ዘፍጥረት 1-2 የዓለም አፈጣጠር

መጽሐፍ ቅዱስ የሳይንስ ማስተማሪያ ወይም የታሪክ መጽሐፍ አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስ ሳይንስንም ሆነ ታሪክን የሚመለከት መረጃ የያዘ ቢሆንም ዓላማው ግን ይህ አይደለም። የመጽሐፍ ቅዱስ ዓላማ እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ለሰው ልጅ መግለጥ ነው። እግዚአብሔር ዛሬም ቢሆን ለሰው ልጆች የሚናገርበት ዋናው መንገድ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። አንዳንዱ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መረጃ ሳይንስንና ታሪክን የሚመለከት ጉዳይ ቢኖረውም፥ ሳይንስና ታሪክ መርምረው ያገኙት አብዛኛው ነገር በመጽሐፍ ቅዱስ አልተካተተም። ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስ የገለጠው ነገር ሁሉ በሳይንቲስቶችና በታሪክ አዋቂዎች ዛሬ ባይታመን እንኳ፥ ሊታመንና ተቀባይነት ሊያገኝ ይገባል። ክርስቲያኖች እንደመሆናችን ከሰዎች አስተሳሰብና አመለካከት ይልቅ የእግዚአብሔርን ቃል መምረጥ አለብን። 

እንደምናውቀው ዘፍጥረት 1፡1 እንደ ዮሐ. 1፡1 ወደ ጊዜና ወደ ታሪክ መጀመሪያ ይመልሰናል። ይህ የእግዚአብሔር መጀመሪያ ሳይሆን፥ የተፈጠሩ ነገሮች ሁሉ መጀመሪያ ነው። እግዚአብሔር ዘላለማዊ ስለሆነ መጀመሪያ የለውም። 

ዘፍጥረት 1-2 የፍጥረታት ታሪክ አጠር ባለ መልክ አጠቃልሉ ያቀርበዋል። ዘፍጥረት 1 ፍጥረትን ሁሉ በመገምገምና በእያንዳንዱ ቀን የተፈጠረውን ነገር በመናገር የፍጥረታትን ታሪክ ያሳየናል። ከፍጥረታት ሁሉ በመጨረሻ የተፈጠረው የሰው ልጅ ምን ያህል ከሁሉ የላቀ ፍጡር መሆኑንም ያመለክታል። ዘፍጥረት 2 የሚያተኩረው ወንድና ሴት ሆኖ በተፈጠረው በሰው ልጅ ላይ ሲሆን፥ ይኖርበት ዘንድ ስለተዘጋጀለት ዔደን ተብሎ ስለሚጠራው ስፍራም ይናገራል።

በዘፍጥረት 1 እግዚአብሔር ነገሮች ሁሉ እንዴት እንደተፈጠሩ ለማሳየት አይፈልግም። ለምሳሌ መላእክት ወይም ሰይጣን የተፈጠሩት እንዴትና መቼ እንደሆነ የሚናገር ነገር የለም። ይልቁንም በቀላል ቋንቋ እግዚአብሔር የሁሉ ነገር ፈጣሪ እንደሆነ ተገልጧል። ስለዚህ የተፈጠሩ ነገሮች በሙሉ የፈጣሪያቸው የእግዚአብሔር ንብረት ናቸው።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ፈጣሪያችን ስለሆነ ስለ እርሱ ሊኖረን የሚገባ አመለካከት ምን ዓይነት ነው? ለ) እግዚአብሔር ፈጣሪያችንን ልናከብር የምንችልባቸውን መንገዶች ግለጥ። 

በዓለም ላይ የምናያቸው ነገሮች በሙሉ ስለተገኙባቸው መንገዶች የሚናገሩ አምስት የተለያዩ አመለካከቶች አሉ። ከእነዚህ መካከል ሁለቱ መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን የማይቀበሉ ክርስቲያን ያልሆኑ ሰዎች አመለካከቶች ናቸው።

ክርስቲያን ባልሆኑ ሰዎች የሚንፀባረቁ ሁለት አመለካከቶች 

  1. የተፈጠሩ ነገሮች በሙሉ ፈጣሪዎቻቸው የሆኑ የተለያዩ አማልክት የሥራ ውጤቶች ናቸው። ይህ አመለካከት እውነተኛውን አምላክ የማያውቁ የጥንት ሰዎች የሚያንፀባርቁት ነው። ለምሳሌ፡- በብዙ አማልክት የሚያምኑ አንዳንድ ጣዖት አምላኪዎች፡- ምድር የፀሐይ አምላክና የሴት ጨረቃ አምላክ ልጅ ነው ብለው ያምኑ ነበር። በተጨማሪም የሰው ልጅ ከአማልክት መካከል የአንዱ ዝርያ ነው ብለው ያምኑ ነበር። ይህም የቀድሞዎቹ ባቢሎናውያን፥ ግሪኮች፥ ሮማውያንና ከነዓናውያን አመለካከት ነበር። ዛሬም የብዙ አፍሪካውያን አመለካከት ሲሆን ሂንዱይዝም በተባለው በምሥራቃውያን እምነት ውስጥም የሚታይ ነው።

እግዚአብሔር የፍጥረታትን ታሪክ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንዲካተት ያደረገበት አንዱ ምክንያት እርሱ ብቻ የሁሉ ነገር ፈጣሪ እንደሆነ ለማሳየት ነው። ዛሬ እግዚአብሔር እስራኤላውያንንና እኛን አንድ እውነተኛ አምላክ ብቻ እንዳለ ሊያስተምረን ይፈልጋል። እግዚአብሔር «በምድርና በሰማይ ያሉ» ነገሮች ሁሉ ፈጣሪ ነው። ለሰው ልጅ ትክክለኛ ቦታው ራሱን ለእግዚአብሔር አሳልፎ በመስጠት ፈጣሪውና ጌታው መሆኑን ተረድቶ እርሱን በማክበር መኖር ነው። 

  1. የተፈጠሩ ነገሮች በሙሉ የተፈጥሮ «አዝጋሚ ለውጥ» (ኢቮሉሽን) ውጤቶች ናቸው። ይህ ፅንሰ አሳብ ብዙዎቻችን በመንግሥት ትምህርት ቤት የተማርነው ነው። አዝጋሚ ለውጥ እንዴት እንደተፈጸመ የሚያስረዱ በርካታ የተለያዩ ንድፈ አሳቦች ቢኖሩም፥ ይህ አመለካከት የሚያስተምረው ከብዙ ቢሊዮን ዓመታት በፊት አንድ ታላቅ ፍንዳታ ተፈጽሞ ፀሐይ፥ ከዋክብት፥ ሌሉች ፕላኔቶች፥ ወዘተ. ተፈጠሩ። በአንድ ባልታወቀ ምክንያት ሕይወት መጀመሪያ ከተፈጠረው ፕላኔት ይወጣ ጀመር። ከዚያም በመጀመሪያ ዕፀዋት፥ ቀጥሉም እንደ አሜባ ያሉ በጣም ጥቃቅን እንስሳት ተገኙ። እነርሱም ቀስ በቀስ እንቁራሪት ወደ መሳሰሉ እንስሳት ተለወጡ። እነዚያ ደግሞ ቀስ በቀስ ወደ ጡት አጥቢ እንስሳት ተለወጡ በማለት ነው፤ ስለዚህ በቀላል አማርኛ ሰው ከፍተኛው የአዝጋሚ ሂደት ለውጥ ውጤት ነው። ይህ አመለካከት ለእግዚአብሔርና እርሱ ለፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ ምንም ቦታ አይሰጥም።

ሕዝ. 28፡11-17። በእግዚአብሔርና በሰይጣን መካከል በተደረገው ጦርነት የመጀመሪያዋ ምድር ወደ ባዶነትና ጨለማ ተለወጠች በማለት ግምታዊ አስተሳሰባቸውን ይሰጣሉ።

ስለዚህ ይህ አመለካከት ያላቸው ሰዎች ዘፍጥረት ምዕራፍ አንድን ምርኩዝ በማድረግ እግዚአብሔር ዓለምን እንደገና ጠግኖአል ወይም አድሶአል በማለት ያስተምራሉ።

ይህ አመለካከት ሙሉ በሙሉ እንደማይሆን አድርጎ ለመቃወም ባይቻልም ሁለት ዓለማት ስለ መፈጠራቸው መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው ማስረጃ የለም። 

  1. ዘፍጥረት 1 የሚናገረው እግዚአብሔር ዛሬ በዓለም ላይ የሚገኙትን ነገሮች ሁሉ እንዴት እንደፈጠረ ነው። ቁሳዊ የሆኑትን ነገሮች በሙሉ እግዚአብሔር በስድስት ቀናት ውስጥ የፈጠራቸው ናቸው። የተፈጠሩትም ከምንም ነው (ዕብ. 11፡3 ተመልከት)። ይህ አመለካከት በዘመናት ሁሉ አብዛኛዎቹ ክርስቲያኖች ያመኑበት ሲሆን ከሌሎች ሁሉ በተሻለ ሁኔታ ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ጋር የሚስማማ ነው።

ማንም ሰው እነዚህን አመለካከቶች «ማረጋገጥ» አይችልም። ይልቁንም ክርስቲያኖችም ሆኑ ክርስቲያን ያልሆኑ ሰዎች የሚከተሉአቸው እነዚህ አመለካከቶች እምነትን ወይም ሊያዩ የማይችሉትን ነገር መቀበልን ይጠይቃል። የማያምኑ ሰዎችን ሁሉ ማርካት በሚቻልበት መንገድ ክርስቲያኖች ሊገልጹዋቸው የማይችሉዋቸው አንዳንድ ነገሮች ቢኖሩም፥ በዕብ. 11፡3 እንደምናነበው እግዚአብሔር የሁሉ ነገር ፈጣሪ መሆኑን የምንቀበለው «በእምነት» ነው። ይህ ማለት እኛ የእርሱ ፍጥረት ነን። እርሱ ፈጣሪ በመሆኑ በእኛ ላይ ሙሉ ሥልጣን አለው። እኛም ለእርሱ በመገዛት መኖር አለብን።

የውይይት ጥያቄ፥ ሕይወታችንን በሙሉ ለእግዚአብሔር ለመስጠትና እርሱን ሙሉ በሙሉ ለመታዘዝ የምንቸገረው ለምንድን ነው?

እስካሁን ባለን እውቀት አንጻር እግዚአብሔር ዓለምን በስድስት ቀናት እንደፈጠረ ማመን ከሁሉም የሚሻል ነገር ይመስላል። እግዚአብሔር እንደሌለና ነገሮች ሁሉ የአዝጋሚ ለውጥ ውጤቶች እንደሆኑ የሚያምኑ ሰዎችን አጥብቀን መቃወም ያለብን ቢሆንም፥ እኛ ስለ ፍጥረታት አፈጣጠር ካለን አመለካከት ለየት ያለ እምነት ያላቸውን ክርስቲያኖች መቀበል አለብን። ደኅንነታችን የተመሠረተው ስለ ፍጥረታት ባለን ትክክለኛ አመለካከት ሳይሆን፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ባለን እምነት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ፍጥረት የሚናገረው ታሪክ እኛ ለማወቅ የምንፈልገውን ነገር ሁሉ የሚያብራራ ሳይንሳዊ ዘገባ አይደለም። የፍጥረት ታሪክ የተገለጠበት ዓላማ እግዚአብሔር ፈጣሪ እንደሆነና እኛ የእርሱ ልዩ ፍጥረቶች እንደሆንን በግልጥ ለማስተማር ነው።

ይሁን እንጂ የእግዚአብሔርን ቃል ትክክለኛነት በምንም ዓይነት ሁኔታ ከመጠራጠር መጠንቀቅ አለብን። የእግዚአብሔርን ቃል ከለወጥንና እርሱ በግልጽ ከሚያስተምረን ነገር የተለየ አመለካከት ካለን፥ መሠረታችንን አጣን ማለት ነው። ስለ ፍጥረት አፈጣጠር መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው ትምህርት የተሳሳተ ከሆነ ስለ እግዚአብሔር ማንነት፥ ስለ ኢየሱስ ማንነትና እኛን እንዴት እንዳዳነን፥ ወዘተ. የሚሰጠው ትምህርትም የተሳሳተ ሊሆን ይችላል ማለት ነው። እኛም ሆንን ሌሉች ክርስቲያኖች የምንከተለው ማንኛውም አመለካከት በእግዚአብሔር ቃል ላይ በሚገባ የተመሠረተ መሆን አለበት።

ዘፍ. 1፡1-2 የፍጥረት ታሪክ መግቢያ ነው። በመግቢያው ውስጥ እግዚአብሔር የፍጥረት ሁሉ ምንጭ እንደሆነ ይገልጻል። የቀረው የፍጥረት ሥራም እንዴት እንደተከናወነ የሚገልጽ አስተዋጽኦ ይሰጣል። እግዚአብሔር ምንም ቅርፅ የሌላትን ዓለም ወስዶ ቅርፅ ሰጣት። እንዲሁም ባዶና አንዳች ያልነበረባትን ዓለም ወስዶ በተለያዩ ነገሮች ሞላት። 

ከዘፍጥረት ታሪክ የሚከተሉትን ነገሮች አስተውል፡. አንደኛ፥ እግዚአብሔር ሁሉን ነገር የፈጠረባቸው ስድስት ቀናት ነበሩ። ሁለተኛ፥ የፍጥረትን ሥራ የሚመለከቱ ሁለት ዋና ዋና ክፍሎች አሉ። የመጀመሪያው ክፍል እግዚአብሔር ለምድር ቅርፅን እንደሰጠ የሚናገር ሲሆን፥ ሁለተኛው ክፍል ደግሞ እግዚአብሔር የፈጠረውን ነገር በተለያዩ ነገሮች እንደሞላ ይናገራል። ሦስተኛው፥ የሁለቱ ክፍሎች እያንዳንዱ ቀን የተያያዘ ነው። ለምሳሌ፡- 1ኛና 4ኛ ቀናት በሰማይ ስላሉ ብርሃናት መፈጠር ይናገራሉ። 2ኛና 5ኛ ቀናት እግዚአብሔር ባሕርንና ጠፈርን ሲያዘጋጃቸውና ሲሞላቸው እናያለን። 3ኛና 6ኛ ቀናት ደረቅ ምድርን የማዘጋጀትና የመሙላት ሥራ የተከናወነባቸው ቀናት ናቸው። ይህም ዓለምን የመፍጠር ሥራ ግልጥ የሆነ ቅንብር ተደርጎለት እንደ ነበር ያሳየናል።

እግዚአብሔር ሰውን በፈጠረ ጊዜ ይህ ሥራ የሥላሴ ተግባር ነበር። በዘፍ. 1፡2 እግዚአብሔር በመንፈስ ቅዱስ ሥራ አማካይነት የመፍጠርን ተግባር እንዳከናወነ እናነባለን። እግዚአብሔር «እንፍጠር» እያለ ራሱን በብዙ ቁጥር ሲጠራ እንመለከታለን (ዘፍ. 1፡26)። ይህንን በተለያዩ መንገዶች መረዳት ቢቻልም፥ እግዚአብሔር ሦስት አካላት አሉት። እነርሱም እግዚአብሔር አብ፥ እግዚአብሔር ወልድ፥ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሲሆኑ፥ አዲስ ኪዳን በሚሰጠው በዚህ ትምህርት መሠረት ሥላሴ ፍጥረትን በሚመለከት አብረው እንደወሰኑና ሦስቱም በመፍጠር ሥራ ውስጥ እንደተሳተፉ እናያለን። 

