Site icon

የክርስቶስ ምጽአት (ራእይ 19:1-21)

፩) በሰማይ ያሉት ለባቢሎን ውድመት የሰጡት ምላሽ (ራእይ 19፡1-10)

በራእይ 18 ዮሐንስ ዓለማውያን ለባቢሎን መደምሰስ የሰጡትን ምላሽ ገልጾል። ለእነርሱ ይህ የሐዘን ጊዜ ነበር። ምክንያቱም የወደዷቸው ነገሮች፥ ኃይልና ክብራቸው ሁሉ ወድሟልና ይህም ቁሳዊ ሀብት የሚያመጣው ነው። በራእይ 19፡1-10 ግን በሰማይ ለባቢሎን መደምሰስ የተሰጠው ምላሽ ተገልጾአል። ዮሐንስ በተለያዩ ሰዎች እግዚአብሔር በባቢሎን ተምሳሌትነት ለተገለጸው የዓለም ላይ ክፋት ፍርዱን ስለገለጸ ደስ ተሰኝተው ያመሰግኑታል።

ሀ) በሰማይ የታዩ እጅግ ብዙ ሕዝብ ቀደም ሲል በራእይ 7፡9-17 የተገለጹት አማኞች ናቸው። በእነዚህ ውስጥ ቀደም ሲል ታላቁ መከራ ተብሎ በሚጠራው የመከራ ጊዜ የሞቱ አማኞች ይገኛሉ። እነዚህ ሰዎች ለእምነታቸው በሰማዕትነት ያለፉ ናቸው። ለሞት አሳልፈው የሰጧቸው ክፉ ሥርዓቶች (ፖለቲካዊ፥ ሃይማኖታዊ፥ ኢኮኖሚያዊ) ሲወድሙ በማየታቸው አማኞቹ ደስ ተሰኝተው እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል። ይህ በተጨማሪም ራሳቸውን በንጽሕና የጠበቁና የዓለም ፍቅር እንዳይቆጣጠራቸው ያደረጉ እውነተኛ አማኞች ሁሉ የሚሰጡት ምላሽ ምልክት ነው። ፍትሕ ሊሰፍን ደስ ይሰኛሉ።

«ሃሌሉያ» የሚለው ቃል ከአይሁድ የአምልኮ ሥርዓት ተወስዶ ሳይተረጉም በአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተቀመጠ ነው። የቃሉ ትርጉም «ጌታ ይመስገን» የሚል ነው። የቀድሞይቱ ቤተ ክርስቲያን ያልተለመደ ደስታ ሲገጥማት ወይም በአምልኮ ጊዜ ይህንን ቃል ትጠቀም ነበር። በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ክርስቲያኖች ይህንን ቃል በተደጋጋሚ ይጠቀማሉ። ይህ ቃል የመንፈሳዊነት ወይም የልዩ ኃይል ምልክት የሆነ ይመስል ደጋግመን እንጠቀምበታለን። ምንም እንኳን ለአማኞች ትርጉሙን ካወቅነው ይህንን ቃል መጠቀሙ መልካም ቢሆንም፥ እነዚህ ቃላት የመንፈሳዊነት ምልክቶች ወይም በጸሎት ጊዜ ልንጠቀምባቸው የሚገቡ ምትሃታዊ ቃላት እንደሆኑ ማሰብ የለብንም። የደስታ ስሜታችን በተፈጥሯዊ መንገድ ሃሌሉያ ወይም እልል በማለት ራሱን ከገለጸ መልካም ነው። ይሁንና፥ ተራ አገላለጽ ተጠቅመው «ጌታ ይመስገን» ለማለት የሚመርጡትን ሌሎች አማኞች መኮነን የለብንም።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንዳንድ ሰዎች በተደጋጋሚ ሃሌሉያ እያሉ የሚጮሁት እንዴት ነው? ለ) ሰዎች ይህንን ቃል የሚጠቀሙት ትርጉሙን ተረድተውና አግባብነትን ጠብቀው ነው ወይስ የበለጠ መንፈሳዊ ወይም ለጸሎታቸው ኃይል እንደሚሰጥ በማሰብ?

ለ) ሃያ አራቱ ሽማግሌዎችና አራቱ እንስሶችም እግዚአብሔርን ላከናወነው ተግባር ያመሰግኑታል።

ሐ) ሁለተኛው እጅግ ብዙ ሕዝብ። ይህ ሕዝብ ምናልባትም በዘመናት ሁሉ ድነትን (ደኅንነትን) ያገኙ ሰዎች ክምችት ሳይሆን አይቀርም። እነርሱም እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል። የደስታቸውም ምንጭ ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ መንገሡ ነው። ከእንግዲህ በሰማያት ያሉ ጠላቶች (ሰይጣን) አገዛዙን አይዋጉም። በምድር ላይም ያሉ ቢሆን አገዛዙን የሚቃወሙ (ለምሳሌ፥ መንግሥታት) ጠላቶች አይኖሩም። በሰማይና በምድር ያለው ነገር ሁሉ ለእግዚአብሔር አገዛዝ በመስገድ ትክክለኛ ሚናቸውን ይጫወታሉ። ይህ ሕዝብ የሚደሰትበት ሌላው ምክንያት ደግሞ የበጉ ሠርግ መቅረቡና ሙሽራይቱም ራሷን ማዘጋጀቷ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ብዙውን ጊዜ በብሉይም ሆነ በአዲስ ኪዳን ውስጥ የነበሩትን የእግዚአብሔርን ሕዝብ ከሙሽራ ጋር ያነጻጽራል (ሆሴዕ 2፡19-20፤ 2ኛ ቆሮ. 11፡2)። አይሁዶች የመሢሑ መንግሥት የሚጀምረው በታላቅ ግብዣ እንደሆነ ያምኑ ነበር (ማቴ. 25፡1-13)። ዮሐንስ ይህንኑ ምሳሌ በዚህ ስፍራ ይጠቀማል። ነገር ግን ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ገና ለክርስቶስ እንደ ታጨች እንጂ እንዳገባችው አልገለጸም። ክርስቶስ በመስቀል ላይ ከሞተበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ጋብቻው አልተፈጸመም። ቤተ ክርስቲያን ለጋብቻ እየተዘጋጀች እንዳለች ሙሽራ ነች። ነገር ግን እግዚአብሔር ባቢሎንን ሲያጠፋና ክርስቶስም መግዛት ሲጀምር፥ በክርስቶስና በቤተ ክርስቲያን መካከል ያለው ግንኙነት ይበልጥ ንጹሕና የጠለቀ ይሆናል። በተምሳሌታዊ መልኩ ክርስቶስ ሙሽራ፥ ቤተ ክርስቲያን ሙሽራይቱ፥ እንዲሁም በመካከላቸው ያለው ግንኙነት እግዚአብሔር እንዳቀደው ንጹሕ ይሆናል። በሕይወታችን ውስጥ የኃጢአት መሰናክል ሳይኖር ክርስቶስን ፊት ለፊት እናየዋለን። ያ የጋብቻ ሥርዓት ጊዜ በምድር ላይ ከተደረጉት ከየትኞቹም የጋብቻ ባህሎች የላቀ ይሆናል።

ዮሐንስ አማኞች ዛሬ ለዚሁ ጋብቻ መዘጋጀት እንዳለባቸው ያስገነዝበናል። ቀጭንና ነጭ የተልባ እግር መልበስ ይኖርብናል። ይህ ተምሳሌት ሁለት ጠቃሚ እውነቶችን ያመለክታል። በመጀመሪያ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመናችን እግዚአብሔር ጻድቃን ናችሁ ብሎናል። ለዚህም ነው ሰዎች የተልባ እግሩን ራሳቸው ያላዘጋጁትና ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበሉት። ሁለተኛ፥ ዮሐንስ ድነንት (ደኅንነትን) እንዳገኙ ሰዎች እንዴት መመላለስ እንዳለብን ያስጠነቅቀናል። በሕይወታችን ውስጥ ካለው ክፋት ሁሉ ተላቅቀን ለእጮኛችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ክብርን የሚያመጡትን ነገሮች ማድረግ ይኖርብናል።

በዮሐንስ ራእይ መጨረሻ አካባቢ ዮሐንስ ሁለት ጊዜ መላእክትን ሊያመልክ ሲሰግድና ዳሩ ግን ይህንኑ እንዳያደርግ ሲከለክል እንመለከታለን (ራእይ 19፡10፤ 22፡8-9)። በቀድሞዎቹ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ከተስፋፉት ሐሰተኛ ትምህርቶች አንዱ መላእክትን ማምለክ ነበር (ቆላ. 2፡18) አንብብ። ይህም ዛሬ በአንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ የሚታይ ሁኔታ ነው። ነገር ግን እግዚአብሔር መላእክት ማን እንደሆኑና መላእክትን ማምለኩ ለምን ትክክለኛ ተግባር እንዳልሆነ እንድንገነዘብ ይፈልጋል። መላእክት በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት ከእኛ የበለጡ አይደሉም። ነገር ግን መላእክት ከእኛ በተለየ መንገድ የተፈጠሩ ፍጥረታት ናቸው። መላእክትም ሆኑ ሰዎች ሁላችንም የእግዚአብሔር አገልጋዮች ነን። እንዲያውም እግዚአብሔር ለመላእክት ከሰጣቸው ዐበይት ተግባራት አንዱ የኢየሱስ ክርስቶስን ምስክርነት የሚጠብቁትን አማኞች እንዲረዱ ነው። ቅዱሳንን ማምለክ አያስፈልግም። ማርያምን ማምለክ አያስፈልግም። አያት ቅድመ አያቶቻችንንም ማምለክ የለብንም። ልናመልከውና ልንሰግድለት የሚገባው እግዚአብሔር ብቻ ናቸው። 

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንዳንድ ክርስቲያኖች ለመላእክት፥ ለቅዱሳን፥ ለአያት ቅድመ እያቶቻቸው፥ ለማርያም፥ ወዘተ… የሚሰግዱት ለምንድን ነው? ለ) እነዚህ ክርስቲያኖች ከእግዚአብሔር ጋር ስላለን ግንኙነት ያልተገነዘቡት ነገር ምንድን ነው? ሐ) እነዚህ ሰዎች ስለ መላእክትና ታላላቅ ክርስቲያኖች የያዙት የተሳሳተ ግንዛቤ ምንድን ነው? 

፪) ባቢሎን የወደመችበትን ሁኔታ የሚያሳይ ገለጻ (ራእይ 19፡11-21)

ራእይ 16:17-18፡24 ባቢሎን በተለያዩ መልኮች እንደ ወደመች ያሳያል። ነገር ግን እነዚህ ራእዮች ክፋት እንዴት ሊጠፋ እንደ ቻለ በግልጽ አያሳዩም። ራእይ 19፡11-21 ክፉ ፖለቲካዊና መንግሥታዊ ሥርዓቶች እንዴት እንደ ወደሙ ያሳየናል። በዚህም ጊዜ ክርስቶስ የበላይ ሆኖ መንገሡን እንመለከታለን። ይህ ክርስቶስ በሚመለስበት ጊዜ በቀጥታ የሚሳተፍበት ተግባር ነው። ዮሐንስ ታላቁ ሰማያዊ ተዋጊ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ ወደ ምድር ሲመጣ ያሳየናል። በዚህ ክፍል ውስጥ የተጠቀሱትን ነገሮች ከዚህ በታች ተመልከት፡-

ሀ) ተዋጊው ክርስቶስ የታመነና እውነተኛ ነው። እርሱ በተከታዮቹ የታመነ ሲሆን፥ በበቀል የገደሏቸውን ሰዎች ይቀጣል። እርሱ የሚናገራቸውን ነገሮች ሁልጊዜም ስለሚፈጽም እውነተኛ ነው። ለሰው ልጆች ስለ ዘላለማዊ ፍርድ የሰጠው ማስጠንቀቂያ ደግሞ ይፈጸማል።

ለ) የእሳት ነበልባል የሆኑት ዓይኖቹ በጽድቅ ቁጣና በፍርድ የተሞሉ ናቸው።

ሐ) ማንም የማያውቀው ስሙ እርሱ ከማንም እንደሚበልጥ፥ ባሕሪውንና እንደ አምላክ ታላቅነቱን መረዳት ከሰዎች አእምሮ በላይ መሆኑን ያሳያል።

መ) ልብሱ በደም ተጨማልቋል። ምንም እንኳ ይህ ክርስቶስ ሰዎችን ለማዳንና በሰይጣን ላይ ለመፍረድ ሥልጣን ያገኘበትን የመስቀል ላይ ሞቱን ሊያመለክት ቢችልም፥ አማኞችን መቅጣቱን በበለጠ የሚያሳይ ይመስላል። ይህም የአንድ ተዋጊ ወታደር ልብሶች በጠላቶቹ ደም እንደሚበላሽ ማለት ነው።

ሠ) የሰማይ ሠራዊት ይከተሉታል። እነዚህ መላእክትና ከሰማይ ወደ ምድር ተከትለውት የሚመጡ አማኞች ናቸው። ከእርሱ ጋር የሚመጡት በውጊያው ለማገዝ ሳይሆን፥ ድሉን አብረውት ለማክበር ነው። ምክንያቱም ወደ ኋላ እንደምንመለከተው ክርስቶስ ጠላቶቹን ሁሉ በአንድ ትእዛዝ ቃል ብቻ ያጠፋቸዋል።

ረ) የጦርነቱ መሣሪያ የክርስቶስ የትእዛዝ ሰይፍ ነው። እርሱ እጅግ የሚበልጥ በመሆኑ ውጊያው በእኩልነት ላይ የተመሠረተ አይደለም። (የኃይል ሚዛኑ አይመጣጠንም)። ክርስቶስ እርሱን ለመውጋት የተሰበሰቡትን ክፉ ገዢዎችም አይፈራም። ጦርነቱ የሚጠናቀቀው በሰይፍ በመጨፋጨፍና የኋላ ኋላም ጠላት ድልን በመንሣቱ ሳይሆን፥ በክርስቶስ ኃይለኛ የትእዛዝ ቃል ነው። የክርስቶስ ኃይል እንዲህ ነው።

ሰ) እርሱ የነገሥታት ንጉሥና የጌቶች ጌታ ነው። ክርስቶስ ሁሉንም ነገሥታትና ጌቶች በሰማይም ሆነ በምድር ይቆጣጠራል። 

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ከእነዚህ ጥቅሶች ስለ አዳኛችን ኃይል ምን እንማራለን? ለ) ይህ ከሰይጣን፥ ከክፋት፥ እንዲሁም በምድር ላይ ካሉት ክፉ ሰዎች ጋር በምናደርገው ጦርነት ውስጥ ማበረታቻን የሚሰጠን እንዴት ነው? 

ዮሐንስ ክርስቶስ ለተለያዩ የሕዝብ ቡድኖች የሰጠውን ትእዛዝ ውጤት ይገልጻል፡-

ሀ) ክርስቶስ በሕይወታቸው ውስጥ እንዲገዛ የማይፈቅዱትን ሰዎች ከመሪዎች እስከ ዝቅተኛ ባሪያዎች፥ ከታላላቆች እስከ ታናናሾች ድረስ በኃያል ትእዛዙ ይገድላቸዋል። ለዚህም ነው አሞራዎች የወደቁትን ሰዎች እንዲበሉ የተጠሩት። ይህ ክፉዎች አካላዊ ሞት እንደሚጠብቃቸውና የመቀበርም ዕድል እንደማያገኙ ያሳያል። ውድመታቸው ከፍጻሜ ይደርስና ለታላቅ ኃፍረት ይጋለጣሉ። ነገር ግን ሲዖል የሚወርዱበት ዘላለማዊ ሞት ገና አልደረሰባቸውም።

ለ) በምድር ላይ እጅግ ኃያላን የሆኑት ሰዎች ማለትም ሐሳዊ መሢሕና ረዳቱ በእሳት ባሕር ውስጥ ይጣላሉ። ይህም የዘላለም ፍርድ ስፍራ ነው። ከኃያሉ ክርስቶስ ጋር ሲነጻጸሩ እነዚህ ታላላቅ መሪዎች ደካማና ኃይል የሌላቸው ናቸው። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version