አማኝ እምነቱን ተግባራዊ የሚያደርግባቸው መንገዶች (ያዕ. 1፡19-2፡26)

በዚህ ክፍል ውስጥ ያዕቆብ ብዙዎቻችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለንን እምነት በሚያንጸባርቅ መልኩ ለመኖር የተቸገርንባቸውን ጉዳዮች ይዘረዝራል።

፩. እውነተኛ አማኞች ቁጣቸውንና አንደበታቸውን ይቆጣጠራሉ (ያዕ. 1፡19-20)

በአማኞች መካከል የተከሰቱትን አብዛኞቹን ክፍፍሎች ብንመለከት፥ በአብዛኛው የችግሩ መንሥኤ አንደበታችንን አለአግባብ መጠቀማችን መሆኑን እንገነዘባለን። ይህም እንደ እሳት እየተቀጣጠለ ክፍፍሉ እንዲፈጠርና እያደገ እንዲሄድ ያደርጋል። ከያዕቆብ ዐበይት ትምህርቶች አንዱ አንደበታችንን የሚመለከት ነው። ብዙውን ጊዜ ስንቆጣ የተሳሳቱ ነገሮችን እንናገራለን። ወደ ውስጥ አጥልቀን ብንቆፍር በአመዛኙ ቁጣችንን የሚቆሰቁሰው ራስ ወዳድነታችንና ትዕቢታችን ነው። ያዕቆብ ንዴታችንንና አንደበታችንን ለመቆጣጠር እንድንማር ይነግረናል። ብዙውን ጊዜ በጥንቃቄ ሳናስብ የምንናገራቸው ነገሮች ለችግር ስለሚያጋልጡን ትንሽ የመናገርና ብዙ የማድመጥ ክህሎት ልናዳብር ይገባል።

፪. እውነተኛ አማኞች የቃሉን እውነት ተግባራዊ ለማድረግ አኗኗራቸውን ይለውጣሉ (ያዕ. 1፡21-27)

ያዕቆብ እንዴት ልንኖር እንደሚገባ በዝርዝር ማብራሪያዎችን ከሰጠ በኋላ ከትምህርቶቹ ሁሉ በስተጀርባ መሠረታዊ መርሆ ይጠቅሳል። እውነተኛ አማኞች ከሆንን፥ መጽሐፍ ቅዱስን እንደምንወድና ልንታዘዘው እንደምንፈልግ የምንናገር ከሆነ፥ በሕይወታችን ክፍሎች ሁሉ ሕይወታችንን ተግባራዊ ለማድረግ መቁረጥ ይኖርብናል። ዋናው መጽሐፍ ቅዱስ ማንበቡ አይደለም፥ ያነበብነውን መታዘዙ እንጂ፤ ስብከት መስማቱ አስፈላጊ ቢሆንም ዋናው ግን የተሰጠውን ትምህርት ተግባራዊ ማድረጉ ነው። ለብዙዎቻችን ችግሩ የእውቀት ማነስ አይደለም፥ ነገር ግን በምናውቀው መሠረት አንኖርም። መስታወት አይተው እንደሚዘነጉት ሰዎች ነን። መስታወቱን አይተን ጸጉራችንን በማበጠር እንዳላስተካከሉት ሰዎች ነን።

ያዕቆብ በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ የምንመለከተውን ነገር ከሕይወታችን ጋር የማናዛምድባቸውን ነገሮች በምሳሌነት ይዘረዝራል። ሃይማኖተኞች ነን ብንልም፥ አንደበታችንን አንገዛም። የክርስቶስ ተከታዮች ነን ብንልም፥ ለመበለቶችና ለእጓለማውታዎች በመከራ ውስጥ ላሉትም ሰዎች ፍቅርንና ርኅራኄን አናሳይም። የተቀደሰ ሕይወትም አንኖርም። (ማስታወሻ፡ መጽሐፍ ቅዱስን፥ በተለይም የብሉይ ኪዳንን የትንቢት መጻሕፍት በጥንቃቄ ብናነብ እግዚአብሔር ለድሆች፥ ለእጓለማውታዎችና ለመበለቶች ልዩ ርኅራኄ እንዳለው እንረዳለን። ልጆቹ እንደዚህ ያሉትን ድሆች ለመርዳት ግዴለሾች በሚሆኑበት ጊዜ በጣም ይቆጣል። ነገር ግን በዘመናችን፥ ራስ ወዳዶች በመሆናችን እግዚአብሔር የሰጠንን የእኛን ያህል ላልታደሉት ከማካፈል ይልቅ የበለጠ ቁሳዊ ሀብት ለማሰባሰብ እንፈልጋለን።)

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ያዕቆብ እግዚአብሔር የሚቀበለው እውነተኛ ሃይማኖት ምን ዓይነት ነው ይላል? ለ) ያዕቆብ የእውነተኛ አምልኮ እምብርቶች ናቸው ብሎ የሚዘረዝራቸውን ነገሮች እምብዛም የማንጠቅሰው ለምንድን ነው? ሐ) ቤተ ክርስቲያንህ እውነተኛ ሃይማኖትን የምታሳየው እንዴት ነው? መ) እውነተኛውን ሃይማኖት የምታሳይባቸው ተግባራዊ መንገዶች ምን ምን ናቸው?

፫. እውነተኛ አማኞች በሃብታምና በድሃ እማኞች መካከል መድልዎ አይፈጽሙም (ያዕ. 2፡1-13)

እግዚአብሔር ከሚጠላቸው ኃጢአቶች አንዱ አድልዎ ነው። በያዕቆብ ዘመን ይህ የአድልዎ ኃጢአት በሃብታምና ደሃ አይሁዳውያን አማኞች መካከል ይታያል። ሀብታምና ደሃ አማኞች ወደ ቤተ ክርስቲያን በሚመጡበት ጊዜ የሚሆነው ነገር አድልዎ መኖሩን ያሳይ ነበር። ሀብታም አማኞች ከመድረኩ ፊት ያማረ ስፍራ ይሰጣቸዋል። ድሆች ግን ከወለሉ ላይ ወይም ከኋላ እንዲቀመጡ ይደረጋል። ያዕቆብ ይህ በሁለት ምክንያቶች የተሳሳተ አመለካከት መሆኑን ይናገራል።

ሀ) ይህ አማኞች የሚያሳድዷቸውን ሰዎች እንዲያከብሩ ያደርጋል። ብዙውን ጊዜ ስደት የሚመጣው ከድሆች አይደለም። አሳዳጆች ሀብታሞችና ኃይለኞች ናቸው። እነዚህም ነጋዴዎች፥ የሃይማኖት መሪዎችና የፖለቲካ መሪዎች ናቸው። ለሃብታሞች ማዳላቱ ሞኝነት መሆኑን ለማመልክት ያዕቆብ እነዚህ ሰዎች በአብዛኛው አሳዳጆቻችን መሆናቸውን ይናገራል።

ለ) ይህ የእግዚአብሔርን ሕግ ይተላለፋል። ያዕቆብ ከእግዚአብሔር ሕግጋት አንዱን «የንጉሥ ሕግ» ይለዋል። ይህ ሕግ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ወደድ» የሚለው ነው። ሀብታሙን ማክበርና ድሃውን መናቅ ሰዎች ሁሉ፥ ሀብታሙም ድሃውም ባልንጀሮቻችን ስለሆኑ እኩል አክብሮት ይገባቸዋል የሚለውን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መጣስ ይሆናል። ይህን ሕግ በምንተላለፍበት ጊዜ (አድልዎ በማሳየት) ሕግ ተላላፊዎች ሆነናል ማለት ነው። ይህም እንደ አመንዝራነት ወይም ነፍሰ ገዳይነት መሆኑ ነው። ስለሆነም፥ አድልዎ በምንፈጽምበት ጊዜ ሕግን ስለተላለፍን የእግዚአብሔር ፍርድ ይጠብቀናል።

ዛሬ አብያተ ክርስቲያኖቻችን በዚህ ኃጢአት ተበክለዋል። በያዕቆብ ዘመን እንደነበሩት አይሁዶች፥ ሀብታሞችን በማክበር ከቤተ ክርስቲያን የስብከት መድረክ ፊት ለፊት እናስቀምጣቸዋለን። ድሆችን ግን እንንቃቸዋለን። የተማሩትን እያከበርን፥ ያልተማሩትን ግን እንንቃለን። ነጋዴዎችን እያከበርን፥ ባሪያዎችን ወይም ብረት ሠሪዎችን እንንቃቸዋለን። አንዱን ጎሣ ከሌላው እናስበልጣለን። ቤተሰባችንን ስናከብር፥ ቤተሰባችን ያልሆኑትን እንንቃለን። (ለምሳሌ፥ ልጆቻችንን የመዘምራን ቡድን ውስጥ እናስገባለን። ነገር ግን የድሆች ልጆች ብዙም ወደ ኳየሩ እንዲገቡ አይደረግም።) ዝሙት ላንፈጽም ብንችልም፥ ያዕቆብ በእግዚአብሔር ዐይኖች ፊት አድልዎ እንደ ዝሙት የከፋ መሆኑን ይናገራል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ቤተ ክርስቲያንህን ገምግም። ምን ዓይነት አድልዎዎች ታያለህ? ለ) እግዚአብሔር ይህን ሁኔታ እንዴት የሚመለከት ይመስልሃል? ሐ) እግዚአብሔር እነዚህን የተለያዩ ዓይነት ሰዎች እንድናስተናግድ የሚፈልገው እንዴት ይመስልሃል?

፬. እውነተኛ አማኞች የእምነታቸውን እውነተኛነት በተግባራቸው ያሳያሉ (ያዕ. 2፡14–26)

ያዕቆብ አድልዎ የዝሙትን ያህል የከፋ መሆኑን በሚናገርበት ጊዜ አንድ ሰው ክርክር የገጠመው በሚመስል ሁኔታ ይጽፋል። ያ ክርክር የገጠመው ሰው፥ ሰዎች እውነት የሆነውን እስካመኑ ድረስ እግዚአብሔር ደስ ይለዋል ሲል ይናገራል። ሰዎች ኢየሱስ አምላክ እንደሆነና ለኃጢአታቸው እንደ ሞተ ካመኑ፥ እግዚአብሔር ደስ ይለዋል «እግዚአብሔር የሚፈልገው ትክክለኛ እውቀትን ነው። ምንም እንኳን የሚገባኝን ያህል ለድሆች ፍቅር ባላሳይም፥ ይህ በቂ ይሆናል» ሲል ይከራከራል።

ይህ ክፍል ምናልባትም ያዕቆብ አማኞችን ለማስተማር የፈለገው ዐቢይ እውነት ሳይሆን አይቀርም። «መዳናችንን እንዴት እናሳያለን? ይህንን የምናደርገው ትክክለኛ እውነቶችን በማመን ነው? ወይስ የተለወጠ ሕይወት በመኖር?» የያዕቆብ ምላሽ መዳናችንን የምናሳየው በተግባራችን እንጂ በቃላችን አይደለም የሚል ነው። ትክክለኛ ቃላትን ተናግሮ በተለወጠ ሕይወት ራሱን የማይገልጥ እምነት «የሞተ እምነት» ነው። አጋንንት እንኳን እግዚአብሔር እንዳለ በትክክል ያውቃሉ። ትክክለኛ እምነታቸው ግን አያድናቸውም። ምክንያቱም በተግባራቸው ልባቸው እንዳልተለወጠ ያሳያሉ። እምነት ከሥራ ተለይቶ ሊታይ አይችልም። ያዕቆብ እውነተኛ እምነት በሰዎች ተግባራት የተገለጠባቸውን የብሉይ ኪዳን ምሳሌዎች ይገልጻል።

ሀ) አብርሃም፡- አብርሃም በእግዚአብሔር ላይ የነበረውን እምነት የገለጸው ይስሐቅን በመሠዋት ነበር። ለአብርሃም፥ «ከይስሐቅ በላይ እወድሃለሁ። ይስሐቅን ከሞት ልታነሣው እንደምችትል አውቃለሁ» የሚል ቃል ለእግዚአብሔር መናገሩ ብቻ በቂ አይሆንም ነበር። ለእግዚአብሔር ያለውን ፍቅርና እግዚአብሔር ይስሐቅን ከሞት እንደሚያስነሣው ማመኑን ልጁን ወደ ሞሪያ ተራራ ወስዶ በመሠዋት ማሳየት ነበረበት። እምነቱን በተገቢ ተግባራት በተጨባጭ ማሳየት ያስፈልገው ነበር።

ለ) ረአብ፡- በኢያሱ ዘመን ሁለት ሰላዮች ከተማይቱን ለመሰለል ወደ ኢያሪኮ ተልከው ነበር። ጋለሞታ የነበረችው ረአብ እነዚህ ሰዎች እስራኤላውያን ሰላዮች መሆናቸውን ተገነዘበች። ነገር ግን ስለ ታላቁና ኃያሉ አምላካቸው ቀደም ሲል ሰምታ ነበርና በእርሱ አመነች። ይሁንና እምነቷ እውነት መሆኑን እንዴት እናውቃለን? ከተጋረጠባት አደገኛ ሁኔታ ባሻገር፥ ረአብ ሰላዮቹን በቤቷ ውስጥ ደበቀች።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በእግዚአብሔር ማመን አስቸጋሪ ተግባር እንድናከናውን የሚጠይቀን መሆኑን ለማሳየት ከዛሬው ዓለም ሁለት ምሳሌዎችን ጥቀስ። ለ) እምነት እንዳለን በሚያሳይ መልኩ ቀጣይ እርምጃ በማንወስድበት ጊዜ ስለ እምነታችን ምን እናሳያለን?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ ስለዚህ አስደናቂ አገልግሎታቸው እግዚአብሔር ይባርካቸው፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: