የፔንታቱክ መግቢያ

ከዚህ በፊት በነበሩት ትምህርቶች፥ ስለብሉይ ኪዳን አንዳንድ የመግቢያ አሳቦች አጥንተናል፤ የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነም ተመልከተናል። ከብዙ ዓመታት በፊት 39 የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የእግዚአብሔር ቃል ይሆኑ ዘንድ በአይሁዶች እንዴት እንደተለዩ ተምረናል። በዚህ ሳምንት ፔንታቱክ ወይም የሙሴ ሕግ ተብለው የሚጠሩትን የመጀመሪያዎቹ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት መመልከት እንጀምራለን። 

ብሉይ ኪዳን የተጻፈው በሁለት ቋንቋዎች ነበር። አብዛኛዎቹ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የተጻፉት በዘመኑ የአይሁድ ቋንቋ በነበረው በዕብራይስጥ ነበር፤ ነገር ግን የባቢሎንና በመካከለኛው ምሥራቅ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ዋና የንግድ ቋንቋ በነበረው በአራማይክ የተጻፉ አንዳንድ የብሉይ ኪዳን ክፍሎችም አሉ። ለምሳሌ፡- ዳን. 2-7ና የዕዝራ አንዳንድ ክፍሎች የተጻፉት በአራማይክ ቋንቋ ነው። ይህ የሆነው በዚህ ጊዜ ብዙ አይሁድ በመካከለኛው ምሥራቅ ተበትነው በአሕዛብ መካከል በምርኮ ላይ ስለ ነበሩ ነው። 

የውይይት ጥያቄ፥ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት፥ ዘዳ. 28፡61፤ ኢያ. 8፡31፤ (ሉቃ. 2፡22)፤ 2ኛ ዜና 31፡3፤ (ሉቃ. 2፡23)፤ ነህ. 8፡3። የመጀመሪያዎቹ አምስት የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት ብዙ ጊዜ በአይሁድ ምን ተብለው ይጠሩ ነበር?

የመጀመሪያዎቹ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት አንዳንድ ጊዜ «ፔንታቱክ» እየተባሉ ይጠሩ ነበር። ፔንታቱክ የሚለው የግሪክ ቃል ትርጉም «አምስት ጥቅል መጻሕፍት» ማለት ነው። ይህም የሚያመለክተው በሙሴ የተጻፉትና በአይሁድ ዘንድ እንደ አንድ ክፍል የሚቆጠሩትን የመጀመሪያዎቹን አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ነው። ይህን ስም ብዙ ጊዜ የሚገለገሉበት በክርስቶስ ጊዜ የግሪክ ቋንቋ ይናገሩ የነበሩ አይሁድ ነበሩ። የዕብራይስጥ ቋንቋ ይናገሩ የነበሩ አይሁድ ግን ለእነዚሁ መጻሕፍት ሌሎች ስሞች ነበሯቸው። ብዙ ጊዜ «ሕግ» ወይም «ቶራህ» ብለው ይጠሯቸው ነበር። ቶራህ ለሕግ የተሰጠ የዕብራይስጥ ስም ነው። 

በመጽሐፍ ቅዱስ በአጠቃላይ የመጀመሪያዎቹ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የተለያዩ ስሞች ተሰጥተዋቸዋል። አንዳንድ ጊዜ «የሕግ መጻሕፍት»፥ «ሕግ»፥ «የሙሴ የሕግ መጻሕፍት»፥ «የሙሴ ሕግ»፥ «በሙሴ መጽሐፍ ውስጥ ያለ ሕግ»፥ «የጌታ ሕግ»፥ «የጌታ ሕግ መጽሐፍ» እና «የሕግ መጽሐፍ» ተብለው ተጠርተዋል። 

አይሁድ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን በሙሉ የሚያከብሩና በእግዚአብሔር መንፈስ ምሪት መጻፋቸውን የሚያምኑ ቢሆኑም ፔንታቱክ ወይም የሙሴ ሕግ መጻሕፍትን ከሁሉ አብልጠው ያከብሯቸዋል። 

የፔንታቱክ መጻሕፍት ጸሐፊ 

የብሉይ ኪዳን የመጀመሪያ መጻሕፍትን ማን ጻፋቸው? እስካለፈው 100 ዓመታት ድረስ አይሁድም ሆኑ ክርስቲያኖች ሙሴ እንደጻፋቸው ያምኑ ነበር፤ ምክንያታቸውም የተመሠረተው በመጽሐፍ ቅዱስና በሽማግሌዎች ወግ ላይ ነው። ቀደም ሲል እንዳየነው፥ ከመጀመሪያዎቹ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ስሞች አንዱ «የሙሴ ሕግ» የሚለው ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 24፡3-4 እና ዮሐ. 5፡46-47 አንብብ። በእነዚህ ቁጥሮች መሠረት የመጀመሪያዎቹን አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የጻፈው ማን ነው? 

ከዘፍጥረት እስከ ዘዳግም ያሉትን መጻሕፍት የጻፈው ሙሴ ነው ብሎ መጽሐፍ ቅዱስ በቀጥታ ባይነግረንም እንኳ በፔንታቱክ ውስጥ የተካተቱ አንዳንድ ነገሮችን እርሱ እንደጻፋቸው ግልጽ ነው። በሲና ተራራ የተቀበላቸውን ሕግጋት እርሱ እንደጻፋቸው እናውቃለን። ከሙሴ ሞት በኋላ ኢያሱ ወዲያውኑ ተተክቶ ሕዝቡን መምራት ሲጀምር እንዲታዘዘው የተሰጠው፥ በሙሴ የተጻፈ መጽሐፍ ነበር፤ (ኢያሱ 1፡7-8 ተመልከት)። ከአዲስ ኪዳን ዘመን ቀደም ብሎ የመጀመሪያዎቹን አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የጻፈው ሙሴ እንደሆነ አይሁድ አምነው ነበር። በአዲስ ኪዳን ውስጥም ቢሆን የፔንታቱክ መጻሕፍት አብዛኛዎቹን ሙሴ እንደጻፈ ተጠቅሶአል። ዘጸአት (ማር. 7፡10)። ዘሌዋውያን (ሮሜ 10፡5)፤ ዘዳግም (ማቴ. 19፡7-8) የተጻፉት በሙሴ እንደሆነ ኢየሱስና ሌሎች በግልጥ ተናግረዋል። የሕግ መጻሕፍት አመዳደብ እንደ ሙሴ መጻሕፍት ሲሆን ይህም ሙሴ በጸሐፊነት የሚታይ መሆኑን ያመለከታል (ሉቃስ 24፡44 ተመልከት)።

በ1900 ዓ.ም. አካባቢ ግን ፔንታቱክን የጻፈው በእርግጥ ሙሴ ለመሆኑ ምሁራን ይጠራጠሩት ጀመር። የፔንታቱክን መጻሕፍት በሚመረምሩበት ጊዜ ከአንድ በላይ የሆኑ ጸሐፊዎች እንደጻፉት የሚያሳዩ በርካታ ነገሮችን አገኙ። ለምሳሌ፡- በኦሪት ዘፍጥረት ሁለት የተለያዩ የፍጥረት ትረካዎች አሉ (ዘፍ. 1 ና 2)፤ ሙሴ ከኖረበት ዘመን ከ500 ዓመታት በኋላ ይኖሩ የነበሩ የእስራኤል ነገሥታት ተጠቅሰዋል (ዘፍጥ. 36፡31)፤ እስከ ዘመነ መሳፍንት ድረስ ወደ ከነዓን ያልመጡ ፍልስጥኤማውያን ተጠቅሰው እናያለን (ዘፍጥ. 21፡34)፤ ደግሞም «እስከ ዛሬ ድረስ» የሚለው ቃል መጽሐፉ የተጻፈው ከሙሴ በኋላ መሆኑን የሚጠቁም ሐረግ ይመስላል (ዘፍጥ. 32፡32)። በተጨማሪም እነዚህ ምሁራን በአጻጻፍ ስልትና በቃላት አጠቃቀም ረገድ ያለው ልዩነት ራሱ የተለያዩ ጸሐፊዎች እንደጻፉት ያሳያል ይላሉ።

በዚህ ምክንያት የፔንታቱክ ጸሐፊ ማን ነው? የሚለውን ጥያቄ በሚመለከት አለመግባባት አለ። እነዚህ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ስለተገኙበት መንገድ አምስት ዋና አመለካከቶች ወይም አሳቦች አሉ።

  1. የፔንታቱክን መጻሕፍት ሁሉ የጻፈው ሙሴ ነው። ሙሴ ያልጻፈው የፔንታቱክ ክፍል ከእርሱ ሞት በኋላ የተጻፈው ዘዳግም 34 ብቻ ነው። ይህንን አቋም የያዙ ሰዎች እንደሚሉት ሙሴ ሌሉች መጻሕፍት ተጠቅሞ ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን እነዚህን አምስት መጻሕፍት ያዘጋጀና የጻፈ እርሱ ነው ይላሉ። አቋማቸውን ለመደገፍም የሚከተለውን መረጃ ይጠቁማሉ፡-

ሀ. ዘኁል. 33፡2 እና በፔንታቱክ ውስጥ ያሉ ሌሎች ጥቅሶች መጻሕፍቱን የጻፈው ሙሴ ነው ይላሉ። 

ለ. በብሉይና በአዲስ ኪዳን የሚገኙ ሌሎች መጻሕፍት ሙሴ የፔንታቱክ ጸሐፊ እንደሆነ ይናገራሉ፤ (ዘኁል. 24፡3-4ና ዮሐ. 5፡46-47)። 

ሐ. በአይሁድም ሆነ በክርስትና አፈ ታሪክ መሠረት ጸሐፊው ሙሴ እንደሆነ ይነገራል።

መ. መጽሐፉን በጥልቀት በማጥናት የምንረዳው ነገር ጸሐፊው የድርጊቱ የዓይን ምስክር እንዲሁም የግብፅን ቋንቋና ባሕል የሚያውቅ ሰው መሆኑን ነው። እነዚህን መመዘኛዎች ሊያሟላ የሚችል ከሙሴ የተሻለ ሰው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጨርሶ አልተጠቀሰም።

  1. ሙሌ የፔንታቱክ ዋነኛው ጸሐፊ ነው። ኦሪት ዘፍጥረትን በሚመለከት የተጻፉት ጽሑፎች በሙሉ ለይቶ፥ አቀናብሮና አስተካክሎ ያዘጋጀ እርሱ ነው። ከቀሩት አራት መጻሕፍትም አብዛኛውን የጻፈው እርሱ ነው፤ ነገር ግን ሙሴ ከሞተ ከረጅም ጊዜ በኋላ አንድ ያልታወቀ ሰው አንዳንድ ጥቃቅን ነገሮችን አክሉባቸዋል። አምስቱ መጻሕፍት ሙሉ በሙሉ የተጠናቀቁት በመጽሐፈ ኢያሱ መጨረሻ አካባቢ ወይም ምናልባት በነቢዩ ሳሙኤል ጊዜ ነው። 
  2. የመጀመሪያዎቹ አምስቱ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የተጻፉት በተለያዩ ሰዎች ሲሆን የተጻፉትም በብዙ መቶ ዓመታት ጊዜ ውስጥ ነው። ይህ አሳብ የተጀመረው በ1876 ሲሆን «በመረጃ የተደገፈ መላምት» ወይም «ጄ.ኢ.ዲ.ፒ. ቲዎሪ» በመባል ይታወቃል። ይህንን አመለካከት የሚደግፉ አብዛኛዎቹ ምሁራን ፔንታቱክም ሆነ የተቀረው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ስሕተት የሌለበት እውነተኛ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን አያምኑም። የአይሁድን ሃይማኖታዊ ልምምድ ለማሳየት የጥንት ሰዎች የጻፉት አድርገው ማመኑ ይቀላቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ በዓለም ዙሪያ እንደሚገኙ እንደ ሌሎች ሃይማኖታዊ መጻሕፍት ነው ይላሉ። እነዚህ ምሁራን በተአምራት፥ በነቢያትም ሆነ በመሳሰለው ለማመን ፈቃደኞች አይደሉም። ትንቢትና ተአምራትን ላለመቀበል አስቀድመው አእምሮአቸውን ያዘጋጁ ናቸው። ይህን መጽሐፍ ቅዱስን በመረዳትና በመተርጎም በኩል ተጽዕኖ ያደርግባቸዋል። ይህ አመለካከት በተለይ ላለፉት 50 ዓመታት ተከታዮች ያተረፈ ቢሆንም፤ በአሁኑ ጊዜ ግን እያሽቆለቆለ በመምጣት ላይ ይገኛል። ይህ አመለካከት ቀደም ብለን ባነሳነው ጉዳይ ላይ በማተኮር፥ ለፔንታቱክ መጻሕፍት አንድ ጸሐፊ ብቻ ሊኖር እንደማይችል ይናገራል። በመሠረቱ ይህ አመለካከት ፔንታቱክ ቢያንስ የአራት ዋና ዋና መጻሕፍት ጥርቅም ሆኖ በአራት መቶ ዓመታት የጊዜ ገደብ ውስጥ እንደተጻፈ የሚያስተምር ነው።

ሀ. የመጀመሪያው መጽሐፍ የሚጠራው በዕብራይስጥ ቋንቋ የእግዚአብሔር ስም በሚጀመርበት «ጄ» በሚለው ፊደል ነው። ስሙም «ጄሆቫ» (ያህዌ) ነው። ይህ ጽሑፍ በ9ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (ዓ.ዓ.) የያህዌ እግዚአብሔርን ታላቅነት ለማግነን በፈለጉ አይሁድ እንደተጻፈ ይናገራል። 

ለ. ሁለተኛው ጽሑፍ የሚጠራው አይሁድ ለእግዚአብሔር ከሰጡት «ኤሎሂም» ከሚለው ስም በተገኘው «ኢ» በሚለው ፊደል ነው። የዚህ ጽሑፍ ጸሐፊ ከእስራኤል የሰሜኑ ክፍል የመጣ ሲሆን የጻፈውም በ8ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (ዓ.ዓ.) እንደሆነ የዚህ አመለካከት አራማጆች ይናገራሉ። ይህ ጸሐፊ «ኤሎሂም» በሚለው የእግዚአብሔር ስም ላይ አተኩሯል። 

እነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ሁለቱ ጽሑፎች ከተጻፉና ሰማርያ በ722 ዓ.ዓ. በአሦራውያን እጅ ከወደቀች በኋላ ከይሁዳ ሳይሆን አይቀርም ተብሎ የሚታሰብ ሰው ወደ አንድ መጽሐፍ አጣምሮአቸዋል የሚል አሳብ ይሰነዝራሉ።

ሐ. ሦስተኛው ጽሑፍ ከመጨረሻው የፔንታቱክ መጽሐፍ በእንግሊዝኛ ዲዮተሮኖሚ ከሚለው ስም የመጀመሪያ ፊደል በመውሰድ «ዲ» ብለው ሰይመውታል። ይህ ሰው ኦሪት ዘዳግምን ከጻፈ በኋላ ከመጽሐፈ ኢያሱ እስከ 2ኛ ነገሥት ላሉት መጻሕፍት ደግሞ የመጨረሻ ማስተካከያ አድርጓል። ይህ የሆነው ከ630-600 ዓ.ዓ. በንጉሥ ኢዮስያስ ዘመን ሳይሆን አይቀርም ይላሉ። 

መ. አራተኛው ጽሑፍ የተጻፈው በአንድ ካህን (ቄስ) ነው ብለው ስለሚያምኑ በእንግሊዝኛ ካህን (ፕሪስት) ከሚለው ስም የመጀመሪያውን ፊደል በመውሰድ «ፒ» ብለው ሰይመውታል። ይህ መጽሐፍ በአምልኮ ሕግጋትና በፔንታቱክ ውስጥ በሚገኘው የትውልድ የዘር ሐረግ ላይ የሚያተኩር ነው። የተጻፈውም ከ500-450 ዓ.ዓ. ነው።

በመጨረሻ፥ በ450 ዓ.ዓ. ገደማ ካህን የነበረ አንድ የመጻሕፍት አዘጋጅ አራቱንም መጻሕፍት በመውሰድ አሁን ዘፍጥረት፥ ዘጸአት፥ ዘሌዋውያን፥ ዘኁልቁና ዘዳግም ወደምንላቸው መጻሕፍት አቀናጃቸው። የዚህ ፅንሰ አሳብ አራማጆች ይህን ያደረገው ካህን ዕዝራ ሳይሆን አይቀርም ይላሉ። ይህም ማለት የፔንታቱክ የመጨረሻ ሥራ አሁን በእጃችን ባለው መልኩ የተጻፈው በ450 ዓ.ዓ. ነው ማለት ነው።

ብዙዎቹ የጥንት የመጽሐፍ ቅዱስ ማብራሪያዎች ፔንታቱክን በሚተረጉሙበት ጊዜ ይህንን ንድፈ ሃሳብ ተከትለዋል። እግዚአብሔር ቃሉን እንዲጽፉ ሰዎችን በመንፈስ ቅዱስ ነድቶአቸዋል፤ ደግሞም መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል በመሆኑ ፍጹም የተለየ መጽሐፍ ነው ብለን ካመንን፥ ይህ አመለካከት ጨርሶ ተቀባይነት ሊኖረው እንደማይችል መገንዘብ አስፈላጊ ነው።

  1. አራተኛው አመለካከት፥ በፔንታቱክ ውስጥ የሚገኙ በርካታ ታሪኮች ከትውልድ ወደ ትውልድ በአፈ ታሪክ (ሥነ-ቃል) ተላልፈዋል የሚል ነው። ከዚያም እነዚህ በአፈ ታሪክ (ሥነ-ቃል) የተላለፉ መልእክቶች በተለያዩ ጸሐፊዎች አማካይነት ተጻፉ። በመጨረሻ እነዚህ መጻሕፍት በአንድ አቀናባሪ ተሰብስበው ተቀናጁ። በ586 ዓ.ዓ. ይሁዳ ከተማረከች በኋላ መጽሐፉ አሁን ባለበት መልኩ ተስተካከለ። 
  2. አንድ የመጨረሻ አመለካከት የሚለው፡- በባቢሎን ምርኮ ጊዜና አይሁድ ወደ ይሁዳ ከተመለሱ በኋላ (586-500 ዓ.ዓ.) የተለያዩ አዘጋጆች የዕብራውያንን ታሪኮች በሙሉ ሰብስበውና አስተካክለው አሁን በመጽሐፍ ቅዱሳችን በሚገኙ አምስት የተለያዩ መጻሕፍት መልክ አቀናበሩአቸው የሚል ነው።

መጽሐፍ ቅዱስ የመጀመሪያዎቹን አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጨምሮ የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነና ሥልጣኑም እግዚአብሔር ራሱ የተናገረን ያህል መሆኑን የምናምን ክርስቲያኖች በመሆናችን ከላይ የተመለከትናቸውን አብዛኛዎቹን አመለካከቶች መቃወም አለብን። የጻፉት የተለያዩ ሰዎች ናቸው ለሚለው አባባላቸው መልስ አለን። አብዛኞቹን የፔንታቱክ መጻሕፍት ክፍሎች የጻፈው ሙሴ ነው የሚለውን አሳባችንን የምንለውጥበት አንዳችም ምክንያት የለንም፤ ነገር ግን ከሙሴ በኋላ የነበሩ ጸሐፊዎች ሙሴ ከሞተ ከብዙ ዓመታት በኋላ ለኖሩ ሰዎች ግልጥ ለማድረግ የተወሰኑ ቃላትን ጨምረው ሊሆን ይችላል የሚለውን አሳብ ልንቀበል እንችላለን። ለምሳሌ «በእነዚያ ቀናት» እና «ከነዓን የፍልስጥኤም ምድር ሆነች» የሚሉትን ቃላት ጨምረው ይሆናል (ዘፍጥ. 10፡14፤ 21፡32)፤ ነገር ግን የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎችና ጌታ ኢየሱስ ራሱም እንዳረጋገጡት የፔንታቱክ ጸሐፊ ሙሴ ነው በሚለው አቋማችን እንጸናለን።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አንድ ሰው ተአምራት የሚባሉ ነገሮች የሉም ብሎ ካመነ ይህ እምነቱ መጽሐፍ ቅዱስን በሚተረጉምበት መንገድ ላይ እንዴት ተጽዕኖ ሊያደርግ ይችላል? ለ) የእግዚአብሔርን ቃል በምንተረጉምበት ጊዜ በእኛ ላይ የሚያደርሰውን ተጽዕኖ በማሰብ አስቀድሞ በአእምሮአችን ስለምንይዘው አሳብ ልንጠነቀቅ እንደሚገባ ይህ ምን ያስተምረናል? ሐ) ራሳቸውን ክርስቲያን ብለው የሚጠሩ የተለያዩ ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል በሚተረጉሙበት ጊዜ እንደዚህ ዓይነት ተጽዕኖ ያደረጉባቸውን ትምህርቶች ዘርዝር፤ (ለምሳሌ፡- የይሖዋ ምስክሮች፥ ካቶሊኮች፡ የኦርቶዶክስ አማኞች፥ ቃለ ሕይወት፣ መካነ ኢየሱስ፥ ሰባተኛ ቀን አክባሪ አድቬንቲስቶች፥ ወዘተ)።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “የፔንታቱክ መግቢያ”

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading