Site icon

የኦሪት ዘፍጥረት ታሪክ ቅደም ተከተልና አስተዋጽኦ፣ ልዩ ባሕሪያት እና ዓላማ

የኦሪት ዘፍጥረት ታሪክ ቅደም ተከተልና አስተዋጽኦ

የውይይት ጥያቄ፥ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት ዘፍ. 2፡4፤ 5፡1፤ 6፡9፣ 10፡1፤ 11፡10፤ 11፡27፤ 25፡12፤ 25፡19፤ 36፡1፥ 9፤ 37፡2። ሙሴ፡- «የ…..ታሪክ ይህ ነው» የሚላቸውን የተለያዩ ነገሮችን ዘርዝር።

ሙሴ ኦሪት ዘፍጥረትን በሚጽፍበት ጊዜ ግልጽ የሆነ አስተዋጽኦ ነበረው። መጽሐፉን ያቀናበረው «የ…ይህ ነው» በሚሉት ቃላት ዙሪያ ነበር። ብዙ ምሁራን ይህንን አከፋፈል የኦሪት ዘፍጥረትን አስተዋጽኦ ለመንደፍ ይጠቀሙበታል።

  1. መግቢያ፡- የነገሮች ሁሉ አፈጣጠር (ዘፍጥ. 1፡1-2፡3) 
  2. ከአይሁድ አባቶች በፊት የነበረው ዘመን (ዘፍ. 2፡4-11፡26)

ሀ) የሰማይና የምድር መፈጠር ታሪክ (ዘፍ. 2፡4-4፡26) 

ለ) የአዳም ትውልድ እና የልጆቹ ታሪክ (ዘፍ. 5፡1-6፡8) 

ሐ) የኖኅ ታሪክ (ዘፍ. 6፡9-9፡29) 

መ) የሴም፥ የካምና የያፌት ታሪክ (ዘፍ. 10፡1-11፡9)

ሠ) የሴም ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 11፡10-26) 

  1. የአይሁድ አባቶች ዘመን (ዘፍ. 11፡27-50)

ሀ) የታራ ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 11፡27-25፡1) 

ለ) የእስማኤል ትውልድ (ዘፍ. 25፡12-18) 

ሐ) የይስሐቅ ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 25፡19-35፡29)

መ) የዔሳው ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 36፡1-37፡1) 

ሠ) የያዕቆብ ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 37፡2-50፡26)

ሙሴ ኦሪት ዘፍጥረትን በዚህ ዓይነት ቢያቀናብረውም ለማስታወስ ቀላል የሆነ ሌላ የቅንብር መንገድ አለ። የሚከተለውን አስተዋጽኦ እየደጋገምህ አጥና ወይም በቃልህ ያዝ፡-

  1. ከአይሁድ አባቶች በፊት የነበረው ዘመን (ዘፍ. 1-11) 

ሀ. ፍጥረት (ዘፍ. 1-2) 

ለ. የሰው ልጅ በኃጢአት መውደቅ (ዘፍ. 3-5) 

ሐ. የጥፋት ውኃ በዓለም ላይ (ኖኅ) (ዘፍ. 6-9)

መ. የባቢሎን ግንብና የሰው ዘር መለያየት (ዘፍ. 10-11) 

  1. የአይሁድ የእምነት አባቶች ዘመን (ዘፍ. 12-50)

ሀ. አብርሃም (ዘፍ. 12-25) 

ለ. ይስሐቅ (ዘፍ. 24-26)

ሐ. ያዕቆብ (ዘፍ. 27-36) 

መ. ዮሴፍ (ዘፍ. 37-50)

ከዚህ በላይ ባለው አስተዋጽኦ ውስጥ ሁለት ነገሮችን ልብ በል፡- – በመጀመሪያ፥ ዘፍጥረት በሁለት ዓበይት ክፍሎች፥ ማለትም በዘፍጥረት 1-11 እንዲሁም በዘፍጥረት 12-50 እንደተከፈለ ልብ በል። የመጀመሪያው ክፍል የሚናገረው ስለ ጥንት ዘመን ሲሆን፥ ፍጥረታትን የመፍጠር ተግባር የተፈጸመው መቼ እንደሆነና ይህ ክፍለ ዘመን ምን ያህል ዓመታት እንደፈጀ ለማወቅ አንችልም። ዘፍ. 12-50 ደግሞ የሚናገረው ስለ አይሁድ ሕዝብ መመሥረትና ያንን ሕዝብ ስለ ጀመሩት አራቱ የእስራኤል አባቶች ታሪክ ነው።

ሁለተኛ፥ እያንዳንዱ ክፍል በአራት ንዑሳን ክፍሎች መከፈሉን ልብ ሰል። ከዘፍ. 1-11 ያለው የመጀመሪያው ክፍል ፍጥረትን፥ ውድቀትን፥ የጥፋት ውኃንና የባቢሎንን ግንብ የሚያጠቃልሉ አራት ክፍሎች አሉት። ከዘፍ. 12-50 ባለው ክፍል ደግሞ ትኩረት የተሰጣቸው አራት ዋና ዋና ሰዎች አሉ። ይህንን የዘፍጥረትን አስተዋጽኦ ብትከተል በመጽሐፉ ውስጥ የሚገኘውን ታሪክ ለማስታወስ ይረዳሃል። የኦሪት ዘፍጥረት ልዩ ባሕርያት በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ መጽሐፉን የበለጠ ለመረዳት ማዕከላዊ የሆኑና ሙሴ ያካተታቸው አንዳንድ ልዩ ነገሮች አሉ።

  1. ዘፍጥረት፥ እግዚአብሔር ከሰዎች ጋር ባለው ግንኙነት ዓላማውን ወደ ፍጻሜ ብዙ ጊዜ ለማድረስ ከተለመደው ባሕላዊ ሁኔታና ተግባር ተቃራኒ በሆነ አቅጣጫ እንደሚጓዝ ያሳያል። ይህ በተለይ የታየው እግዚአብሔር ከበኩሩ (ከመጀመሪያው ልጅ) ይልቅ ሁለተኛውን በመምረጡ ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ እንዳሉት በርካታ ባሕሉች አይሁድ የመጀመሪያ ልጅ ልዩ እንደሆነ በማመን፥ ከአባቱ ንብረት የሚበዛውን ክፍል መውረስ እንዳለበት ይስማሙ ነበር። እግዚአብሔር ግን በዚህ ሰው ሠራሽ ባሕል ራሱን አልወሰነም። ለምሳሌ፡- በዘፍጥረት ውስጥ እግዚአብሔር ከቃየን ይልቅ ሴትን፥ ከያፌት ይልቅ ሴምን፥ ከእስማኤል ይልቅ ይስሐቅን፥ ከዔሳው ይልቅ ያዕቆብን፥ ከቀሩት ወንድሞቻቸው ይልቅ ይሁዳንና ዮሴፍን፥ ከምናሴ ይልቅ ኤፍሬምን ሲመርጥ እንመለከታለን። ይህ ሁሉ የሚያስተምረን እግዚአብሔር በእኛ ባሕላዊ ግንዛቤ መሠረት ብቻ ለመሥራት የሚወሰን አለመሆኑን ነው። ይልቁንም ከእኛ ጋር ባለው ግንኙነት ሉዓላዊ ነው። የተለያዩ ግለሰቦችን የሚመርጠውና በአንዳንዶቹ በኃይል የሚሠራው በሌሉቹ ደግሞ ያንኑ ያህል በኃይል የማይሠራው እግዚአብሔር ራሱ ነው። ይህም እግዚአብሔር በሕይወታችን ላይ ባለው ኃይልና የበላይ ተቆጣጣሪነት ከፍተኛ አድናቆትን እንድንሰጠው የሚያደርግ እንጂ በአእምሮአችን ውስጥ ቅንዓትን የሚፈጥር መሆን የለበትም። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ብዙ ክርስቲያኖች ሌሉች ክርስቲያኖች ባለጸጎች መሆናቸውን ወይም እግዚአብሔር ከእነርሱ ይልቅ በኃይል እየተጠቀመባቸው መሆኑን ሲገነዘቡ የሚቀኑት ለምንድን ነው? ለ) ሕይወታችንን ለእግዚአብሔር ዕቅድ አሳልፎ ስለመስጠት የሚያስተምረን ነገር ምንድን ነው? ሐ) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በጣም አስፈላጊው ነገር፥ እግዚአብሔር ለሰጠን ስጦታዎችና ችሉታዎች ወይም ሥራዎች ታማኝ መሆን ነው፥ ወይስ በሰዎች ላይ ታላቅ መሪ መሆን? መልስህን አብራራ።

  1. በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ ተምሳሌታዊ ትርጉም ያላቸው አንዳንድ ቁጥሮች ይገኛሉ። የሚከተሉትን ቁጥሮች ተመልከት፡- 

ሀ) አሥር – በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ አሥር ዋና ዋና ክፍሎች አሉ፤ (አሥር ጊዜ «የ … ይህ ነው» ታሪኮች) እንዲሁም በዘፍጥረት 5 ና 11 «አሥር» ትውልዶችን የሚጠቅሱ ትንተናዎች እናገኛለን»። ለአይሁድ አሥር የምሉዕነት ተምሳሌት ነው።

ለ) ሰባት – ሰባት የፍጥረታት ሥራ የተከናወኑባቸው ቀናት ከመኖራቸውም፥ በምዕራፍ 4 ውስጥ በሚገኘው የትውልዶች ታሪክ ውስጥ የሚገኙ ሰባት ስሞች፥ በጥፋት ውኃ ታሪክ ውስጥ የሚገኙ በርካታ ሰባት ቁጥሮች፣ ለአብርሃም የተገቡ ሰባት ቃል ኪዳኖች፥ በግብፅ ውስጥ የደረሱ ሰባት የጥጋብና ሰባት የራብ ዓመታት እናገኛለን፡፡ እንዲሁም 70 (7 ጊዜ 10) የኖኅና የያዕቆብ ዝርያዎች ናቸው። ሰባት ብዙ ጊዜ የፍጹምነት ምሳሌ ነው።

ሐ) አሥራ ሁለት – የያዕቆብና የእስማኤል ነገዶች እያንዳንዳቸው አሥራ ሁለት ነገዶች ነበሩ (ዘፍ. 25፡16፤ 49፡28)። 

መ) አርባ፡- በጥፋት ውኃ ታሪክ ውስጥ የተለያዩ የ40 ቁጥር ክፍፍሎች እናያለን (ዘፍ. 6-9)። በኋላም እስራኤላውያን 40 ዓመታት በምድረ በዳ እንደተንከራተቱ እናነባለን። አንድ ሰው ብሉይ ኪዳንን በሚያጠናበት ጊዜ እነዚህ ቁጥሮች ለአይሁድ የተለዩ እንደሆኑ ግልጽ እየሆነለት ይመጣል። ለምሳሌ 40 ቁጥር የፍርድና የፈተና ጊዜ ይመስላል (ለምሳሌ፡- ኢየሱስ በምድረ በዳ ለ40 ቀናት ተፈትኖአል)። ሰባት ማለት ደግሞ የተሟላ ወይም ፍጹም ማለት ነው፤ (ለምሳሌ፡- በዮሐንስ ራእይ መንፈስ ቅዱስ ሰባቱ የእግዚአብሔር መናፍስት ተብሎ ተጠርቷል)።

  1. በዮሐንስ ራእይ የመጨረሻ ምዕራፎች የሚገኙት በተለይም መንግሥተ ሰማያትን የሚገልጡት ሥዕላዊ መግለጫዎች ከኦሪት ዘፍጥረት የመጀመሪያ ሦስት ምዕራፎች ስለ ዔደን ገነት ከተነገሩ መግለጫዎች የተወሰዱ መሆናቸው ትኩረትን የሚስብ ነው። እነዚህ መጻሕፍት የተጻፉት በ1500 ዓመታት ልዩነት መካከል ቢሆንም ይህን የመሰለ ግንኙነት በመካከላቸው መታየቱ፥ እግዚአብሔር የመጽሐፍ ቅዱስ ሁሉ ጸሐፊ መሆኑን የሚያሳይ ነው። 

የኦሪት ዘፍጥረት ዋና ዓላማ

የመጽሐፍ ቅዱስን አጠቃላይ ዓላማ ብንመለከት፥ ኢየሱስ ክርስቶስን መግለጥ ነው ለማለት እንችላለን። እርሱ «የእግዚአብሔር ቃል» ነው ( ዮሐ. 1፡1-4፤ ዕብ. 1፡1-3)። «ኢየሱስ ክርስቶስ በብሉይ ኪዳን ተሰውሮአል፤ በአዲስ ኪዳን ግን ተገልጦአል» የሚል አንድ አባባል አለ።

በሌላ አባባል የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በትንቢቶች አማካይነት የኢየሱስን መምጣት አሻግረው ተመለከቱ። እንዲሁም በሰዎች፥ በድርጊቶችና በነገሮች ሁሉ ውስጥ የመሢሑ መምጣት ሥዕላዊ መግለጫ ነበር። ስለሆነም ከኦሪት ዘፍጥረት ጀምሮ የኢየሱስ ክርስቶስን መገለጥ አጀማመር እናያለን። በዘፍጥረት ስለ ኢየሱስ የተነገሩ ትንቢቶችን አጀማመር እንመለከታለን። በአንዳንድ ታሪኮች ውስጥም የተደበቁ የኢየሱስ ተምሳሌቶች ወይም ሥዕላዊ መግለጫዎች አሉ። ብሉይ ኪዳንን ስናጠና እነዚህም ትንቢቶችና አምሳያዎች መፈለግ አለብን። ይህ ከኦሪት ዘፍጥረት ጀምሮ እስከ ዮሐንስ ራእይ የሚቀጥል «የድነት (ደኅንነት) መስመር» በመባል ይታወቃል።

ነገር ግን ሙሴ ፔንታቱክን የጻፈበት ዋና ዓላማ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ያደረገውን «ቃል ኪዳን» ለመግለጥ ነበር። ፔንታቱክና መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳት መሠረታዊ የሆነው አሳብ ይህ ቃል ኪዳን ነው፤ ስለዚህ የኦሪት ዘፍጥረት ማዕከላዊ እውነቶች የሚያተኩሩት ቃል ኪዳንን በሚመለከት አሳብ ላይ ነው። ዘፍጥረት 1-11 ከተለዩ ሕዝቦች ጋር ቃል ኪዳን ያስፈለገበትን ምክንያት ይናገራል። የሰው ልጅ በአጠቃላይ ፈጣሪውን ክዶ ኃጢአትን እንዴት እንደመረጠ ይናገራል። ዘፍ. 12-50 ደግሞ እግዚአብሔር ከአንድ ሰውና ከቤተሰቡ ጀምሮ አይሁድ ተብሎ የተጠራ አንድን የተለየ ሕዝብ እንዴት እንደመረጠ ይገልጻል። እግዚአብሔር ዓለምን ወደ ራሱ ለመመለስ የፈለገው በእነርሱ በኩል ነበር።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በእግዚአብሔርና በሰው መካከል ያለው የቃል ኪዳን አሳብ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ወይም በአዲስ ኪዳን የሚታየው እንዴት ነው? ለ) የእስራኤል ሕዝብና የቤተ ክርስቲያን ዓላማ የሚመሳሰለው እንዴት ነው? ሐ) እግዚአብሔር አብርሃምን በመረጠው ጊዜ የነበረውን ዓላማ ዛሬ ቤተ ክርስቲያንህ እንዴት እየፈጸመችው ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version