፩. አዲስ ሰማይና ምድር (ራእይ 21፡1–22፡6)
ስለ መንግሥተ ሰማይና በዚያ ሕይወት ምን እንደሚመስል የበለጠ ብናውቅ ደስ ባለን። ነገር ግን አብዛኛው ነገር ከእኛ የተሰወረ ነው። በዚህ ክፍል ውስጥ መጽሐፍ ቅዱስ መንግሥተ ሰማይ ምን እንደምትመስል በግልጽ ያሳየናል። እግዚአብሔር የተለያዩ ተምሳሌቶችን በመጠቀም የዘላለም ቤታችን ምን ያህል ውብ እንደሆነች እንድንገነዘብና ሕይወታችንን በሚገባ እያዘጋጀን እንድንኖር ያበረታታናል። ዮሐንስ የተለያዩ ምሳሌዎችን በመጠቀም ስለ ዘላለማዊ ቤታችን አንዳንድ ታላላቅ ነገሮችን ይነግረናል፡
ሀ. እግዚአብሔር አዲስ ሰማይና አዲስ ምድርን ይፈጥራል። አሁን ያለ ነው በኃጢአት በተጨማለቀች ምድር ውስጥ ነው። ይሁንና አሁንም ለእኛ ውብ ናት። በኃጢአት ያልተበከሉ አዲስ ሰማይና ምድር ምን ያህል የበለጠ ያምሩ ይሆን!
ለ. እግዚአብሔርና ሰው ከመቼውም በበለጠ ቅርበት ኅብረት ያደርጋሉ። እግዚአብሔር ከሰው ጋር አብሮ ለመኖር ሲል ከሰማይ ወደ ምድር እንደሚመጣ በተምሳሌታዊ ቋንቋ ተገልጾአል። በዚህም እንደ ሃያ አራቱ ሽማግሌዎችና አራቱ እንስሳት እግዚአብሔርን ፊት ለፊት ልናመልከው ስለምንችል፥ የቤተ መቅደስም ሆነ የቤተ ክርስቲያን ሕንጻ አያስፈልግም። ይህቺ እዲሲቱ ኢየሩሳሌም በዚህ ምድር ላይ ውድና ተፈላጊ ከሆኑት ነገሮች ሁሉ በላይ የደመቀች ናት። በመሆኑም በዚህ ምድር ላይ ውድ የሆኑት ነገሮች በዚያ ተራ ነገሮች ይሆናሉ። ጎዳናዎች በወርቅ ይነጠፋሉ። በሮች በከበሩ ማዕድናት ይሠራሉ።
ሐ. ለሐዘን ሊዳርገን የሚችል ምንም ዓይነት ነገር አይኖርም። እግዚአብሔር የጸጸትንና የሐዘንን እንባዎች ከዓይኖቻችንና ከአእምሮአችን በማበስ ለመቼውም እንዳናስታውሳቸው ያደርገናል። ኃጢአት፥ በሽታ፥ ሞት፥ ስደት፥ ማንኛውም ዛሬ ሥቃይን የሚያስከትልብን ነገር በዚያ አይኖርም።
መ. በእግዚአብሔር ላይ የሚያምጹ ሰዎች በዚያ አይኖሩም። ዮሐንስ ከእግዚአብሔር ዘላለማዊ ቤት ውጭ ያደርጉናል ብሎ የዘረዘራቸው ኃጢአቶች በዮሐንስ ዘመን የነበሩ ክርስቲያኖች ስደትን ለመሸሽ የሚፈተኑባቸው መሆናቸው አስገራሚ ነው። ለእምነታቸው ጸንተው ለመቆም ያልቻሉ ፈሪዎች፥ የከርስቶስን መሢሕነት ያልተቀበሉና ከእምነት የራቁ፥ የጠላትን ሐሰተኛ አምልኮ የተቀላቀሉ፥ እንዲሁም ወሲባዊ ኃጢአቶችን የፈጸሙና የጎደፉ ሰዎች ለቅጣት እንደሚጋለጡ ተገልጾአል።
ሠ. የክፋት ጨለማ ይወገድና የእግዚአብሔር ዘላለማዊ የመገኘቱ ብርሃን በሕዝቡ ላይ ያበራል።
ረ. ከተማይቱ ከማንኛውም አስጊ ነገር የጸዳች በመሆኗ በሮቿ አይዘጉም። ሌቦች ይመጡብናል ብሎ በር መዝጋቱ ያበቃል።
ሰ. ለእግዚአብሔር ንጹሕ አምልኮ ስለሚቀርብ በዘላለማዊ መንግሥት ውስጥ ያለ ሰው ሁሉ እግዚአብሔርን ለማምለክ ይመጣል። በኦሮጌዎቹ ሰማይና ምድር እንደነበረው ዐመፃ አይታሰብም።
ሸ. ከእግዚአብሔር አብና ወልድ በአዲሲቱ ኢየሩሳሌም ለሚኖሩ አማኞች በረከቶች እንደማያቋርጥ የወንዝ ውኃ ይፈሱላቸዋል። እንዲሁም ከቶውንም የማይወድቅና እንደማይጠወልግ የሕይወት ዛፍ (ፈዋሽ ቅጠሎች ያሉት) የማያቋርጥ፥ ፈውስ ይመጣላቸዋል። ይህ ከበሽታ መፈወስን ሳይሆን፥ አሮጌዎቹ ሰማይና ምድር በሰዎች ላይ ዐመፀኛነቱን ከቀሰቀሱት ክፉ ነገሮች መፈወስን የሚያሳይ ነው።
ቀ. የእግዚአብሔር ቤተሰብ ለዘላለም ከእግዚአብሔር አብና ወልድ ጋር ይነግሣሉ።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እነዚህ እስጨናቂ የእግዚአብሔር የተስፋ ቃሎች መንግሥተ ሰማይን እንድትናፍቅ የሚያደርጉህ እንዴት ነው? ለ) እነዚህ የተስፋ ቃሎች ዛሬ ለኢየሱስ ክርስቶስ ታማኞች እንድንሆን የሚያበረታቱን እንዴት ነው?
፪. የክርስቶስ ዳግም ምጽአት ተስፋ (ራእይ 22፡7-21)
የዮሐንስ ራእይ የመጽሐፉ መሠረት በሆኑት እውነቶች ይጠናቀቃል። በመጀመሪያ፥ ክርስቶስ በቶሎ እንደሚመለስ ለተከታዮቹ ያስገነዝባቸዋል (ራእይ 22፡7፥ 12)። ስለሆነም፥ ዳግም ምጽአቱን በናፍቆት መጠባበቅ ይኖርብናል። ዮሐንስ፥ መንፈስ ቅዱስና ሙሽራይቱ (ቤተ ክርስቲያን) ዳግም ምጽአቱን በመናፈቅ «ጌታ ኢየሱስ ሆይ፥ ቶሎ ና» ሲሉ ይጸልያሉ። ማናችንም ክርስቶስ መቼ እንደሚመለስ አናውቅም። እስከ ዛሬ ሁለት ሺህ ዓመታት ቢቆጠሩም፥ ጌታ ገና አልተመለሰም። ነገር ግን ለእግዚአብሔር «በቶሎ» ማለት እኛ የምናስበው ዓይነቱ ቶሎ ላይሆን ይችላል። (2ኛ ጴጥ. 3፡8 አንብብ)። ነገር ግን እያንዳንዱ የአማኞች ትውልድ የክርስቶስን ምጽአት ሊጠባበቅና በቶሎ እንደሚደርስ ተስፋ ሊያደርግ ይገባል።
ሁለተኛ፥ ክርስቶስ ተከታዮቹ አኗኗራቸውን ከዳግም ምጽአቱ እውነታ አንጻር እንዲያስተካክሉ ያስጠነቅቃል። የዮሐንስ ራእይ የተሰጠው ወደፊት የሚሆነውን ብቻ ሳይሆን፥ በመጽሐፉ ውስጥ የተገለጹትን የትንቢት ቃሎች እንድንጠብቅ ጭምር ነው። እነዚህ በሕይወታችን ውስጥ ተግባራዊ ልናደርጋቸው የሚገቡ እውነቶች ናቸው። የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮች ልብሳችንን አጥበን ማንጻታችንን ማረጋገጥ አለብን። ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ ማመናችንን የሚያመለክት ነው። እንዲሁም እምነታችንን ባለመደበቅ ወይም ባለመካድ፥ ሐሰተኛ አምልኮን ባለመከተልና የዓለማውያንን የተሳሳቱ ልምምዶች ተግባራዊ ባለማድረግ በቅድስና ልንመላለስ ይገባል። እነዚህ ዓለማውያን የእግዚአብሔር በረከቶች ተካፋይ እንደማይሆኑ ግልጽ ነው።
ሦስተኛ፥ ለማያምኑ ሰዎች የተሰጠ መልእክት። ክርስቶስ እስከሚመለስና ፍርድ እስከሚጀምር ድረስ እግዚአብሔር መንፈሳዊ ጥማት ላደረባቸው ሰዎች ድነትን (ደኅንነትን) ይሰጣቸዋል። የዘላለም ሕይወት ውኃ ነፃ ነው። ይህን ለማግኘት ሰዎች ዋጋ መክፈል አያስፈልጋቸውም። አንድ ሰው ሊያደርግ የሚገባው ነገር ቢኖር ወደ ክርስቶስ ተመልሶ በእርሱ ማመን ነው። ነገር ግን በእግዚአብሔር ላይ ባላቸው ዐመፀኛነት ቢቀጥሉ፥ በዮሐንስ ራእይ ውስጥ ለተጠቀሱት መቅሰፍቶች ፍርድ ይጋለጣሉ።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እነዚህ ሦስት መልእክቶች እግዚአብሔር የሰጠን እጅግ ጠቃሚ መልእክቶች የሚሆኑት ለምንድን ነው? ለ) ቤተ ክርስቲያንህ እነዚህን ሦስት መልእክቶች ለአማኞችና ለማያምኑ ሰዎች እያደረሰች ያለችው እንዴት ነው? ሐ) ከዮሐንስ ራእይ ያገኘሃቸው ሌሎች ጠቃሚ ትምህርቶች ምን ምንድን ናቸው?
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)