ፔንታቱክ በአንድ ጸሐፊ (ሙሴ) የተጻፈ የቅዱሳት መጻሕፍት አንድ ክፍል ቢሆንም፥ በውስጡ አራት የተለያዩ የሥነ-ጽሑፍ ዓይነቶች ይገኛሉ፡፡ አንድ የተወሰነ ክፍል ወስደን ለመተርጎም በምናጠናበት ጊዜ ሰሚገባ እንተረጉመው ዘንድ የሥነ-ጽሑፍ ዓይነት ወስነን በዚያው መልክ መተርጎም ይገባናል። በፔንታቱክ ውስጥ አራት ዋና ዋና የሥነ-ጽሑፍ ዓይነቶች ይገኛሉ።
፩. የታሪክ ጽሑፎች፡- በብሉይ ኪዳን ውስጥ በብዛት የምናገኘው የሥነ -ጽሑፍ ዓይነት የታሪክ ጽሑፍ ወይም ትረካ ነው። መጽሐፍ ቅዱሳችንን በአጠቃላይ በሚመለከትም ይህ እውነት ነው። የብሉይ ኪዳንን ሥነ ጽሑፍ ስንመለከት ከመቶ አርባው እጅ (40%) ትረካ ነው። በታሪክ ጽሑፎች ውስጥ የቅዱሳት መጻሕፍት ጸሐፊው ማንኛውም ሰው በሚረዳው በቀላል ቋንቋ ታሪኩን ይተርካል። የሚናገረውም ምን እንደተፈጸመ ነው። ይህም ሆኖ መጽሐፍ ቅዱስን ልዩ የሚያደርገው የሚናገረው ታሪክ ተራ ያለመሆኑ ነው። ታሪኮቹ የተጻፉት በድሮ ጊዜ ምን እንደተፈጸመ ሊነግሩን ብቻ አይደለም።
የውይይት ጥያቄ፥ ሮሜ 15፡4 እና 1ኛ ቆሮ. 10፡11 አንብብ። የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ዛሬ ለእኛ ያላቸው ዓላማ ምንድን ነው?
እንዳንድ ምሁራን የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክን «የድነት (ደኅንነት) ታሪክ» ብለው ይጠሩታል። ሌሎች ደግሞ «የእግዚአብሔር ታሪክ» ይሉታል። የታሪክ ጽሑፎች ዋና ዓላማ እግዚአብሔር በፍጥረት ውስጥና በሕዝቡ መካከል ሲሠራ ማሳየት ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ዳር እስከ ዳር የምናየው አንድ ዋና ዓላማ እግዚአብሔር በታሪክ ውስጥ በተለያዩ ሰዎች ሕይወትና በልዩ ነገድ ውስጥ ሲሠራ ድነትን (ደኅንነትን) እየገለጠ መሆኑን ነው፤ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገረው ከዚህ በፊት ስለተፈጸሙት እውነተኛ ታሪካዊ ክስተቶች ቢሆንም ጸሐፊው ስለ እነርሱ በሚጽፍበት ጊዜ ሁለት ዓላማዎችን ይዞ ነበር። የመጀመሪያው፥ ባለፈው ጊዜ ምን እንደተፈጸመ በትክክል መናገር ሲሆን፥ ሁለተኛው ደግሞ፥ የእግዚአብሔር ሰዎች ባለፉት ጊዜያት ከኖሩት ሰዎች አዎንታዊ ወይም አሉታዊ ምሳሌነት በመማር እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሕይወት እንዴት መኖር እንደሚችሉ ለማሳየት ነው። ለምሳሌ፡- ሳምሶን በአሉታዊ ምሳሌነቱ ትምህርት ልናገኝበት ለምንችለው ታሪክ አንድ ጥሩ ምሳሌ ነው (መሳ. 13-16)። ክርስቲያኖች እንደመሆናችን፥ ሳምሶን በፍትወተ ሥጋ ኃጢአት በመውደቁ ሕይወቱን እንዴት እንዳጠፋ በመመልከት። ሕይወታችንና አገልግሎታችን እንዳይበላሽ በፍትወተ ሥጋ ኃጢአት እንዳንወድቅ መጠንቀቅ እንዳለብን እንማራለን።
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አንዳንድ ክርስቲያን መሪዎች ሳምሶን በወደቀበትአኳኋን የሚወድቁት እንዴት ነው? ለ) ከሳምሶን ሕይወት መጥፎ ምሳሌነት ምን ሊማሩ ይገባ ነበር?
ከታሪኮች በጎ ምሳሌነትም ልንማር ይገባናል። ለምሳሌ፥ አብርሃም ይስሐቅን ለመሠዋት ከፈቀደበት ታሪክ እግዚአብሔር ከማንኛውም ነገር ይልቅ ከቤተሰባችንም በላይ እንዴት እርሱን መውደድ እንዳለብን እንደሚፈልግ እንማራለን (ዘፍ. 22)።
የብሉይ ኪዳንን ታሪካዊ ክፍሉች የምንተረጉምባችው በርካታ መመሪያዎች አሉ። ከዚህ በታች የተሰጡት እግዚአብሔር ከታሪክ ውስጥ ምን ሊያስተምረን እንደሚፈልግ ለመረዳት እንድንችል ሁል ጊዜ በአእምሮአችን ውስጥ ልንጠብቃችው ከሚገቡን ነገሮች ጥቂቶቹ ናቸው።
- የብሉይና የአዲስ ኪዳን ታሪኮችን መረዳት የሚገባን በሦስት የተለያዩ ደረጃዎች ነው። በመጀመሪያ፥ እያንዳንዱ ታሪክ ከፍተኛ ደረጃ አለው። ታሪኩ በዚህ ደረጃው ስለ እግዚአብሔር ሰፊ ነገር ያስተምረናል። በዚህ ደረጃ ጸሐፊው ሊነግረን የሚፈልገው፥ እግዚአብሔር በአንድ ሕዝብ ወይም በግለሰቦች ሕይወት ውስጥ ሊሠራ ያለውን ዓለም አቀፋዊ ዕቅድ ነው። አብዛኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ስለ እግዚአብሔር አካላዊ ሕልውና፥ ዓለምን ስለ መፍጠሩ፥ ስለ ሰው ልጅ ክፋትና በእግዚአብሔር ስለ መቤዠት አስፈላጊነት አንዳንድ ነገሮችን ያስተምረናል። ይህ ከፍተኛ ደረጃ እግዚአብሔር ሁሉን ነገር ለማስተካከል ስለ ሚሰጠው መሢሕም ይናገራል።
የውይይት ጥያቄ፥ አንድ የብሉይ ኪዳን ታሪክ ምረጥ። ይህ የመረጥከው ታሪክ (ስለ እግዚአብሔር ባሕርይና ዓላማ፥ ከሰው ልጅ ጋር አብሮ ስለ መሥራቱ፥ ለስው ልጅ ኃጢአተኛነት ወይም እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ለመዋጀት ስላለው ዕቅድ ምን ያስተምረናል?
ሁለተኛው፥ የታሪኩ መካከለኛ ክፍል ነው። ይህ ደረጃ ማዕከላዊ የሚያደርገው በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ሕዝብ የነበሩትን እስራኤልን ነው። በአዲስ ኪዳን ይህ ደረጃ የሚያተኩረው በኢየሱስና በቤተ ክርስቲያን ጅማሬ ላይ ነው። የብሉይ ኪዳን ታሪክ የሚያተኩረው በእስራኤል ሕዝብ አካባቢ ነው። የእስራኤል ሕዝብ በአብርሃምና በዘሮቹ እንዴት እንደተጀመረ በዘፍጥረት እናነባለን። ከዘጸአት ጀምሮ እስከ 2ኛ ዜና ባለው ክፍል ደግሞ እግዚአብሔር ለእስራኤል ሕዝብ የተስፋይቱን ምድር እንዴት እንደሰጣቸው፥ በዳዊት በኩል የተሳካላቸው ሕዝብ አድርጎ እንዴት እንደለወጣችው፥ ሕዝቡ እንዴት በኃጢአት እንደወደቁና እግዚአብሔር እንደቀጣቸው እንመለከታለን። አብዛኛውን ጊዜ የብሉይ ኪዳን ታሪኮች እግዚአብሔር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር እንዴት ይሠራ እንደነበረ ያመለክታሉ። ስለዚህ አንድን ታሪክ በምናጠናበት ጊዜ እግዚአብሔር ስለ እስራኤል ሕዝብ ምን እንደሚል መገመት አለብን።
የውይይት ጥያቄ፥ ሌላ የብሉይ ኪዳን ታሪክ ምረጥ። ያ ታሪክ በእስራኤል ሕዝብ አጠቃላይ ታሪክ ላይ ምን የሚጨምረው ነገር አለ?
ሦስተኛው፥ የእስራኤልን ሕዝብ ታሪክ የተሟላ የሚያደርጉት የግለሰቦች ታሪኮች አሉ። የአብርሃም፥ የሙሴ፥ የዳዊት፥ ወዘተ ታሪኮች ተጽፈው ይገኛሉ። ከእነዚህ ታሪኮች በርካታ መንፈሳዊ እውነቶችን እንማራለን።
እያንዳንዱ የግለሰብ ታሪክ የመጽሐፍ ቅዱስ ትረካ የተመሠረተበት ነው። ጸሐፊው የእያንዳንዱን ግለሰብ ታሪክ ሲጽፍ ትልቅ ዓላማ ነበረው። ሊነግረን የፈለገው የእስራኤልን ሕዝብ ታሪክ ቢሆንም፥ የእያንዳንዱ ግለሰብ ታሪክ የሚጫወተው ትልቅ ሚና አለው፤ ነገር ግን ከዚህም በላይ ጸሐፊው ሊነግረን የፈለገው ስለ እግዚአብሔርና ከሰዎች ጋር ስላለው ግንኙነት ነው።
ስለ እግዚአብሔር ማስተማር
ስለ እስራኤል ማስተማር
ስለ ግለሰቦች ማስተማር
- የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች በትምህርት ቤት እንደምናጠናቸው ዓይነት የጥንት ሰዎች ታሪክ ብቻ አይደሉም። ይልቁንም እግዚአብሔርን ለመግለጥና ለሰዎች በሰዎች በኩል ምን እንዳደረገ የሚነግሩን ናቸው። የመጽሐፍ ቅዱስ ትኩረት በእግዚአብሔር ላይ እንጂ ሰዎች ባደረጉት ነገር ላይ አይደለም።
- በብሉይ ኪዳን የታሪክ ጽሑፎች ውስጥ የቃላትን ተምሳሌታዊ ትርጉም መፈለግ የለብንም። ታሪኩን ልክ ተጽፎ እንዳለ በቀጥታ ለመረዳት መሞከር ያሻል። ይህም ማለት ድርጊቱ በተፈጸመበት ታሪካዊ መሠረት ልንረዳው ያስፈልጋል ማለት ነው። ለመረዳት የማንችላቸው ባሕላዊ ነገሮች ካሉ ለመረዳት መሞከር አለብን። አንድን ታሪክ ከመተርጎማችን በፊት ባሕላዊ ነገሮችን ስለ መረዳት አስፈላጊነት ጥሩ ምሳሌ የሚሆንን ቦዔዝ በምሽት መጎናጸፊያውን በሩት ላይ ስለማኖሩ የሚናገረው ታሪክ ነው። በአይሁድ ባሕል ይህ አንድ ሰው የማግባት መግለጫ ነው (ሩት 3፡9)። እነዚህን የተለያዩ ባሕላዊ ተግባሮች ለመረዳት ካልቻልን፥ በታሪኩ ውስጥ ልንረዳቸው የማንችላቸው በርካታ ነገሮች ይኖሩና የእግዚአብሔርን ሥራና በታሪኩ ውስጥ በተመለከትነው መንገድ አንድን ነገር የፈጸመበትን ምክንያት ምን እንደሆነ ሳንረዳ እንቀራለን። ታሪኩን ለማሟላት አንዳንድ ነገሮችን በመገመት የራሳችንን አስተሳሰብ እንዳንጨምር መጠንቀቅ አለብን።
- አንዳንድ ጊዜ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ዋናውን ትምህርት በቀጥታ አያስተምሩም። እንደ አንዳዶቹ የመጽሐፍ ቅዱስ የማስተሪያ ክፍሎች፥ (ለምሳሌ፡- ሮሜ) እግዚአብሔር እንድናውቅ የሚፈልገውን ነገር በቀጥታ አይናገሩም። ይልቁንም በታሪኩ ውስጥ ያለውን ትምህርት የምናገኘው በተዘዋዋሪ መንገድ ነው። ብዙውን ጊዜ ታሪኮቹ በሌላ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሚገኙ ቀጥተኛ ትምህርቶችን ይገልጻሉ። ለምሳሌ፡- በዳዊትና በቤርሳቤህ ታሪክ ውስጥ ዝሙት ስሕተት እንደሆነ በቀጥታ አልተናገረም። ይህ ዘጸ. 20፡14 ላይ በቀጥታ ተነግሯል። ይህ ታሪክ ግን በተዘዋዋሪ መንገድ እግዚአብሔር ዝሙትን እንደሚጠላ ያስተምራል።
- እያንዳንዱን ታሪክ ለሥነ- ምግባር ወይም ለማስተማሪያነት ከመፈፈለግ ይልቅ አንድ ታሪክ የሌላ ትልቅ ታሪክ ክፍል አካል መሆኑንና ዋናው ትኩረቱም የትልቁን ታሪክ ዋና ትምህርት ማግኘት እንጂ ትንሹ ታሪክ ላይ እንዳልሆነ ልናስታውስ ያስፈልገናል።
- በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙ ታሪኮች እያንዳንዳቸው መንፈሳዊ መመሪያን ለማስተማር የተመረጡ ናቸው። የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች ሊጠቀሙባቸው የሚችሉ በርካታ ታሪኮች ነበሩ። አንድን ታሪክ በተለይ የመረጡበት ምክንያት ምንድን ነው? ምክንያቱም እነዚያ ታሪኮች የሥነ ምግባር ወይም መንፈሳዊ ትምህርት ለማስተማር የተመረጡ ነበሩ፤ ስለዚህ አንድ ታሪክ በባሕላዊ መልኩ አንድ ጊዜ በግልጽ ከተረዳነው በኋላ ከታሪኩ የሚገኘውን ዋና መንፈሳዊ ትምህርት መፈለግ አለብን። ይህ ትምህርት ብዙ ጊዜ የሚገኘው በታሪኩ ውስጥ የሚገኙ ሰዎች ባደረጉት ምርጫ ወይም በፈጸሙት ተግባር ነው። ታሪኩን በመረዳት ሂደት ውስጥ ራሳችንን በውስጡ በማስገባት በዚያን ጊዜ የምንኖር ብንሆን ኖሮ ምን ይሰማን ወይም ምን እናደርግ ነበር? ብሎ መጠየቅ ብዙ ጊዜ በጣም ጠቃሚ ነው።
- በትረካው ጽሑፍ ውስጥ ጸሐፊው የተፈጸመውን ነገር በትክክል የሚገልጽ መሆኑን መገንዘብ መልካም ነው። እርሱ ይህ ጥሩ ነው ላይል ይችላል። ለምሳሌ፡- በዘፍ. 38 ይሁዳ ሴተኛ አዳሪ ናት ብሎ ከገመታት ሴት ጋር እንደ አመነዘረ እናነባለን። ይህ ስሕተት እንደሆነ ከሌሎች የቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርቶች በግልጽ እንረዳለን። የጸሐፊው ትኩረት ግን ድርጊቱን መግለጥ ነው እንጂ የሰውዬውን ተግባር መደገፉ አልነበረም፤ ስለዚህ የመጽሐፍ ቅዱስን ታሪክ በምንመዝንበት ጊዜ ጸሐፊው ዝም ብሉ የተፈጸመውን ድርጊት መግለጥ (ለምሳሌ የአንድን ግለሰብ ኃጢአት) ወይም እነዚያ ታሪኮች የተከበሩና ልንከተላችው የሚገባን መሆናቸውን እያስተማረን እንደሆነ መገንዘብ አለብን።
የውይይት ጥያቄ፥ ዘፍ. 9፡20-27 አንብብ። ሀ) በእነዚህ ቁጥሮች የተነገረው ታሪክ ምንድን ነው? ለ) በዚህ ታሪክ ውስጥ ልንረዳቸው የሚያስፈልጉ ባሕላዊ ነገሮች የትኞቹ ናቸው? ሐ) የዚህ ታሪክ የሥነ-ምግባር ትምህርት ምንድን ነው? መ) የሥነ-ምግባር ትምህርቱ የተገኘው ከአዎንታዊ ነው ወይስ ከአሉታዊ ተግባር? አብራራ። ሠ) ጸሐፊው በቀጥታ ስሕተት መሆኑን የማያሳየው፥ ነገር ግን ከሌላ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የምንረዳው ምን ድርጊት ተገልጧል?
፪. ግጥምና ቅኔ፡- በፔንታቱክ ውስጥ የጥንት የዕብራውያን ንግጥምና ቅኔ ተሠራጭቶ እናገኛለን። ሥነ-ግጥምና ቅኔ በተለያዩ ባሕሎች ውስጥ የተለያየ ገጽታ ስላለው፥ አይሁድ እንዴት እንደሚጠቀሙበት ልንገነዘብ ያስፈልጋል። ቆየት ብለን እንደ መዝሙረ ዳዊትና መጽሐፈ ምሳሌ ያሉትን መጻሕፍት በምናጠናበት ጊዜ ሥነ-ግጥምና ቅኔ እንዴት እንደሚተረጎሙ የሚያስረዱ ሕግጋትን እንመረምራለን። ስለ ግጥምና ቅኔ ልንረዳው የሚገባ አንድ ዋና ነገር ብዙ ጊዜ የሚጻፈው በተምሳሌታዊ መግለጫ መልክ እንጂ በቀጥታ አለመሆኑን ነው። ለምሳሌ በመዝሙረ ዳዊት ዛፎች ለእግዚአብሔር ሲዘምሩ እንመለከታለን (መዝ. 96፡ 12 ተመልከት)። እኛ በምንዘምረው ዓይነት ዛፎች እንደማይዘምሩ እናውቃለን፤ ነገር ግን እኛ በቃላችን እግዚአብሔርን እንደምናመሰግን ዛፎችም እርሱ ፈጣሪያቸው በመሆኑ ያመሰግኑታል። ስለሆነም በሥነ-ግጥምና ቅኔ ቋንቋ፥ ቃላት ራሳቸው ተምሳሌታዊ ይሆኑና ከምልክቱ ወይም ከምሳሌው ጋር ተመሳሳይ የሆነ አንድ ተግባር ወይም እውነት ይጠቁማሉ። ሥነ-ግጥምና ቅኔን በምንተረጉምበት ጊዜ ምልክቶቹን ከእውነተኛ ትርጉም ወይም ከተሰወረ እውነት መለየት አለብን።
የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 15፡1-18 አንብብ ሀ) ሙሴ ወደ እግዚአብሔር በዘመረው ዝማሬ ውስጥ የሚገኙትን ተምሳሌቶች ዘርዝር። ለ) እነዚህ ተምሳሌቶች ምን ያስተምሩናል?
በእነዚህ ቁጥሮች ሙሴ መዝሙሩን የእግዚአብሔርን ታላቅነትና ክብር ለመግለጥ ይጠቀምበታል። በመዝሙሩ ውስጥ በርካታ ተምሳሌቶችን ይጠቀማል። ለምሳሌ፡- እግዚአብሔር የፈርዖንን ሠራዊት ሊያሸንፍ እንደቻለ አንድ ታላቅ ተዋጊ አድርጎ ያቀርበዋል። ከታሪኩ እንደምናስታውሰው ግን የፈርዖንን ሠራዊት ድል ለማድረግ እግዚአብሔር የተጠቀመው በታላቅ ውኃ ነው። እግዚአብሔር ቀኝ እጅና አፍንጫ እንዳለው ሆኖ ቀርቦ እናየዋለን። ከመጽሐፍ ቅዱስ እንደምንረዳው ግን እግዚአብሔር መንፈስ ስለሆነ እንደ እኛ ሥጋዊ አካል ሊኖረው አይችልም። ሙሴ እግዚአብሔር እንዴት ታላቅ እንደሆነና ለእስራኤል ለመሥራት ሲል ኃይሉን እንዴት እንደተጠቀመበት ለመግለጥ ሰብአዊ አባባሉን በሥነ-ግጥምና በቅኔ መልክ አቅርቧል።
፫. ትንቢት፡- በፔንታቱክ ውስጥ ተሰራጭተው የሚገኙ የተለያዩ ትንቢቶች አሉ። ከእነዚህ ትንቢቶች አንዳንዶቹ በቀጥተኛ ቋንቋ የቀረቡ ሲሆን (ምሳሌ፡- ዘፍጥ. 15፡13)፡ ሌሎቹ ደግሞ በተምሳሌነት ወይም በሥነ-ግጥምና በቅኔ መልክ ቀርበዋል (ምሳሌ፡- ዘፍ. 49፡8-12)። በብሉይ ኪዳን የሚገኙ ትንቢቶች አብዛኛዎቹ በሥነ ግጥምና በቅኔ መልክ የቀረቡ ናቸው። ትንቢት በሥነ-ግጥምና በቅኔ መልክ ቀርቦ ተምሳሌታዊ የሆነ መግለጫ መያዙ ለመተርጎም በጣም ከባድ ያደርገዋል። በብሉይ ኪዳን ትንቢት ሁለት የተለያዩ ትርጉሞች አሉት። በመጀመሪያ፥ ትንቢት የሚለው ቃል በማንኛውም ጊዜ እግዚአብሔር ለሕዝቡ ቀጥተኛ ትምህርትን ለመስጠት ወይም ፈቃዱን ለመግለጥ አንድን ሰው ተጠቅሞ የሚያመጣው መልእክት ነው። በብሉይ ኪዳን የሚገኙ አብዛኛዎቹ ትንቢቶች ስለ ወደፊቱ ነገር የሚናገሩ አይደሉም፤ ነገር ግን እግዚአብሔር በዚያ ዘመን ለነበሩ ሰዎች እነርሱ ምን እንዲያደርጉ ይፈልግ እንደ ነበር የሚገልጥ መልእክት ነው። ሁለተኛ፥ በአንዳንድ ትንቢቶች እግዚአብሔር ወደ ፊት ምን እንደሚሆን አስቀድሞ ይገልጣል። በዘፍጥረት 49 እግዚአብሔር መሢሑ የሚመጣው ከይሁዳ ነገድ እንደሚሆን አስቀድሞ ለመናገር ያዕቆብን ተጠቅሞበታል፤ ስለዚህ የትንቢት መልክ ወዳለው የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍል ስንደርስ የትኛው የወደፊትን ነገር እንደሚያመለክትና የትኛው ደግሞ በዚያን ጊዜ ለሚሆነው ጉዳይ የተለየ ትእዛዝ እንደሆነ መለየት ያስፈልገናል። እንዲሁም ያ ትንቢት የተሰጠው ለምን እንደሆነም በግልጥ መወሰን አለብን። ይህ ትንቢት የተነገረው በዚያን ጊዜ ለነበረ አንድ ሰው፥ ወይም ቡድን ነውን? ወይስ ዛሬ ካለን ሰዎች ሕይወት ጋርም የሚዛመድ ነው? ብለን መጠየቅና ለዚህ መልስ ለማግኘት መቻል አለብን። ከኢሳይያስ እስከ ሚልክያስ ያሉትን የነቢያት መጻሕፍት ስናጠና ይህንን በጥልቀት እንመለከተዋለን።
፬. ሕግ፡- የፔንታቱክ አብዛኛው ክፍል «ሕግ» የተባለ የተለየ ዓይነት ሥነ-ጽሑፍ ነው። በአንዳንድ ረገድ የምድራችን ሕግጋት ድንጋጌዎች የሆኑት ደንቦች ዝርዝር ነው። አንዳንዶቹ ከዘጸአት እስከ ዘዳግም ባሉት መጻሕፍት ውስጥ ከእግዚአብሔር የተሰጡ ከ600 የሚበልጡ ሕግጋት እንዳሉ ገምተዋል።
እግዚአብሔር ለአይሁድ ይህን ሁሉ ሕግ የሰጠበት ምክንያት ምንድን ነው? የመጽሐፍ ቅዱስ ሕግ በእግዚአብሔርና በአይሁድ ሕዝብ መካከል ያለ ቃል ኪዳን አንዱ ክፍል ነበር። እግዚአብሔር እውነተኛ የአይሁድ ንጉሥ እንደመሆኑ መጠን ሕይወታቸውን በሙሉ የሚገዙበትና የተለዩ «ቅዱስ» ሕዝብ ሆነው ለመኖር የሚችሉባቸውን የተለያዩ ግልጥ ሕግጋት ሰጣቸው። የእግዚአብሔር ልጆች እንደመሆናቸው መጠን ቅዱስ የሆነውን እግዚአብሔርን መምሰል ነበረባቸው።
የውይይት ጥያቄ፥ ቅድስና ዛሬ ለእኛ የሚያስፈልገው እንዴት ነው?
እግዚአብሔር፥ አይሁድ የሕይወታቸውን የተለያዩ አቅጣጫዎች በሙሉ እንዲነካ ግንኙነታችውን በእርሱ ላይ እንዲመሠርቱ ይፈልግ ነበር። እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ፊት የተቀደሰ ሕይወት እስከኖሩና እግዚአብሔር የሰጣቸውን የቃል ኪዳን ግዴታዎች እስካሟሉ ድረስ ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ይኖራቸው ነበር። ከዚያም እግዚአብሔር አምላካቸው ይሆንና ሥጋዊም ሆነ መንፈሳዊ ፍላጎታቸውን በማሟላት ከጠላቶቻቸው ሁሉ ይጠብቃቸው ነበር። ስለዚህ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ለአይሁድ የሰጣቸው ሕግጋት የማይነካው የሕይወታቸው ክፍል አልነበረም። ከጎረቤቶቻቸው፥ ከመሪዎቻቸው ከመንግሥታቸውና ከራሱ ከእግዚአብሔር ጋር እንዴት መኖር እንዳለባቸው የሚናገር ነበር።
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ኅብረት ሕይወታችንን በሙሉ የሚነካው እንዴት ነው?) በኢየሱስ ላይ ያለ እምነትህ ከቤተሰብህ፥ ከጎረቤትህ፥ ከመንግሥትህ፥ ከሥራህና ወዘተ ጋር ያለህን ግንኙነት እንዴት እንደለወጠ ከራስህ ሕይወት ምሳሌ ስጥ።
እግዚአብሔር በፔንታቱክ ውስጥ ለአይሁድ የሰጣቸው ሕግጋት ሦስት ዋና ዋና የሕይወት ክፍሎችን የሚመለከቱ ነበሩ። በመጀመሪያ፣ የመንግሥት ወይም የሕዝብ ሕጎች ነበሩ። እነዚህ ሕጎች፡- የጋብቻ የቤተሰብ፥ የውርስ፥ የንብረት ባለቤትነት መብት፥ የባሪያ፥ የቀረጥ፥ የደመወዝ ወዘተ ናቸው። ሁለተኛ፥ የሥነ- ምግባር ሕግጋት የነበሩ ሲሆን እነዚህም፡- የነፍስ ግድያ፥ ዝሙት፥ ያለፈቃዷ ሴትን የመድፈር፥ የሌብነት፥ የሐሰት ምስክር የመሳሰሉት ናቸው። ሦስተኛ፥ የሃይማኖት፥ የሥርዓት ሕግጋት ሲሆኑ እነዚህ ሕግጋት እስራኤላውያን እንዴት እግዚአብሔርን ማምለክ እንዳለባቸው፥ መሥዋዕት ማቅረብ እንዳለባቸው፥ በሥርዓት ቅዳሴ እንዴት ንጹሐን መሆን እንዳለባቸውና ሃይማኖታዊ በዓላቸውን መቼ ማክበር እንደሚገባችው ወዘተ የሚናገሩ ናቸው።
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በአሁኑ ጊዜ የኢትዮጵያ መንግሥት በተለይ የሚቆጣጠረው የትኞቹን ዓይነት ሕግጋት ነው? ለ) በኢትዮጵያ ያሉ ልዩ ልዩ ሃይማኖቶች የትኞቹ ዓይነት ሕግጋት ናቸው ያሉዋቸው? ሐ) በኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ሃይማኖቶች ውስጥ አንዳንድ የሥነ ምግባርና ሃይማኖታዊ ሕግጋት የሚለያዩት እንዴት ነው?
በፔንታቱክ ውስጥ የሚገኙት ሕግጋት የሚከፈሉት በሦስት ዋና ዋና ክፍሉች ቢሆንም በዓይነታቸው ግን አምስት ናቸው። እነርሱም :
- በተለያዩ ሁኔታዎች ውስጥ ለሚነሡ ጉዳዮች የሚሆኑ ሕግጋት፥ እነዚህ ሕግጋት ብዙ ጊዜ «እንዲህ ቢሆን … እንዲህ ይደረግ» የሚሉ ቃላት ይገኙባቸዋል።
የውይይት ጥያቄ፥ ዘዳ. 22፡22-24 ተመልከት። ሀ) ይህ ሕግ የሚጠቅላችው ልዩ ሁኔታዎች ምንድን ናቸው? ለ) የተጠቀሱት ቅጣቶችስ ምንድን ናቸው?
- ቀጥተኛ ትእዛዛትን በመስጠት እግዚአብሔር ምን እንድናደርግ እንደሚፈልግ የሚናገሩ ሕግጋት፡- እነዚህ ሕግጋት አዎንታዊ (አድርግ …) እና አሉታዊ (አታድርግ …) የሚሉ ትእዛዛት ሊሆኑ ይችላሉ።
የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 20፡3-17 አንብብ። ሀ) በእነዚህ ቁጥሮች የሚገኙትን አዎንታዊ ትእዛዛት ዘርዝር። ለ) በእነዚህ ቁጥሮች የሚገኙትን አሉታዊ ትእዛዛት ዘርዝር።
- ሊሆኑ ስለሚችሉ መላምታዊ ነገሮች የሚናገሩ ሕግጋት፥ እነዚህ ሕግጋት ሊሆኑ ስለሚችሉ ተግባራት ምሳሌዎችን ይሰጣሉ፤ ነገር ግን የምናከናውናቸውን ተግባራት በሚመለከት መከተል የሚገባን ብቸኛ ሁኔታዎች አይደሉም። ለምሳሌ በዘሌ. 19፡ 14 እግዚአብሔር እንዲህ የሚል ትእዛዝ ሰጥቷል፡- «ደንቆሮውን . . . አትሳደብ፥ በዕውርም ፊት ዕንቅፋት አታድርግ፥ ነገር ግን አምላክህን ፍራ» የዚህ ሕግ ዓላማ እነዚህን የተለዩ ሁኔታዎች መቆጣጠር ብቻ አይደለም። ለምሳሌ፡- ይህ ማለት ዕውሩን መስደብና ደንቆሮው ፊት ዕንቅፋት ማድረግ ተፈቅዷል ማለት ነውን? አይደለም። በዚህ ሕግ እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ዕውሮችና ደንቆሮዎች የሚገባቸውን ስፍራ ባለመስጠት ከማጉላላት ይልቅ ሊያከብሩአቸው እንደሚገባ ማሳየቱ ነበር። ይህ ሕግ ከእኛ ይልቅ ጉድለት የገጠማቸውን ሰዎች በሚገባ ያለማክበርን የሚቃወም ነው።
- እጅግ የከፋ በደል ከመፈጸም ጋር የተያያዙና ወንጀሉን በፈጸመው ሰው ላይ የሞት ፍርድ የሚያስከትሉ ሕግጋት ናቸው።
የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 21፡14-17 አንብብ። የማይታዘዘው ሰው እንዲገደል እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ያዘዛቸውን ልዩ ልዩ ሁኔታዎች ዘርዝር።
- በምሥጢር የተፈጸሙና ለማረጋገጥ አስቸጋሪ የሆኑ ጉዳዮችን የሚመለከት ሕግ፥ ብዙ ጊዜ ለእነዚህ ሕግጋት የሚሰጠው ቅጣት «እርግማን» ነበር። በምሥጢር የተፈጸመን ነገር መቆጣጠር ለሰው ልጅ አስቸጋሪ ስለሆነ እግዚአብሔር ራሱ ጥፋተኛውን መቅጣት አለበት። እነዚህን ሕግጋት የተላለፉትን ሰዎች እግዚአብሔር እንደሚቀጣቸው (እንደሚረግማቸው) ቃል ገብቶ ነበር። አንድ ሰው እነዚህን ሕግጋት ሲተላለፍ ቢያዝ፥ የሚደርሱበት የተለያዩ ቅጣቶች ቢኖሩም፥ የእነዚህ ዓይነት ሕግጋት ትኩረት ሕጉን የተላለፉ ሰዎች በሰው ባይያዙም እንኳ ሊቀጣቸው የሚችለው እግዚአብሔር እንደሚያያቸው ለመግለጥ ነበር።
የውይይት ጥያቄ፥ ዘዳ. 27፡17-26 አንብብ። ሀ) ሕግጋቱን በተላለፈ ሰው ርግማን እንደሚደርስበት የሚናገሩትን የተለዩ ሕጎች ዘርዝር። ለ) ሰው ኃጢአታችንን ሊያይ ባይችልም እንኳ እግዚአብሔር አይቶ ይቀጣናል። ይህ እውነት ኃጢአትን ከማድረግ እና ቅጣትን እንደምናመልጥ ከማሰብ እንዴት ይጠብቀናል? የብሉይ ኪዳን ሕግጋት ለክርስቲያኖች ጥቅማቸው ምንድን ነው?
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ብዙውን ጊዜ እኛ ልንታዘዛቸው አይገባንም ብለን የምናስባቸው፥ የኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ግን የሚጠብቋቸውን ሕግጋት ዘርዝር። ለ) የሰባተኛ ቀን አክባሪዎች አድቬንቲስት ልንጠብቃቸው ይገባል የሚሉአቸውን የብሉይ ኪዳን ሕግጋት ዘርዝር።
ስለ እነዚህ ሕግጋት ልንጠይቀው የሚገባ አንድ ዋና ጥያቄ «በአዲስ ኪዳን ዘመን የምንኖር ሰዎች ለእነዚህ የብሉይ ኪዳን ሕግጋት ልንሰጣቸው የሚገባ ስፍራ ምንድን ነው?» የሚል ነው። የብሉይ ኪዳን ሕግጋት ለእኛ ባላቸው ስፍራ የክርስቲያኖች አመለካከት የተለያየ ነው። በግልጽ ስሕተት የሆኑ ሁለት ዓይነት አመለካከቶች አሉ። የመጀመሪያው፥ የብሉይ ኪዳን ሕግጋት በሙሉ ዛሬ እኛንም ይገዙናል የሚለው አሳብ የተሳሳተ ነው። ከአዲስ ኪዳን ትምህርቶች በግልጽ እንደምንመለከተው ስለ ምግብ የተነገሩ ሕግጋት ዛሬ እኛን አይገዙንም። በብሉይ ኪዳን ሥጋቸው እንዲበላ የተፈቀዱ የተወሰኑ እንስሶች ነበሩ (ማር. 7፡14-23፤ የሐዋ. 10:9-16)። እንዲሁም ቅዳሜን እንደ አምልኮ ቀን የመጠበቅ ሕግ እንደማይገዛን ተገልጾአል (ቆላ. 2፡16-17)። እነዚህን ሕግጋት መጠበቅ ባይከፋም፥ በክርስቲያን ላይ ሊሠለጥኑ የሚችሉ ግን አይደሉም።
ሁለተኛው አመለካከት ደግሞ፤ የትኞቹም የብሉይ ኪዳን ሕግጋት በአሁኑ ጊዜ እኛን የሚመለከቱ አይደሉም የሚለው የተሳሳተ አቋም ነው። አንዳንድ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳንና በአዲስ ኪዳን ከሕዝቡ ጋር የተገናኘባቸው መንገዶች ፍጹም የተለያዩ ናቸው ብለው ያስተምራሉ። በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር የተገናኘው «በሕግ» አማካይነት ሲሆን በአዲስ ኪዳን ደግሞ ከክርስቲያኖች ወይም ከቤተ ክርስቲያን ጋር የሚገናኘው «በጸጋ» ነው። ይህ አመለካከት የትኞቹንም የብሉይ ኪዳን ሕግጋት መከተል የለብንም ለማለት ከሆነ የተሳሳተ ነው።
የብሉይ ኪዳን ሕግጋት ዛሬ በእኛ ሕይወት ውስጥ ሊኖራቸው ስለሚገባ ስፍራ አዲስ ኪዳን ምን እንደሚል በምንመረምርበት ጊዜ የሚከተሉትን እውነቶች እናገኛለን፡
- የብሉይ ኪዳን ሕግጋት በሙሉ ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው የጻፉአቸው የእግዚአብሔር ቃል ክፍል ናቸው። እንደቀሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ለትምህርትና፥ በጽድቅ ላለው ልምምድ የሚጠቅሙ ናቸው (2ኛ ጢሞ. 3፡16)።
- እግዚአብሔርን የሚገደው ሕግጋትን በውጫዊ ገጽታቸው መጠበቁ ብቻ አይደለም፤ ይልቁንም የልብን አሳብና መሻት ጭምር ይመረምራል። ለምሳሌ፡- እግዚአብሔር «አታመንዝር» የሚለውን ሕግ ሲሰጥ የከለከለው በጋብቻ ያልተጣመሩ ሰዎች የሚፈጽሙትን ፍትወት ብቻ ሳይሆን ሰውን ወደምንዝርና ሊመራ የሚችለውን ጽኑ የፍትወተ ሥጋ ፍላጎት አሳብ ጭምር ነበር (ማቴ. 5፡27-30)። እግዚአብሔርን ከልብ መታዘዝና ትእዛዛቱንም መጠበቅ ያለብን በውጫዊ አሳብ ብቻ ሳይሆን ከውስጥ በሆነ እውነተኛ ዝንባሌና ስሜትም ጭምር ነው።
ብዙውን ጊዜ ክርስቲያኖች አብልጠው የሚያስቡት ሰዎች እንደ ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ራስን መግዛት፥ ወዘተ (ገላ. 5፡22-23) ካሉት ውስጣዊ ነገሮች ይልቅ ውጫዊ የሆኑት የመጽሐፍ ቅዱስና የቤተ ክርስቲያን ሕግጋትን እንዲጠብቁ ነው። ይህም «ሕግ አጥባቂነት» በመባል ይታወቃል። እግዚአብሔር የሰጠንን ሕግ እንድንጠብቅ የሚፈልግ መሆኑ ግልጽ ቢሆንም፥ የምንጠብቃቸው በተገቢ ምክንያቶች ወይም በእውነተኛ ውስጣዊ ዝንባሌዎች መሆኑን ማረጋገጥም ይፈልጋል።
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ሰዎች እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ዝንባሌ ሊጠብቋቸው የሚችሏቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ ወይም የቤተ ክርስቲያን ሕግጋት ዘርዝር። ለ) እግዚአብሔርን በትክክለኛ ዝንባሌ መታዘዝና በተሳሳተ አመለካከት መታዘዝ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው?
- ሕጉ «ቅዱስ፥ ጻድቅና መልካም» ነው (ሮሜ 7፡12 ተመልከት)። ስለሆነም ይህ ዛሬም ለክርስቲያን ልምምድ ጠቃሚ ነው። ኢየሱስ ሕግን ሊፈጽም እንጂ ሊሽር እንዳልመጣ ተናግሮአል (ማቴ. 5፡17-20)። ስለዚህ ለክርስቲያን የብሉይ ኪዳንን ሕግ ማወቅና መረዳት በጣም አስፈላጊ ነው፤ ነገር ግን ሕግን ራሱን በመጠበቅና በመስጠት ረገድ እግዚአብሔር ባለው ዓላማና ዕቅድ መካከል ግልጥ የሆነ ልዩነት ማድረግ አለብን።
- ከሕግ ሁሉ የሚበልጠውና ሕግን በሙሉ የሚፈጽመው የፍቅር ሕግ ነው (ማቴ. 22፡35-40 ተመልከት)። የፍቅር ሕግ ሁለት አቅጣጫዎች አሉት። በመጀመሪያ፥ ፍቅር ወደ እግዚአብሔር ማመልከት አለበት። እግዚአብሔርን በሙሉ ኃይላችን ልንወደው ይገባናል። እግዚአብሔርን እንደምንወደው የምንገልጽበት መንገድ ትእዛዛቱን መጠበቅ ነው (1ኛ ዮሐ. 5፡1-5)። ሁለተኛ፥ የፍቅር ሕግ ወደ ሰዎችም ማመልከት አለበት። በሙሉ ልባችን እግዚአብሔርን ከወደድንና ፍቅራችንን ለሰዎች ከገለጥን የእግዚአብሔርን ሕግጋት ሁሉ እየፈጸምን ነው ማለት ነው።
የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 20፡1-17 አንብብ። ሀ) ለእግዚአብሔርና ለሌሎች ያለን ፍቅር ዓሥርቱን ትእዛዛት የሚፈጽመው እንዴት ነው? ለ) ሌሎች አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን ሕግጋትና ትእዛዛትን እንዲጠብቁ ትኩረት ከማድረግ ፈንታ እግዚአብሔርንና ሰዎችን የበለጠ እንዲወዱ እንዴት ግበረታታት እንችላለን?
የውይይት ጥያቄ፥ ገላ. 3፡21-25 አንብብ። ሀ) እነዚህ ጥቅሶች ስለ ብሉይ ኪዳን ሕግጋት ዓላማ ምን ያስተምሩናል? ለ) የብሉይ ኪዳን ሕግጋት ሰውን የሚገዙት እስከ ምን ድረስ ነበር?
- ከብሉይ ኪዳን ሕግ ዋና ዋና ዓላማዎች አንዱ ለሰው ልጆች በሙሉ ኃጢአተኝነታቸውና በእግዚአብሔር ላይ ያለማቋረጥ ማመፃቸውን ማሳየት ነበር። በእያንዳንዱ ሰው ልብ ውስጥ በተፈጥሮ ያደረውን ክፉ ነገር ልክ እንደ መስተዋት ሆኖ ለማሳየት ነው። ሕግ ሰዎች ሁሉ ኃጢአተኞች መሆናቸውንና በመልካም ሥራቸው ራሳቸውን ማዳን እንደማይችሉ በግልጥ ያሳያል። እነዚህም ወደ ክርስቶስ ፊታቸውን እንዲመልሱና ከኃጢአታቸው ለመዳን በእርሱ ብቻ እንዲታመኑ ይገፋፋቸዋል።
የውይይት ጥያቄ፡ ሀ) በዚህ ዘመን ሰዎች መዳን ይችሉ ዘንድ ይህንን እውነት ማወቅ ያለባቸው ለምንድን ነው? ለ) ዛሬ ብዙ ሰዎች ወደ መንግሥተ ሰማያት መግባት ይችሉ ዘንድ ሕግን ለመጠበቅ እንዴት ይሞክራሉ? ሐ) ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመግባት የሚያበቃ መልካም ተግባር ለመፈጸም ወይም ሕግን ለመጠበቅ የማንችለው ለምንድን ነው?
ለእስራኤላውያንም ሆነ ለመላው ዓለም ያለው የሕግ ዋና ዓላማ ወደ ኢየሱስ ወይም ወደ እግዚአብሔር ጸጋ እንዲመለከቱ መገፋፋት ነው (ገላ. 3፡24 ተመልከት)።
- ብዙዎቹ የብሉይ ኪዳን ሕግጋት የክርስቶስ ኢየሱስን መምጣትና በኢየሱስ በማመን እንዴት መዳን እንደሚቻል ያመለክታሉ።
የውይይት ጥያቄ፥ ሉቃ. 24፡25-27 አንብብ። ኢየሱስ መሞትና ከሞት መነሣት እንዳለበት ለደቀ መዛሙርቱ ለመግለጽ የተጠቀመው በምንድን ነው?
በብሉይ ኪዳን የተፈጸሙ ብዙ ታሪካዊ ድርጊቶች፡ ሰዎችና ነገሮች ሁሉ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ያመለክታሉ። እርሱ የአምሳላቸው ፍጻሜ ነው። ለምሳሌ አዳም የክርስቶስ አምሳል ነው (ሮሜ 5፡14-19 ተመልከት)። የፋሲካ በዓል የክርስቶስ የመስቀል ሞት አምሳል ነው (1ኛ ቆሮ. 5፡7)። ደግሞም የብሉይ ኪዳን የክህነት አገልግሎት የሊቀ ካህናችን የኢየሱስ ምሳሌ ነው (ዕብ. 7-9)።
የብሉይ ኪዳን ሕግጋትን በምናጠናበት ጊዜ እንዴት ልንተረጉማቸው ይገባል?
- የእነዚህ ሕጎች ውጫዊ ሁኔታ ለአንድ የተለየ ሰው፥ ወይም ቡድን፥ ወይም ሰዎችን ሁሉ የሚመለከት ነውን? ብለን ልንጠይቅ ይገባል። ሕጉ የተሰጠው ለአንድ የተለየ ሰው ወይም ቡድን ከሆነ የሕጉን ውጫዊ አፈጻጸም መከተል አያስፈልገንም፤ ነገር ግን ከሕይወታችን ጋር ልናዛምደው የምንችል የሕጉ ውስጣዊ ዓላማ ብዙ ጊዜ ይኖራል።
- እግዚአብሔር ያንን ሕግ በተለይ የሰጠበትን ምክንያት ለመወሰንም መሞከር አለብን። እግዚአብሔር ውስጣዊ የሆኑ የሕግ ዓላማዎችና ውጫዊ አፈጻጸማቸውንም በሚመለከት ጉዳይ አለው። ብዙ ጊዜ እግዚአብሔር ሕግን የሰጠበት ዓላማ ከሕይወታችን ጋር ሊዛመድ ይችላል።
- በብሉይ ኪዳን ከተሰጡት ሕግጋት መካከል እንደገና እንታዘዛቸው ዘንድ በአዲስ ኪዳን የተሰጡ ልዩ ትእዛዛት መኖራቸውን መመልከትና ማረጋገጥ አለብን። በብሉይ ኪዳን የሚገኝ ሕግ በአዲስ ኪዳን ደግሞ ከተሰጠ ዛሬም ልንታዘዘው እንደሚገባ እርግጠኛች እንሆናለን (ለምሳሌ፡- ዝሙት፥ መግደል፥ መዋሸት፥ ወዘተ)። ከብሉይ ኪዳን ሕግጋት መካከል በአዲስ ኪዳን ልንታዘዛቸው አስፈላጊ እንዳልሆነ የተጠቀሱ ሕጎች እንዳሉም ልንመለከት ያስፈልጋል። ለምሳሌ፡- ኢየሱስ ስለ ምግብ የተሰጡ ሕግጋት አስፈላጊ እንዳልሆኑ ተናግሯል። የዕብራውያን መልእክት ደግሞ ከኢየሱስ ሞት በኋላ እንስሳትን የመሠዋት ሥርዓት አስፈላጊ እንዳልሆነ ያስተምራል።
- የተለያዩ የብሉይ ኪዳን ሕግጋት ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ፥ ከእርሱ ጋር ስላለንና ከሰዎች ጋር ሊኖረን ስለሚገባ ግንኙነት የሚናገሩት ነገር አለን? ብለን ልንጠይቅ ያስፈልጋል።
- ያ የተሰጠን ሕግ የኢየሱስ ክርስቶስ፥ የድነት (ደኅንነት)፥ ወይም የሌላ የአዲስ ኪዳን ጠቃሚ እውነት አምሳል እንደሆነ ለማወቅ መመርመር ያስፈልገናል፤ ነገር ግን ይህንን ስናደርግ በጣም መጠንቀቅ አለብን። የትኛው የብሉይ ኪዳን ክፍል የክርስቶስ አምሳል እንደሆነ፥ የትኛው እንዳልሆነ ለማወቅ የአዲስ ኪዳን ትምህርት ማረጋገጫ ብዙ ጊዜ ያስፈልገናል። በአንዳንድ ሰዎች ዘንድ የክርስቶስ አምሳል ባልሆኑት ነገሮች ውስጥ የክርስቶስን አምሳል የመፈለግ ዝንባሌ አለ።
የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 23ን አንብብ። ሀ) እነዚህን ስድስት ደረጃዎች በመጠቀም ልንጠብቃቸው የሚገባንን ሕግጋት ዘርዝር። ለ) ልንጠብቃቸው የማያስፈልጉ ሕግጋትን ዝርዝር ደግሞ ጻፍ። ሐ) አንዳንዶቹን መጠበቅ ሌሎቹን ደግሞ አለመጠበቅ የሚያስፈልግ ለምን እንደሆነ የሚመስልህን ምክንያት ጻፍ።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)