የሰው ልጅ መፈጠር

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በዘፍጥረት 1 ስለ ሰው ልጅ መፈጠር የሚናገሩ ስንት ቁጥሮችን ታገኛለህ? ለ) ስለ ሰው ልጅ አፈጣጠር እግዚአብሔር ይህን የመሰለ ሰፋ ያለ ገለጻ የሰጠው ለምን ይመስልሃል? ሐ) የሰውን ልጅ አፈጣጠር የሚናገረው ታሪክ ስለ ሌሎች አፈጣጠር ከተነገረው ታሪክ የሚለየው እንዴት ነው? መ) ሰው «በእግዚአብሔር አምሳል» ተፈጠረ ማለት ምን ማለት ይመስልሃል?

አብዛኛው የፍጥረት ታሪክ የሚያተኩረው አዳምና ሔዋን ተብለው በሚጠሩት በመጀመሪያዎቹ ሰዎች መፈጠር ላይ ነው። በዘፍ. 1 ሙሴ፥ እግዚአብሔር ወንድና ሴትን እንዴት እንደፈጠረ ባጭሩ ይገልጣል። ወንድና ሴት ሁለቱም የተፈጠሩት በእግዚአብሔር አምሳል ነው።

ሰው የተፈጠረው በእግዚአብሔር አምሳል ነው ማለት ምን ማለት ነው? ከዚህ ዐረፍተ ነገር በርካታ ጠቃሚ እውነቶችን እንመለከታለን፡

  1. ሰው ከእንስሳት የተለየ ነው። በአንዳንድ በኩል ሲታይ ሰው በሥጋዊ አካሉ ከእንስሳት ጋር የሚመሳሰል ቢሆንም፥ በእግዚአብሔር አምላል የተፈጠረ ስለሆነ ከእንስሳት የተለየ ነው። 
  2. ሰው እግዚአብሔር ከፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ የተሻለ ነው። ከማናቸውም ፍጥረታት ሁሉ በጣም ተፈላጊ ነው። 
  3. ሰው በእግዚአብሔር አምሳል ተፈጠረ። እግዚአብሔር እንደ እኛ ዓይነት ሥጋዊ አካል ስለሌለው አካላዊ አለመሆኑ ግልጥ ነው። ይልቁንም አምሳልነቱ በሚከተሉት ነገሮች ነው፡-

ሀ. እግዚአብሔርም ሆነ ሰው ሁለቱም ስብዕና አላቸው። ይህም ማለት ያስባሉ፥ ያዝናሉ፥ ያቅዳሉ። 

ለ. እግዚአብሔርና ሰው ሁለቱም ክፉና ደጉን የመለየት የሥነ ምግባር እውቀት አላቸው። በመሆኑም ክፉውን ወይም ደጉን የመምረጥ ችሎታ አላቸው። 

ሐ. እግዚአብሔርና ሰው ሁለቱም ገዥዎች ናቸው። እግዚአብሔር በፍጥረቱ ሁሉ ላይ ገዥ ነው። ሰውም የእግዚአብሔር ፍጥረታት ሁሉ ገዥ ነው።

መ.እግዚአብሔርና ሰው ሁለቱም «መንፈስ» አላቸው። እግዚአብሔር መንፈስ ነው (ዮሐ. 4፡24 ተመልከት)። ሰውም ዘላለማዊ የሆነ መንፈስ አለው።

  1. ወንድና ሴት ሁለቱም እኩል የእግዚአብሔር አምሳልነት አላቸው። ወንድ ከሴት የተለየ የእግዚአብሔር አምሳልነት የለውም፤ የእግዚአብሔርን አምሳልነት በተመለከተ ሴትም ከወንድ ያነሰ የአፈጣጠር ልዩነት የላትም።

እኛ ሁላችንም በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠርን ስለሆንን በእግዚአብሔር ፊት ምን ያህል ክብር አለን?

ዘፍ.2 የሚያተኩረው በሰው ልጅ አፈጣጠር ላይ ነው። የመጀመሪያዎቹ ወንድና ሴት አዳምና ሔዋን ይኖሩበት ስለ ነበረው እጅግ ውብ ስፍራ ስለ ዔደን ገነት እናነባለን። እንደተገለጸው ከሆነ ዔደን ገነት መስጴጦምያ አካባቢ የነበረች ስፍራ ትመስላለች። እንዲሁም ሴት እንዴት ከወንድ ጎን እንደተሠራችም በዚህ ምዕራፍ ይናገራል።

በወንድና በሴት የአፈጣጠር ታሪክ እግዚአብሔር ለወንዶችና ለሴቶች ሁሉ በጋብቻ ውስጥ ያለው አሳብ ምን እንደሆነ እንመለከታለን። ሁለቱም በእግዚአብሔር አምሳል ስለተፈጠሩ፥ እኩልነት መኖር አለበት። አንድ ሥጋ ስለሚሆኑ፥ አንድነት መኖር አለበት። ሳይለያዩ እስከሞት ድረስ በአንድነት መቆየት አለባቸው። የቅርብ ጓደኛሞች መሆን አለባቸው። ቅርበታቸው ከተለመደው ቤተሰባዊ አቀራረብ ማለት አባትና እናት ከልጆቻቸው ጋር ካላቸው ግንኙነት እጅግ የበለጠ መሆን አለበት። ወንድ በመጀመሪያ ስለተፈጠረ ሚስት ለባሏ ታዛዥ መሆን ይገባታል።

ባልና ሚስት በኅብረታቸው ውስጥ አንዳችም የተሰወረ ነገር ሳይኖር ሙሉ በሙሉ ግልጥ መሆን አለባቸው። ይህም «ራቁታቸውን ነበሩ፤ አይተፋፈሩም ነበር» ከሚለው ቃል የሚታወቅ ነው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በዘፍጥረት 2 የተገለጸው የጋብቻ ሁኔታ ብዙ ሰዎች በጋብቻ ውስጥ የተለመደ ነው ብለው ከሚያስቡት ነገር በምን ይለያያል? ለ) የአንተ ወይም የወላጆችህ ጋብቻ በዘፍጥረት 2 ለትክክለኛ ጋብቻ ምሳሌነት ከቀረበው ከአዳምና ሔዋን ጋብቻ ጋር እንዴት የነጻጸራል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

2 thoughts on “ዘፍጥረት 1-2 የዓለም አፈጣጠር”

  1. ኤፌሶን 1፡3-14
    በክርስቶስ የሚገኝ መንፈሳዊ በረከቶች
    1ኛ. የሰማያዊ በረከት ፀጋና ሠላም
    2ኛ. ገና ሳንፈጠር ልጁ አድርጎን እኛን መምረጡን
    3ኛ. በበጎ ፍቃድ እንደወደደን ልጁን እንድንሆን አስድሞ መረጠን
    4ኛ. በክርስቶስ በማመናችን በመንፈስ ቅዱስ አትሞናል
    5ኛ. ክርስቶስ የርስታችን መያዣ ነው፡፡

  2. From Mulat Eticha
    Mathewes 28:1-8
    Jesus Has Risen
    After the Sabbath, at dawn on the first day of the week, Mary Magdalene and the other Mary went to look at the tomb. 2There was a violent earthquake, for an angel of the Lord came down from heaven and, going to the tomb, rolled back the stone and sat on it. 3His appearance was like lightning, and his clothes were white as snow. 4The guards were so afraid of him that they shook and became like dead men. 5The angel said to the women, “Do not be afraid, for I know that you are looking for Jesus, who was crucified. 6He is not here; he has risen, just as he said. Come and see the place where he lay. 7Then go quickly and tell his disciples: ‘He has risen from the dead and is going ahead of you into Galilee. There you will see him.’ Now I have told you.” 8So the women hurried away from the tomb, afraid yet filled with joy, and ran to tell his disciples.

Leave a Reply to Mulatu Eticha GumaCancel reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading