የ1ኛ ጴጥሮስ መልእክት ዓላማ፣ ባሕሪያት፣ መዋቅር እና አስተዋጽኦ

የ1ኛ ጴጥሮስ መልእክት ዓላማ

የውይይት ጥያቄ፡- 1ኛ ጴጥ. 5፡12 አንብብ። ጴጥሮስ የመልእክቱ ዓላማ ምንድን ነው ይላል?

የ1ኛ ጴጥሮስ መልእክት የተጻፈው ለተለያዩ ዓላማዎች ነበር።

የመጀመሪያው ዓላማ፡ አማኞች ምንም ዓይነት ስደት ወይም መከራ ቢደርስባቸው በእምነታቸው ጸንተው ይቆዩ ዘንድ ለማበረታታት (1ኛ ጴጥ. 1፡6፤ 2፡20፣ 4፡13፥ 19)። በክርስቲያኖች ላይ ስደት እየተጠናከረ መምጣቱን በመመልከቱ፥ ጴጥሮስ አዝማሚያው እየከፋ እንደሚሄድና ብዙ አማኞች ሕይወታቸውን እንደሚያጡ የተገነዘበ ይመስላል። ጴጥሮስ በስደቱ ከመረበሽ ይልቅ ክርስቲያኖች ስደትን የክርስትና ሕይወት አካላቸው አድርገው እንዲቀበሉትና ክርስቶስ እንዳደረገው እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ መከራ መቀበላቸውን መቀበልን እንዲማሩ ያበረታታቸዋል። እንዲያውም ጴጥሮስ እግዚአብሔር ልጆቹ በመንግሥተ ሰማይ ሽልማታቸውን ከመቀበላቸው በፊት በምድር ላይ መከራን እንዲጋፈጡ የሚፈቅድ መሆኑን ይናገራል።

በዘመናችን ከጴጥሮስ የሚቃረን ትምህርት የሚያስተምሩ አንዳንድ አማኞች አሉ። እነዚህ ሰዎች እግዚአብሔር መከራን እንድንቀበል (እንድንደኸይ፥ የምንወዳቸውን ሰዎች እንድናጣ፥ እና እንድንታመም) አይፈልግም ይላሉ። እነዚህ ነገሮች ከሰይጣን የሚመጡ በመሆናቸው፥ ሰይጣንን በመቃወም ልናሸንፋቸው እንደምንችል ያስተምራሉ። ወይም ደግሞ እነዚህ ችግሮች በሕይወታችን ውስጥ ኃጢአት ከመኖሩ የተነሣ የሚመጡ ናቸው ይላሉ። እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ እንደ መሆኑ መጠን ከእነዚህ ጊዜያት ይሰውረናል ብለው ያስተምራሉ። ነገር ግን አብዛኞቹ የቤተ ክርስቲያንና የብሉይ ኪዳን ታሪክ ጸሐፊዎች ይህ እውነት እንዳልሆነ ያስተምራሉ። እግዚአብሔር ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ መከራን እንዲቀበል እንደ ፈቀደ ሁሉ፥ ክርስቲያኖችም መከራን እንዲቀበሉ ይፈቅዳል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔር በኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ ክርስቲያኖች ላይ መከራንና ስደትን ያመጣባቸውን መንገዶች ዘርዝር። ለ) እግዚአብሔር ወደ ሕይወትህ መከራና ስደትን ያመጣው እንዴት ነው። ሐ) በስደትና መከራ ውስጥ ስለ እግዚአብሔርና ክርስትና ሕይወት ምን እንደተማርክ ግለጽ።

ሁለተኛ ዓላማ፡ አማኞች ከምድር ላይ ምቹና የተቃለለ ሕይወት ከመሻት ይልቅ ዓይኖቻቸውን በዘላለማዊ ቤታቸው ላይ እንዲተክሉ ለማበረታታት። ጴጥሮስ አማኞችን መጻተኞች ወይም ወደ ዘላለማዊ የመንግሥተ ሰማይ ቤታቸው እስኪደርሱ ድረስ በምድር ላይ የሚቅበዘበዙ ሰዎች አድርጎ ይገልጻል። ጳውሎስ ሰዎች ፈጥነው እንደሚጠወልግ አበባ መሆናቸውን ይናገራል (1ኛ ጴጥ. 1፡24)። ነገር ግን ክርስቲያኖች ዘላለማዊ የእግዚአብሔር ቃል ዘመን የማይሽረውን የመንግሥተ ሰማይ ርስት ተስፋ እንደሚገባልን መገንዘብ ይኖርብናል (1ኛ ጴጥ. 1፡3-6)።

ሦስተኛ ዓላማ፡ በተወሰኑ ጉዳዮች ላይ ለክርስቲያኖች ምክር ለመስጠት። ዋናው ነገር በሰላም ወደ መንግሥተ ሰማይ መድረስ ብቻ አይደለም። በዚህም ምድራዊ የእምነት ጉዞአችን የምንመላለስበት ሁኔታ ወሳኝ ነው። ስለሆነም ጴጥሮስ፥ ለባሎችና ሚስቶች (1ኛ ጴጥ. 3፡1-7)፥ የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች (1ኛ ጴጥ. 5፡1-4)፥ እንዲሁም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለሚገኙ ወጣቶች (1ኛ ጴጥ. 5፡5) ምክሮችን ይሰጣል። በተለይም ጴጥሮስ ቅድስናና ትሕትና አስፈላጊዎች መሆናቸውን አጽንኦት ሰጥቶ ያስተምራል። ቅድስና እንድ ሰው ከኃጢአት ሕይወት ተመልሶ ለእግዚአብሔር ክብር መኖሩን ያሳያል። ትሕትና በዋናነት አማኞች እርስ በርሳቸው ምን ዓይነት ዝምድና ሊኖራቸው እንደሚገባና በተለይም ለሚያሳድዷቸው ሰዎች መልካም ባህሪ ማሳየት እንዳለባቸው ያሳያል።

የ1ኛ ጴጥሮስ መልእክት ልዩ ባሕርያት

  1. ጴጥሮስ ከክርስቶስ ጋር ከነበረው ግንኙነት የወሰዳቸውን ምሳሌዎች ይጠቀማል። ጴጥሮስ የሚለውን ስም የሰጠው ክርስቶስ ነበር። የስሙም ትርጓሜ ዓለት ማለት ነው። ነገር ግን ይህ ስም የተሰጠው ለእርሱ ብቻ አልነበረም። ክርስቲያኖች ሁሉ እግዚአብሔር እየገነባ ባለው መንፈሳዊ ቤት ውስጥ ሕያዋን ድንጋዮች ናቸው (1ኛ ጴጥ. 2፡5-9)። ክርስቶስ በመጨረሻ አካባቢ ከጴጥሮስ ጋር ሲነጋገር በጎቼን አሠማራ ብሎት ነበር (ዮሐ 21፡15-18)። አሁን ግን ጴጥሮስ የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች የእግዚአብሔርን በጎች ሊንከባከቡ እንደሚገባ ያመለክታል (1ኛ ጴጥ. 2፡25፣ 5፡2፥ 4)።
  2. ከመልእክቱ አጭርነት በተቃራኒ ጴጥሮስ ከብሉይ ኪዳን የወሰዳቸው ምንባቦች በየትኛውም የአዲስ ኪዳን መጽሐፍ ውስጥ ከሚገኙ የብሉይ ኪዳን ጥቅሶች በልጠው ይገኛሉ። ጴጥሮስ የማይለወጥ ዘላለማዊ የእግዚአብሔር ቃል ጠቃሚ በመሆኑ ላይ አጽንኦት ይሰጣል (1ኛ ጴጥ. 1፡23-25)።
  3. ጴጥሮስ ክርስቲያኖች ለተወሰኑ ነገሮች መጠራታቸውን በመግለጽ፥ የክርስትናን ሕይወት ቁልፍ ነገሮች ይዘረዝራል (1ኛ ጴጥ. 1፡15፤ 2፡9፣ 3፡9፤ 5፡10 አንብቡ)። ጴጥሮስ በቅድስና፥ የእግዚአብሔርን ምስጋና ለማወጅ፥ ስደት የሚያመጡብንን ሰዎች ከመርገም ይልቅ ለመባረክ፥ እንዲሁም በሰማይ ወደሚጠብቀን ዘላለማዊ ክብር እስክንገባ ድረስ ለእምነታችን መከራ ለመቀበል የተዘጋጀን እንድንሆን ያብራራል።

የ1ኛ ጴጥሮስ መልእክት መዋቅር

ብዙውን ጊዜ ጳውሎስ መልእክቶችን በሁለት ዐበይት ክፍሎች ይከፍላል። የመጀመሪያው ክፍል በዋናነት ስለ ነገረ መለኮታዊ እውነታችን ሲያስተምር፥ ሁለተኛው ክፍል የክርስቶስ ተከታዮች እንደ መሆናችን እንዴት መመላለስ እንዳለብን የሚያሳዩትን ተግባራዊ እውነቶች ያቀርባል። ጴጥሮስ ግን ሥነ መለኮታዊ እውነቶችን እግዚአብሔርን በሚያስከብርና የአማኞችን እምነት በሚያሳይ መልኩ መመላለስን ከሚያመለክቱ ተግባራዊ አንደምታዎች መካከል ይቀላቅላል።

በሁሉም ምዕራፍ ማለት ይቻላል እንደ ክርስቲያን መከራ የመቀበሉን ጉዳይ ያነሣል። የስደት ጭብጥ ደብዳቤው የተመሠረተበት አቋም ሆኖ እናገኘዋለን።

የ1ኛ ጴጥሮስ መልእክት አስተዋጽኦ

  1. መግቢያ (1ኛ ጴጥ. 1፡1-2)
  2. ድነታችን (ደኅንነታችን) ከመከራ ባሻገር ታላቅ ሽልማቶችን ያስገኛል (1ኛ ጴጥ. 1፡3-12)
  3. ድነት (ደኅንነት) ወደ ተቀደሰ ዓላማ ሊመራን ይችላል (1ኛ ጴጥ. 1፡13-2፡3)።
  4. የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ በመንፈሳዊ ቤተ መቅደሱ ውስጥ ሕያዋን ድንጋዮች ናቸው (1ኛ ጴጥ. 2፡4-12)።
  5. የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ እንዴት ሊመላለስ ይገባል (1ኛ ጴጥ. 2፡13-5፡11)።

ሀ. አማኞች ለመንግሥት መሪዎች መገዛት አለባቸው (1ኛ ጴጥ. 2፡13-17)

ለ. ክርስቲያን ባሪያዎች መከራ ሲደርስባቸውም እንኳን ለሰብአዊ ጌቶቻቸው መገዛት አለባቸው (1ኛ ጴጥ. 2፡18-25)።

ሐ. የእግዚአብሔር ሕዝብ ቤተሰባዊ ግንኙነቶች (1ኛ ጴጥ. 3፡1-7)

  1. ሚስቶች ለባሎቻቸው መገዛት አለባቸው (1ኛ ጴጥ. 3፡1-6)
  2. ባሎች ከሚስቶቻቸው ጋር በማስተዋል መኖር አለባቸው (1ኛ ጴጥ. 3፡7)

መ. የእግዚአብሔር ሰዎች አላግባብ በሚሰደዱበት ጊዜ ሳይቀር ከሰዎች ሁሉ ጋር በሰላም መኖር አለባቸው (1ኛ ጴጥ. 3፡8-22)።

ሠ. አማኞች የተቀደሰ ሕይወት መምራት ይገባቸዋል (1ኛ ጴጥ. 4፡1-6)

ረ. የእግዚአብሔር ሕዝብ ለሌሎች አማኞች ጥልቅ ፍቅር ሊኖራቸው ይገባል (1ኛ ጴጥ. 4፡7-11)።

ሰ. ክርስቲያኖች ስደትን በደስታ መቀበል አለባቸው (1ኛ ጴጥ. 4፡12-19)

ሸ. በእግዚአብሔር ቤተሰብ ውስጥ ሊኖር የሚገባው ግንኙነት (1ኛ ጴጥ. 5፡1-1)

  1. ማጠቃለያ (1ኛ ጴጥ. 5፡12-14)

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

4 thoughts on “የ1ኛ ጴጥሮስ መልእክት ዓላማ፣ ባሕሪያት፣ መዋቅር እና አስተዋጽኦ”

  1. እግዚአብሔር ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ መከራን እንዲቀበል እንደ ፈቀደ ሁሉ፥ ክርስቲያኖችም መከራን እንዲቀበሉ ይፈቅዳል።Be fitsum ewnet aydelem.egzr kiristianoch mekeran endikebelu bifelig eyesusin endezia masekayet baltegebam nebr.
    2, እግዚአብሔር በኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ ክርስቲያኖች ላይ መከራንና ስደትን ያመጣባቸውን መንገዶች ዘርዝር። ለ) እግዚአብሔር ወደ ሕይወትህ መከራና ስደትን ያመጣው እንዴት ነው? egzihabiher aydelem be ethiopia betekiristian wust sidetinina mekaran yametaw. mejemeria sidetina mekera keman endemimetu yones 10;10 bedenb enireda! endhum degmo yaikob 3 ‘ mulun mirafunina specially Bego sitota hulu, fitsumim bereket hulu kelay nachew yemilewn kal be kitu enireda!!

    and ewnet lingerih, egzihabiher enen lijun masekayet kalebet kiristosin lasekayew waga mekfel alebet!! ended!!

  2. Be meceresha, Metsihaf kidusin ke hewotachin antsar metergom akumen, hewotachinin ke mtsihaf kidus antsar endinteregum menfes kidus yirdan!! Amen!!

  3. yezi meder nuro gizeyawi endehone lehyawu tesfa endeteteran bezih mder mesatenoch endemehonachen mekera emnttacnen yasadegal yateral degmom beziya wust yegziyabher hayel na zega yesetenal

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading