበት ግልጽ አድርጎ ያስቀምጣል። ምንባቡን ለመተርጎምና ለማዛመድ አስቸጋሪ ያደረገው በጳውሎስ ጽሑፍ ውስጥ ምን ያህሉ በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ የሚያመለክት እንደነበር ለመለየት አለመቻሉ ነው። በመሆኑም በዘመናት ሁሉ የሚሆነውና ለሁሉም ባህሎች የሚዛመደው ምን ያህሉ እንደሆነ ለማወቅ ያስቸግራል። በ1ኛ ጢሞቴዎስ ውስጥ ጳውሎስ ዛሬ ከሕይወታችን ጋር ልናዛምዳቸው የሚገቡትን አያሌ ጠቃሚ እውነቶች አስተምሯል፡

ሀ) ሴቶች በውጫዊ ውበታቸው ወይም በወንዶች ዘንድ ማራኪነታቸውን በሚጨምሩ ነገሮች ላይ ብቻ ሳይሆን፥ በመንፈሳዊ ውበታቸውም ላይ አጽንኦት መስጠት ይኖርባቸዋል። ጳውሎስ ይህን ሲል ሴቶች ጌጣ ጌጦችን መጠቀማቸውን ወይም ፀጉራቸውን ማሳመራቸውን መቃወሙ አልነበረም፡፡ ይልቁንም ጳውሎስ በሰዎች አመለካከት ላይ ያተኩራል። ሴቶች ውበታቸውን እያዩ ለመኩራራት በማሰብ ጌጣ ጌጦችን፥ የፀጉር አሠራሮችን ወይም ልብሶችን መጠቀማቸው ትክክል አይደለም፡፡ እንዲሁም ደግሞ ሴቶች የወንዶችን ወሲባዊ ስሜት ለመቀስቀስ ጌጣ ጌጦችንና ልብሶችን መጠቀማቸው ተገቢ አይሆንም። ውጫዊ ውበት የእግዚአብሔር ስጦታ ቢሆንም፥ ዋንኛ አስፈላጊ ነገር አይደለም። እግዚአብሔር የሚያየው ልባችንን ነው። እርሱ በአኗኗራችን እንድናስከብረው ይፈልጋል። እግዚአብሔርን የምናስከብረው ደግሞ መንፈሳዊ ባህሪያችንንና እኗኗራችንን በማስተካከል ነው። ሌሎች ሲቸገሩ አይተን በምንረዳቸው ጊዜ እግዚአብሔርን እናከብራለን። ከወንጌሉ ጋር በማይፋታ ወይም ሰዎችን ወደ ኃጢአት በማይገፋ መንገድ በመልበስና በማጋጊያጥ እግዚአብሔርን እናስከብራለን።

ለ) ሴቶች ከወንዶች የበለጠ ሥልጣን ካልያዝን ማለት የለባቸውም፡፡ ጳውሎስ ሰዎች ለአምልኮ በሚሰበሰቡበት ሁኔታ ላይ ያተኩራል። እዚህ ላይ ጳውሎስ የሚናገረው ስለ ሁሉም ሁኔታዎች አይደለም። ለምሳሌ፥ ሴቶች በሥራ ቦታ ላይ የወንዶች አለቆች ሊሆኑ ይችላሉ። አማኞች ይህንን እገዳ የሚረዱት በተለያዩ መንገዶች ነው። አንዳንድ ምሁራን ጳውሎስ ይህንን ክፍል የጻፈው ያልተማሩና ያልሠለጠኑ ሴቶች ከወንዶች ጋር እኩል እንደ መሆናችን መጠን እኛም የማስተማር መብት አለን በማለታቸው ሳይሆን እንዳልቀረ ይናገራሉ። ይህን አቋም የሚያራምዱ ሰዎች ጳውሎስ የሚናገረው ስላልተማሩ ሴቶች ነው ሲሉ ያስረዳሉ። ጳውሎስ ሴቶች እንዲያስተምሩ ያልፈቀደው እንደ ዛሬው ሴቶች ከወንዶች እኩል ወይም በላይ በተማሩበት ሁኔታ ውስጥ ሳይሆን ምንም ትምህርት ያላገኙ ሴቶች በነበሩበት በጥንታዊው ማኅበረሰብ ውስጥ ብቻ እንደሆነ እነዚሁ ምሁራን ያስተምራሉ። ሌሎች ምሁራን ደግሞ ጳውሎስ የሚናገረው ስለ አመራር ሥልጣን እንደሆነ ያስረዳሉ። በመሆኑም ጳውሎስ ሴቶች ከወንዶች በላይ ሆነው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መሾም እንደሌለባቸው ያስተማረ መሆኑን ይናገራሉ። ስለሆነም ሴቶች የልጆች ወይም የሴቶች አስተማሪዎች፥ መጋቢዎችና ሽማግሌዎች ሊሆኑ ቢችሉም፥ የወንዶች ሽማግሌዎች ወይም መጋቢዎች ሊሆኑ እንደማይችሉ ይናገራሉ።

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እግዚአብሔር ሴቶችን ከወንዶች እኩል እንደሚያያቸው እውነት ነው። ነገር ግን እኩልነት ማለት የግድ የሥልጣን መዋቅር አይኖርም ማለት አይደለም። አዲስ ኪዳን እግዚአብሔር በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የአመራርን ሥልጣንና ኃላፊነት ለወንዶች እንደሰጠ ያስተምራል። ጳውሎስ በሌሎች ስፍራዎች እንደሚያስተምረው የተለያዩ የሥልጣን ደረጃዎች አሉ። ይህም በሥላሴ ውስጥ እኩልነትና የተለያየ የሥልጣን ደረጃ እንዳለ በሚያመለክት ምሳሌ ተብራርቷል። እግዚአብሔር አብ ከኢየሱስ ክርስቶስ በላይ ነው። አብና ወልድ ደግሞ ከመንፈስ ቅዱስ በላይ ናቸው (1ኛ ቆሮ. 11፡3)፡፡ (ማስታወሻ፡- እግዚአብሔር ሥልጣንን ለማገልገል እንጂ ሌሎችን በጭካኔ ለመግዛት አለመጠቀሙ፥ ወንዶች በሴቶች ወይም ሽማግሌዎች በቤተ ክርስቲያን ላይ ምን ዓይነት ሥልጣን ሊኖራቸው እንደሚገባ የሚያመለክት ነው። የተሰጣቸው ሥልጣን ሌሎችን የማገልገል እንጂ የመግዛት ወይም የመጨቆን አይደለም።) ጳውሎስ ሴቶች በወንዶች ላይ ሥልጣን ሊኖራቸው አይገባም የሚለውን አሳብ ለማስደገፍ በፍጥረት ውስጥ የታየውን የእግዚአብሔርን ዕቅድ ይጠቅሳል። እግዚአብሔር አዳምን መጀመሪያ ሔዋንን ደግሞ ቀጥሎ መፍጠሩ ወንድ በሴት ላይ ሥልጣን እንዳለው ያሳያል። ሴት ከወንድ ቀድማ በኃጢአት መውደቋ ይህንኑ ያጠናክራል።

ይህ ማለት ሴቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ምንም ዓይነት ሥልጣን እንደማይኖራቸው ወይም ሊያስተምሩ እንደማይችሉ ያሳያልን? ይህ ክፍል ሴቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሥልጣን ስፍራ በመያዝ እንደ ሽማግሌ የምእመናንን መንፈሳዊ ሕይወት መንከባከብ እንደሌለባት የሚያስተምር ይመስላል። እንዲሁም ደግሞ ሴቶች ወንዶች እንዴት ሊመላለሱ እንደሚገባ በሥልጣን ሊያዙ በሚችሉበት የማስተማር አገልግሎት ላይ ሊቀመጡ እንደማይገባ የሚያስተምርም ይመስላል። ነገር ግን ይህ እገዳ ሴቶች በልጆች ወይም በሴቶች ላይ የመሪነት ሥልጣን እንዳይኖራቸው አያስተምርም (ቲቶ 2፡3-4 አንብቡ።) (ለምሳሌ፥ የሰንበት ትምህርት ቤቶች፥ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መሪዎች፥ የሴቶች አገልግሎት ዳይሬክተሮች፥ ወዘተ…) እግዚአብሔር ለሴቶች የትንቢት ስጦታ መስጠቱ (1ኛ ቆሮ. 11፡5 አንብብ።) ሴቶች የእግዚአብሔርን ቃል የማስተማር ስጦታ ሊኖራቸው እንደሚችል ያሳያል። ይህ ግን በቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ሥልጣን ሥር መከናወን አለበት።

ሐ) የሴቶች ቀዳማዊ ሚና መንፈሳዊ እናትነት ነው። ጳውሎስ ሴት በምትወልድበት ጊዜ መንፈሳዊ ደኅንነትን አገኘች የሚል አሳብ እንደማያስተላልፍ ከሌሎቹ የአዲስ ኪዳን ክፍሎች መረዳት ይቻላል። እንደዚያ ከሆነማ መንፈሳዊ ደኅንነት ሴቶች በሥራ የሚያገኙት መሆኑ ነው። ልጅ ያልወለዱ ሴቶችና ወንዶች ደግሞ የመዳን ተስፋ አይኖራቸውም። በአዲስ ኪዳን ውስጥ መንፈሳዊ ደኅንነት ሁልጊዜም በኢየሱስ ክርስቶስ በምናምንበት ጊዜ ከእግዚአብሔር የምንቀበለው ስጦታ መሆኑ ተገልጾአል። ይህን ለመረዳት የሚያስቸግር ጥቅስ ለማብራራት አያሌ አማራጮች ቀርበዋል።

  1. ጳውሎስ በዚህ ስፍራ መዳን የሚለውን ቃል የሚጠቀመው የተሟላን ሕይወት ለማመልከት ነው። እርካታና የተሟላ ሕይወት ሴቶች የወንዶችን ዓይነት ሥራ በመሥራት ወይም ደግሞ የወንዶችን ያህል ሥልጣን በመያዝ እኩል መሆናቸውን በማወጃቸው አይደለም። ነገር ግን እርካታና የተሟላ ሕይወት የሚመጣው አንዲት ሴት እግዚአብሔር ያዘጋጀላትን ዕቅድ ተግባራዊ ስታደርግ ነው። ይህም በቤተሰብ ውስጥ የእናትነት ሚናዋን መጫወት ነው። ይህንን ሚና ተግባራዊ በምታደርግበት ጊዜ በግሪክ ማኅበረሰብ ውስጥ የነበሩት ሴቶች የሚፈጽሙትን ዓይነት ኃጢአት ከመፈጸም ትድናለች።
  2. ጳውሎስ መጀመሪያ በሴቶች ላይ የተጣለውን የመጀመሪያውን እርግማን ይጠቅሳል (ዘፍጥ. 3፡16)። ክርስቲያን መሆን ሴቶች ልጅ በሚወልዱበት ጊዜ የሚሰማቸውን የምጥ ጣር ሥቃይ አያስወግድም። ክርስቶስ እስከሚመለስ ድረስ እርግማኑ ይቀጥላል። ነገር ግን ይህ ማለት ሴቶች ከእግዚአብሔር ፍርድ ድነው መንፈሳዊ ድነትን (ደኅንነትን) አያገኙም ማለት አይደለም። ሴቶች በክርስቶስ በማመን እንደ ወንዶች ሁሉ ድነትን ሊወርሱ ይችላሉ።
  3. ጳውሎላ አጽንኦት የሰጠው ልጅን በመውለድ ላይ ሳይሆን፥ አንዲት የተለየች ሴት በወለደችው ልጅ ላይ ነው። ድነት ወደ ዓለም የመጣው ማርያም የተባለች ሴት በወለደችው ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካኝነት ነው። ማርያም እግዚአብሔር የሰጣትን ኃላፊነት ባትወጣ ኖሮ ሴቶችም ሆኑ ዓለም በሙሉ ደኅንነትን አያገኙም ነበር። ነገር ግን ማርያም የድርሻዋን ስለተወጣች እግዚአብሔር በልጁ በኩል ደኅንነትን ወደ ዓለም አመጣ (ዘፍጥ. 3፡15)።
  4. ጳውሎስ መዳን የሚለውን ቃል የተጠቀመው ሴቶች ልጅ በሚወልዱበት ጊዜ ለሥጋዊ ጉዳት አለመጋለጣቸውን ለማመልከት ነው። ስለሆነም አንዲት ሴት በመንፈሳዊ ሕይወቷ ብቻ ሳይሆን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከወንዶች ጋር ባላት ግንኙነትም እግዚአብሔርን በምታስከብርበት ጊዜ፥ እግዚአብሔር ያቺን ሴት ልጅ በመውለዱ አደገኛ ሂደት ውስጥ ከአደጋ ይጠብቃታል።

የዚህ መጽሐፍ ጸሐፊ እንደሚያስበው፥ የመጀመሪያው ወይም ሁለተኛው አመለካከት ሊሆን የሚችል ይመስላል።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “የቤተ ክርስቲያን መሪ፣ ሴቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ምሳሌያዊ ሕይወት እንዲኖሩ መርዳት አለበት (1ኛ ጢሞ. 2፡9-15)”

Leave a Reply

%d