የክርስቶስ የሺህ ዓመት ንግሥና (ራእይ 20፡1-15)

፩. የክርስቶስ የአንድ ሺህ ዓመት ንግሥና (ራእይ 20፡1-6)

ከክርስቶስ ጠላቶች መደምሰስ በኋላ የዮሐንስ ራእይ ስለ ዘላለማዊ መንግሥት አጀማመር ይነግረናል ብለን እንጠብቃለን። ነገር ግን በመጽሐፉ ውስጥ የምናገኘው ክርስቶስ ለአንድ ሺህ ዓመታት በምድር ላይ እንደሚነግሥ የሚያስረዳውን ክፍል ነው። የዮሐንስ ራእይ በተምሳሌቶች የተሞላ መጽሐፍ በመሆኑ፥ ብዙ አማኞች የሺህ ዓመቱ መንግሥት ክርስቶስ በምድር ላይ በአማኞች ልብ ውስጥ፥ በሰማይ ደግሞ በቅዱሳን ሕይወት መንገሡን የሚያመለክት ነው ይላሉ። ነገር ግን ይህ ክፍል መሢሑ ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ለአንድ ሺህ ዓመታት በቀጥታ የሚነግሥ መሆኑን የሚያሳይ ይመስላል።

እግዚአብሔር የዘላለምን መንግሥት ከመጀመሩ በፊት ለሺህ ዓመታት በምድር ላይ ለመግዛት የፈለገበትን ምክንያት አናውቅም። ነገር ግን ሁለት ሊሆኑ የሚችሉ ምክንያቶች አሉ። በመጀመሪያ፥ በብሉይ ኪዳን ነቢያት የተነገሩና እንደ ዳዊት ካሉ ሰዎች ጋር የተደረጉ አብዛኞቹ ቃል ኪዳኖች ክርስቶስ በምድር ላይ የሚነግሥ መሆኑን ያሳይሉ። ስለሆነም፥ እግዚአብሔር በተለይ ለአይሁዶችና በአጠቃላይ ለሰዎች ሁሉ እነዚህን የተስፋ ቃሎች ለማሟላት የክርስቶስን የምድር ላይ መንግሥት ይመሠርታል። ሁለተኛ፥ እግዚአብሔር የሰዎችን ልብ ክፋት ለማሳየት ይፈልጋል። ብዙውን ጊዜ ሰዎች ክፋትን የሚማሩት ከእነርሱ ውጭ የሆነ ነገር ወደ ከፋት ስለሚመራቸው ነው ብለን እናስባለን። ሰዎች ከወላጆቻቸው፥ ከባህላቸው፥ ወዘተ… ክፋትን ይማራሉ ብለን እናስባለን። ነገሮች ሁሉ መልካም ቢሆኑ፥ በምድር ላይ እውነተኛ ፍቅር ቢኖር፥ ሰዎች ሁሉ ቢማሩ፥ ሰዎች እግዚአብሔርን በማክበር በትክክለኛው መንገድ ይኖራሉ ብለን እናስባለን። ይህ ግን እውነት አይደለም። የሰው ልብ ክፉ ስለሆነ ሁልጊዜም የእግዚአብሔርን አገዛዝ ይቃወማል (ኤር. 17፡9)። ይህም በዚህ ክፍል ውስጥ በግልጽ ተመልክቷል። ምንም ዓይነት ባህላዊ፥ ወላጃዊ ወይም ማኅበራዊ ክፋቶች ለማማሃኛነት ሊጠቀሱ በማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ (ክርስቶስ በጽድቅ ነግሦ ሳለ) ሰዎች አሁንም በእግዚአብሔር ላይ ያምጻሉ። ምናልባትም ታላቁን መከራ ካለፉት ክርስቲያኖች የተወለዱ ልጆች ከዚሁ የክርስቶስ የሺህ ዓመታት መንግሥት ፍጻሜ ላይ ማመጽ ይጀምራሉ። ወዲያውኑ ሰይጣን እንደ ተፈታ ከእርሱ ጋር በመተባበር ከእግዚአብሔር ጋር ይዋጋሉ። የሰው ልጅ ምንኛ ክፉ ነው! 

የውይይት ጥያቄ፡- የእግዚአብሔር ልጅ ብትሆንም እንኳን የልብህን ክፋት እንዴት እንደተመለከትህ ግለጽ። ይህ ስለ እግዚአብሔር ምሕረት ታላቅነት ምን ያስተምረናል?

ዮሐንስ የተለያዩ ቡድኖችንና ክርስቶስ በምድር ላይ ለመግዛት ከሰማይ በሚመለስበት ጊዜ በእነርሱ ላይ ስለሚሆኑት ነገሮች ያብራራል።

ሀ) ሰይጣንና ተከታዮቹ አጋንንት ሺህ ዓመታት ወደ ጥልቁ ወርደው ይታሰራሉ። ይህም ጥልቁ ጉድጓድ ክፉ መናፍስት የሚታሰሩበት ነው። በዚያም በእስር ቤት ሰዎች ኃጢአትን እንዲሠሩና በመሢሃቸው ላይ እንዲያምጹ ሊያደርጉ አይችሉም።

ለ) የተሠዉ አማኞችና በዘመናት ሁሉ የኖሩ ክርስቲያኖች ከሞት ተነሥተው የትንሣኤን አካል ይለብሳሉ። በታላቁ መከራ ጊዜ ያልሞቱና በሕይወት ያሉ አማኞችም ተለውጠው ከእነዚሁ ክርስቲያኖች ጋር ይሆናሉ (1ኛ ቆሮ. 15፡51-54)። አማኞቹ በእግዚአብሔር ተከብረው ከክርስቶስ ጋር በምድር ላይ ይነግሣሉ። (ማስታወሻ፡ በዮሐንስ ራእይ ውስጥ ሁሉ ዮሐንስ በሰማዕትነት ባለፉት አማኞች ላይ አጭር ማስታወሻ ይሰጣል። ይህንንም ያደረገው አማኞች በቆራጥነት ስደትን እንዲጋፈጡና ያለ ፍርሃት ለእምነታቸው እንዲሞቱ ለማበረታታት ነው። መከራን የሚቀበሉ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር እንደሚያከብራቸው ማስታወስ ይኖርባቸዋል። ምንም እንኳ ለጊዜው ክፉ ሰዎች ሁኔታዎችን በመቆጣጠር ላይ ቢሆኑም፥ እነዚህ መከራን የተቀበሉ አማኞች የሚነግሡበት ቀን ይመጣል። ከሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በግልጽ እንደሚታየው፥ አማኞች ሁሉ ከሞት ተነሥተው ከክርስቶስ ጋር ይነግሣሉ (1ኛ ተሰ. 4፡13-18፤ 2ኛ ጢሞ. 2፡12፥ ራእይ 5፡9-10)። ከክርስቶስ ትምህርት እንደምንመለከተው፥ በዚህ ምድራዊ ንግሥና እያንዳንዱ አማኝ የሚኖረው ሥልጣን አሁን እርሱን በምናገለግልበት ጊዜ ባለን ታማኝነት ላይ ይመሠረታል (ማቴ. 25፡14-30)። ዮሐንስ የአማኞችን ትንሣኤ የመጀመሪያው ትንሣኤ ሲል ይጠራዋል። ወደ ሲዖል መውረድን ደግሞ ሁለተኛው ሞት ሲል ይጠራዋል። ክርስቶስን በታማኝነት የሚከተሉ ሰዎች የዚህ የመጀመሪያው ትንሣኤ አካል ከመሆናቸው በተጨማሪ፥ በሁለተኛው ሞት ወደ ሲዖል እንደማይወርዱም ተገልጾአል።

ሐ) በሁሉም ዘመን የሞቱ ሰዎች ገና ከሞት አይነሡም።

፪. የሰይጣን መፈታትና የሰው ልጆች ዐመፅ (ራእይ 20፡7-15)

ሁላችንም የአዳምንና የሔዋንን ታሪክ እናውቃለን። በምርጥ ስፍራ ሲኖሩ ሳለ ሰይጣን በፈተናቸው ጊዜ ለማመጽ መርጠዋል። እኛ ግን ክርስቶስ በመካከላችን ቢኖር እንዲህ ዓይነት ኃጢአት እንፈጽምም ብለን ልናስብ እንችላለን። ይሁንና ኃጢአት መፈጸማችን የማይቀር ነው። ዮሐንስ የሰው ልጅ እንዴት ሁልጊዜም በእግዚአብሔር ላይ እንደሚያምጽ ያሳያል። ሰይጣን ከእስራቱ ከተፈታ በኋላ በቀላሉ የዓለም ሰዎች እንዲያምጹ ያደርጋል። እነዚህ ሰዎች ለሕይወት የሚያስፈልጉ ቁሳዊ በረከቶች ሁሉ በተሟሉባት የክርስቶስ የጽድቅ መንግሥት ውስጥ ይኖሩ ነበር። ይሁንና አሁንም ሰይጣንን ለመከተል መረጡ። ክርስቶስ የንግሥናው መዲና አድርጎ ወደ መረጣት ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ እየገሰገሰ ሳለ ክርስቶስ በራእይ 19 ጠላቶቹን እንዳሸነፈ ሁሉ በቀላሉ ያሸንፋቸዋል። የሚገርመው እነዚህ ሰዎች ከአንድ ሺህ ዓመታት በፊት ከተገለጸው የክርስቶስ ኃይል አለመማራቸው ነው። ዮሐንስ የዘላለም መንግሥት ከመጀመሩ በፊት ለእነዚህ የተለያዩ ቡድኖች ስለሚሆነው ሁኔታ ይገልጻል፡

ሀ) ሰይጣን ወደ እሳት ባህር ይወረወራል። እዚያም ለዘላለም ስለሚታሰር ከእንግዲህ ሰዎች በእግዚአብሔር ላይ እንዲያምጹ የሚያደርግበትን ዕድል አያገኝም። ይህ የእሳት ባህር ወይም ሲዖል የእግዚአብሔር ጠላቶች ለዘላለም የሚቀጡበት ስፍራ ነው። ለሲዖል በመጽሐፍ ቅዱስ ከምንመለከታቸው ነገሮች ምን ያህሎቹ ተምሳሌታዊ ምን ያህሎቹ ደግሞ ቀጥተኛ እንደሆኑ እናውቅም። ነገር ግን አራት ነገሮችን እናውቃለን። 1. ሲዖል ለዘላለም የሚቀጥል ነው። ይህ ሰዎች ከኃጢአታቸው ጸድተው የሚወጡበት የመቆያ (ፐርጋቶሪ) ስፍራ አይደለም። 2. ሰዎች ወደ ምንምነት ወይም አዕምሮአቸውን ወደማያውቁበት ሁኔታ ውስጥ አይሆኑም። ሕይወት ያላቸውና ያሉበትን ሁኔታ የሚያውቁ ይሆናሉ። 3. ይህ ጥልቅ ሥቃይና መከራ የሚበዛበት ስፍራ ነው። እዛ ያሉት ሁሉ በጣም ይሠቃያሉ። 4. ሲዖል ምንም ዓይነት የእግዚአብሔር በረከት የሌለበት ስፍራ ነው። ከእግዚአብሔር ምሕረትና ፍቅር ደስታ የሚያመልጡልን ነገሮች ሁሉ በዚያ አይኖሩም።

ለ) ሙታን ከሞት ተነሥተው በታላቁ ነጭ ዙፋን ፊት ይቆማሉ። ምሁራን እነዚህ እነማን ናቸው በሚለው ጉዳይ ላይ ይከራከራሉ። የክርስቶስ የፍርድ ወንበርና ታላቁ ነጭ ዙፋን አንድ ናቸው ወይስ የተለያዩ? አንድ ከሆኑ፥ ይህ ታላቁ የነጭ ዙፋን ፍርድ ለአማኞችም ለማያምኑ ሰዎችም መሆኑ ነው። የተለያዩ ከሆኑ፥ ይህ ፍርድ የሚሰጠው ለማያምኑ ሰዎች ብቻ ይሆናል። በራእይ 20፡5 የተገለጸው ትንሣኤ (ሌሎች የአዲስ ኪዳን ክፍሎች የሚጠቅሱት) አማኞችን ሁሉ የሚያካትት ከሆነ፥ ሌሎችም የአዲስ ኪዳን ክፍሎች እንደሚጠቁሙን በነጭ ዙፋን ፊት የቆሙት ቀደም ሲል ለሕይወት ያልተነሡ ዓለማውያን ሊሆኑ ይችላሉ።

(ማስታወሻ፡ ይህ እውነት ከሆነ፥ ከዚህ ቀደም ብሎ የአማኞች የምድር ላይ ሕይወት የሚገመገምበትና ሰማያዊ ሽልማት የሚያገኙበት ጊዜ ይኖራል። ጳውሎስ ይህንን የክርስቶስ የፍርድ ወንበር ሲል ይጠራዋል። 1ኛ ቆሮ. 3፡11–15 አንብብ። ይህ ፍርድ ድነትን (ደኅንነትን) የሚመለከት አይደለም። ነገር ግን የአንድ አማኝ ሕይወት በማይጠቅሙ ነገሮች ለምሳሌ፡- ገለባ፥ እንጨት፥ ወይም በሚጠቅሙ ነገሮች ለምሳሌ፡- ወርቅ፥ ብር፥ የከበሩ ድንጋዮች መሟላቱን ለማረጋገጥ የተሰየመ ችሎት ነው። ለእግዚአብሔር የምናደርገው ነገር ጠቃሚ መሆን አለመሆኑ የሚወሰነው ክርስቶስን በምናገለግልበት ጊዜ ባለን ዓላማና አመለካከት ላይ ነው። በዙፋኑ ላይ የተቀመጠው እጅግ ታላቅ፥ ኃያልና ቅዱስ በመሆኑ፥ በተምሳሌታዊ አገላለጽ ፍጥረት ሁሉ ከፊቱ ሊቆም አይችልም። ፈራጁ እግዚአብሔር አብና ወልድ ይመስላል (ራእይ 22፡1፥3)። የፍርዱ መሠረት ምንድን ነው? ፍርዱ የሚሰጠው በሁለት መጻሕፍት ላይ ተመሥርቶ ነው፡–

ሀ. የሕይወት መጽሐፍ፡ ይህ የሰማይ ዜጎችን ስም የሚዘረዝር መጽሐፍ ነው። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የሚገኘው በዘመናት ሁሉ ያመኑት ሰዎች ስም ብቻ ነው። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ስማቸው የተጻፈላቸው ሰዎች የመንግሥተ ሰማይ ነዋሪነትና የዘላለም ሕይወት ይሰጣቸዋል። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ስማቸው ያልተጻፈላቸው ሰዎች ወደ ሲዖልና ዘላለማዊ ሞት ይላካሉ።

ለ. የሰዎችን ተግባራት የሚገልጹ መጻሕፍት፡ አንድ ሰው በምድር ላይ በኖረበት ሁኔታ ላይ ተመሥርቶ በሰማይ ለአማኞች የሚሰጡ ሽልማቶች በደረጃ እንደሚለያዩ ሁሉ፥ ለኃጢአተኞችም በምድር ላይ ሳሉ በፈጸሟቸው ተግባራት ላይ የተመሠረቱ የተለያዩ ፍርዶች የሚሰጡ ይመስላል። እንደ ሂትለር ሰይጣን የላቀ ክፋት ለመፈጸም የተጠቀመባቸው ሰዎች ክርስቶስን አልከተልም እያለ ዳሩ ግን መልካም ሕይወት ከመራ ሰው የባሰ ቅጣት ይጠብቃቸዋል። ነገር ግን መልካም ሕይወት መምራቱ ብቻ ሰውን ስሙ በመንግሥተ ሰማይ ዜጎች መዝገብ ውስጥ እንዲሰፍር አያስችለውም። የማያምኑ ሰዎች ሁሉ ሁለተኛው ሞት ለተባለው ዘላለማዊ የሲዖል ፍርድ ይጋለጣሉ። በዚህ ስፍራ ሞት የሚያመለክተው የሕልውናን ፍጻሜ ሳይሆን ከእግዚአብሔር መለየትን ነው። 

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ይህ በክርስቶስ ላይ ያላቸውን እምነት ለሚተዉ ሰዎች እንዴት ጠንካራ ማስጠንቀቂያ እንደሚሆን ግለጽ። ለ) ይህ ለማያምኑ ሰዎች ምን ማስጠንቀቂያ ይሰጣል? 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “የክርስቶስ የሺህ ዓመት ንግሥና (ራእይ 20፡1-15)”

Leave a Reply

%d bloggers like this: