የእግዚአብሔር ሕዝብ በባርነት ቀንበር ሥር መሆን እና እግዚአብሔር ሕዝቡን ከባርነት ለማውጣት መሪ መጥራቱ (ዘጸአት 1-4)

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በአሁኑ ጊዜ አንተም ሆንክ በኢትዮጵያ ያሉ ሌሎች ክርስቲያኖች የምትጋፈጧቸው የመንፈሳዊ ውጊያ ክፍል የሆኑ ነገሮችን ዘርዝር። ለ) ብዙ ክርስቲያኖች እየተሸነፉ ያሉት እንዴት ነው? ሐ) እግዚአብሔር ለአንተና ለቤተ ክርስቲያንህ በእነዚህ ነገሮች ላይ ድልን ሲሰጥ ያየኸው እንዴት ነው?

ክርስቲያን በመንፈሳዊ ውጊያ ውስጥ መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምራል። ይህ ውጊያ በመጨረሻ በእግዚአብሔርና በሰይጣን መካከል በከፍተኛ ደረጃ የሚጧጧፍ ነው። ውጊያው ሰይጣንና የእግዚአብሔር ሕዝቦችንም ያሳትፋል። ሰይጣን የእግዚአብሔርን ሕዝቦች ለመጨቆን ብዙ የተለያዩ ነገሮችን ይጠቀማል። ሰዎች የሌሎች ባሪያዎች እንዲሆኑ በማድረግ ሥጋዊ እስራትን ሊያመጣ ይችላል። ሰዎችን የሚጨቁንና ወንጌልን የሚቃወም መንግሥትንም መሣሪያ ሊያደርግ ይችላል። የእግዚአብሔር ሕዝብ ከእውነት ዞር እንዲሉ ለማድረግ የሚፈልጉ ሐሰተኛ ሃይማኖቶችንም መጠቀም ይችላል። ብዙ ጊዜ ክርስቲያኖች ይህን በመሰለ መንፈሳዊ ውጊያ ውስጥ ሲገቡ እግዚአብሔር የተዋቸውና የሚሸነፉም ይመስላቸዋል፤ ይህ ግን እውነት አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስ አሸናፊው ሁልጊዜ እግዚአብሔር እንደሆነ ይናገራል። እርሱ መንግሥታትን፥ መሪዎችን፥ ሐሰተኛ ሃይማኖቶችን፥ ሰይጣንና አጋንንትን ሁሉ የሚቆጣጠር ነው። አምላካችን ገዥ ነው። እግዚአብሔር በራሱ ጊዜ ኃይሉን በጠላቶቹ ሁሉ ላይ ይገልጻል። አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔር አንዳዶችን ሲያነሣና ሌሉችን ሲጥል በሕይወት ዘመናችን ኃይሉን እናያለን። በሌላ ጊዜ ደግሞ የእግዚአብሔር ኃይል ጠላቶቹን ሁሉ እስከሚጥልበት፥ እስከመጨረሻው ጊዜ ድረስ ተሰውሮ ይቆያል። 

ይህ የኦሪት ዘጸአት የመጀመሪያ ክፍል ታሪክ እግዚአብሔር ሰይጣንን ለማሸነፍ እንዴት እንደሠራ ይነግረናል። እግዚአብሔር የተመረጡትን ሕዝቦቹን ከባርነት ነፃ ለማድረግ የሠራውን ሥራ ይተርክልናል። እግዚአብሔር ዓላማውን ለመፈጸም ተፈጥሮንና መሪዎችን በመቆጣጠር ረገድ በሕዝቡ ሠርቷል። 

የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 1-12 አንብብ። ሀ) የእግዚአብሔር ሕዝብ የነበሩበት ሁኔታ ምን ይመስል ነበር? ለ) እግዚአብሔር ሙሴን ለመሪነት ለማዘጋጀት እንዴት ሠራ? ሐ) የተመረጠ መሪ መሆኑን ለማረጋገጥ እግዚአብሔር ለሙሴ ያሳያቸው ሦስት ተአምራት ምንድን ናቸው? መ) ሙሴ የእስራኤልን ሕዝብ ከባርነት ነፃ ለማውጣት በሚሞክርበት ጊዜ ያገኘው የመጀመሪያ ውጤት ምን ነበር? ) እግዚአብሔር ግብፃውያን፥ ሕዝቡን (እስራኤላውያንን) ይለቁ ዘንድ ያመጣባቸው አሥር መቅሠፍቶችን ዘርዝር። ረ) እነዚህ መቅሠፍቶች በግብፅ ላይ በወረዱ ጊዜ እግዚአብሔር ለሕዝቡ ለእስራኤል ያለውን እንክብካቤ እንዴት ገለጠ? ሰ) የፋሲካ በዓል ዓላማ ምን ነበር? ቀ) ከእነዚህ ቁጥሮች ስለ እግዚአብሔር የምንማራቸው ነገሮች ምንድን ናቸው? ሸ) እስራኤላውያን ግብፃውያንን «የበዘበዙት» በምን መንገድ ነበር?

፩. ዘጸአት 1. የእግዚአብሔር ሕዝብ በባርነት ቀንበር ሥር መሆን 

ሀ. እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ስለባረካቸው ተባዙ (ዘጸ. 1፡1-7)

ኦሪት ዘጸአት የሚጀምረው የዘፍጥረትን የመጨረሻ ታሪክ በክለሳ መልክ አጠቃልሉ በማቅረብ ነው። ዘጸአት ፔንታቱክ ተብሎ የሚታወቀው መጽሐፍ ትልቅ ክፍል መሆኑን አስታውስ።

የእስራኤል ሕዝብ ወደ ግብፅ የወረዱት ለምንድ ነው? በባርነትስ የወደቁት እንዴት ነበር? እነዚህ የዘጸአት ምዕራፍ 1 ሁለት ዋና ዋና ጥያቄዎች ናቸው። እስራኤላውያን ወደ ግብፅ የወረዱበት ምክንያት የያዕቆብ ዝርያዎች፥ የአሥራ ሁለቱ ነገድ መሪዎች በሆኑት አሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆች መሪነት በዚያ ለመኖር መሆኑን ሙሴ ያስታውሰናል። መጀመሪያ ወደ ግብፅ በደረሱ ጊዜ 70 ሰዎች ብቻ ነበሩ። እግዚአብሔር ግን ለአብርሃም የገባውን የተስፋ ቃል አስቦና አክብሮ ታላቅና የተፈራ ሕዝብ አድርጎ አበዛቸው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ዘፍ. 12፡2 አንብብ። ሀ) እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠው ተስፋ ምን ነበር? ለ) ይህ ተስፋ በዘጸ. 1 የተፈጸመው እንዴት ነው? ሐ) ስለ እግዚአብሔርና ስለ ተስፋ ቃሉቹ ይህ ምን ያስተምረናል? – በዘጸ. 1፡6 ና 1፡7 መካከል በመቶ የሚቆጠሩ ዓመታት ልዩነት አለ። እስራኤላውያን በሙሴ መሪነት ከግብፅ ለመውጣት በተንቀሳቀሱበት ጊዜ ቁጥራቸው ከሚሊዮን በላይ ይሆን እንደነበር ምሁራን ይገምታሉ። (በዘጸ. 12፡37 ሴቶችና ልጆች ሳይቆጠሩ ቁጥራቸው ስድስት መቶ ሺህ እንደነበር ተጽፏል። 

ለ. እስራኤላውያን በባርነት ቀንበር ሥር የወደቁና የተጨቆኑ ነበሩ (ዘጻ.1፡8-22)

በዘጸ. 1፡8 እንደምናነበው፥ ዮሴፍን የማያውቅ አዲስ ንጉሥ ተነሥቶ የእግዚአብሔርን ሕዝብ መጨቆን ጀመረ። ይህ ነገር የሆነው በግምት ዮሴፍ ከሞተ ከ200 ዓመታት በኋላ ነበር። በዚህ ጊዜ ግብፃውያን ሐይክሶላውያንን አሸንፈው አገራቸውን እንደገና ማስተዳደር ጀምረው ነበር። የውጭ ዜጎች በአገልግሎት ሥልጣን እንዳይኖራቸው በመደረጉ፥ አይሁዶች በባርነት ቀንበር ተያዙ። ምሁራን ይህ ጭቆና የተጀመረው በ1550 ዓ.ዓ. ነው ይላሉ። ይህም ማለት አይሁድ ከባርነት ነፃ እስከ ወጡበት 1450 ዓ.ዓ. ድረስ፥ ለ100 ዓመታት በባርነት ቀንበር ሥር ቆይተዋል ማለት ነው።

ግብፆች አይሁዳውያንን ከማባረር ይልቅ ከተሞችን ለመገንባት ሊጠቀሙባቸው መረጡ። ስለዚህ ግብፃውያን አይሁዳውያንን ባሪያዎች አደረጉአቸው። አይሁዳውያን በግብፅ ውስጥ የሚገኙትን ከባድ ሥራዎች ሁሉ ለመሥራት ተገደዱ። ነገር ግን ቁጥራቸው እጅግ እንዳይበዛና ግብፃውያንን ሥጋት ላይ እንዳይጥሉአቸው የግብፅ ንጉሥ እስራኤላዊ የሆነ ወንድ በሚወለድበት ጊዜ እንዲገደል አዋላጆችን አዘዘ። አዋላጆች ግን ይህንን ከማድረግ ተቆጠቡ።

በባርነት ቀንበር ሥር በነበሩበት ጊዜ እንኳ የእግዚአብሔር እጅ አልተለያቸውም ነበር። እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ስለባረከ የግብፃውያን ጥረት ሁሉ ከንቱ ሆኖ ቀረ። (ቁጥራቸው እጅግ እየጨመረ ሄደ፤)

የውይይት ጥያቄ፥ በዚህ ውስጥ ስለታየው የእግዚአብሔር ኃይል ምን እንማራለን?

፪. እግዚአብሔር ሕዝቡን ከግብፅ ለማውጣት አንድ መሪን ጠራ (ዘጸ. 2-4)። 

የሙሴ ሕይወት በሦስት ዘመናት ሊከፈል ይችላል፡- ሀ) ሙሴ እንደ አንድ ግብፃዊ ለ40 ዓመታት ሠልጥኗል። ለ) እግዚአብሔር ሙሴን በምድረ በዳ ለ40 ዓመታት አሠለጠነው። ሐ) ሙሴ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ለ40 ዓመታት መርቷል።

ሀ. ሙሴ እንደ አንድ ግብፃዊ ሠልጥኗል (ዘጸ. 2፡1-10)።

ስለ ሙሴ የመጀመሪያ 40 ዓመታት የተጻፈው ነገር በጣም ጥቂት ነው። በሕፃንነቱ በግብፃውያን እጅ ከመገደል እግዚአብሔር በተአምር የጠበቀው ሰው ነው። ወላጆቹ ገና ከመወለዱ ጀምሮ ልዩ ልጅ እንደነበር የተረዱ ይመስላል። ምክንያቱም ያማረ ሕፃን፥ ወይም ተራ ያልሆነ ልጅ ተብሎ ተጠርቷል፤ (ዕብ. 11፡23 ተመልከት)። የሙሴ ወላጆች አቅማቸው የፈቀደውን ያህል ከሸሽጉት በኋላ፥ ሊደብቁት ከማይችሉበት ደረጃ ላይ ሲደርሱ፥ ይጠብቀው ዘንድ ለእግዚአብሔር አሳልፈው ሰጡት፤ በእግዚአብሔርም ታመኑ። በቅርጫት አድርገው በዓባይ ወንዝ ላይ አኖሩት። የእግዚአብሔር ጥበቃ በዚህ ሰው ላይ ምን ያህልና እንዴት እንደነበረ አስተውል፡

  1. እግዚአብሔር ሁኔታዎችን ስለተቆጣጠረ፥ የፈርዖን ሴት ልጅ በቅርጫት ተደርጎ በተቀመጠበት ወንዝ ዳር ሙሴን አገኘችውና እንደ ልጇ ልታሳድገው ወደ ቤቷ ወሰደችው፡፡
  2. የሙሴ እናትና እኅት በአስተዳደጉ ላይ ተጽዕኖ እንዲያሳድሩ እግዚአብሔር ሁኔታዎችን አመቻቸ። ሙሴ ዕብራዊ መሆኑን የተማረው ከየት ነበር? ስለ እግዚአብሔር የተማረውስ የት ነው? ከእናቱና ከእኅቱ እንደሆነ አይጠረጠርም። 

የውይይት ጥያቄ፥ ወንጌልን ለልጆቻችን ስለማስተማር አስፈላጊነት ይህ ምን ያስተምረናል?

ሙሴ በግብፅ ያሳለፈው አብዛኛው ነገር አልተገለጸም። የምናውቀው ነገር ቢኖር በግብፅ ትምህርትና ጥበብ ሁሉ ማደጉን ነው (የሐዋ. 7፡22፤ ዕብ. 11፡24-27 ተመልከት)። ከግብፃውያን ትምህርት ቤቶች ከሁሉ በተሻለው ውስጥ ከንጉሣውያን ቤተሰብ ልጆች ጋር ሳይማር አልቀረም። አንዳንድ ምሁራን የግብፅ ንጉሥ ለመሆን በሚችልበት መስመር ላይ ነበር ይላሉ።

ሙሴ በግብፅ የተማረው ትምህርት በኋላ ፔንታቱክን ለመጻፍ ተግባሩ ጠቅሞታል።

ለ. ሙሴን በምድረ በዳ ውስጥ እግዚአብሔር አሠለጠነው።

ሙሴ የእስራኤልን ሕዝብ እንዲመራ እግዚአብሔር እንደፈለገው ሳያውቅ አልቀረም። ነገር ግን እግዚአብሔር እስኪሠራ መጠበቅ ሲገባው የራሱን እርምጃ በመውሰድ፥ አንዱን እስራኤላዊ ለመርዳት ሲሞክር አንድ ግብፃዊን ገደለ። ከዚያም በምድያን ወዳለው ምድረ በዳ ሄዶ በኋላ ልጁን የዳረለትን ዮቶርን በእረኝነት በማገልገል 40 ዓመታት አሳለፈ። ሙሴ በነፃነት ወደ ግብፅ ለመመለስ የቻለው በእርሱ ጊዜ የነበረው ንጉሥ ከሞተ በኋላ ብቻ ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ነፃ ለማውጣት ያን ያህል ረጅም ጊዜ የቆየው ለምን ይመስልሃል? ለ) ሙሴ ከመምረጡ በፊት ለ40 ዓመታት የቆየውስ ለምንድን ነው? ሐ) የሙሴ ታሪክ ስለ መንፈሳዊ መሪነት ምን ያስተምረናል?

ሙሴ በምድረ በዳ የተማረውን ነገር በኋላ እግዚአብሔር ተጠቅሞበታል። ሙሴ የተዘጋጀው በመንፈሳዊ ሕይወቱ ብቻ ሳይሆን፥ በሥጋዊ ረገድም በምድረ በዳ መኖር እንዴት እንደሚቻል ተምሯል።

ስለዚህ በምድረ በዳ ስለመኖር አንዳችም እውቀት የሌላቸው አይሁዳውያን ወገኖቹን ለ40 ዓመታት በምድረ በዳ ለመምራት በቅቷል።

፫. የእስራኤል ሕዝብ መሪ እንዲሆን እግዚአብሔር ሙሴን ጠራው (ዘጸአት 3-4)።

እግዚአብሔር በመጀመሪያ ሙሴን የተገናኘበት መንገድ አስገራሚ ትዕይንት የታየበት ነበር። እሳት እየነደደበት ነገር ግን ተቃጥሎ የማያልቅ ቁጥቋጦ ባለበት ስፍራ ተገናኘው። እግዚአብሔር ለሙሴ ኃይሉን ሊያሳየው ፈልጎ ነበር። ደግሞም እሳት ብዙ ጊዜ የእግዚአብሔር ሕልውና ምልክት ነው፤ (ሕዝ. 1፡4-5፥ 27 ተመልከት)። የእግዚአብሔር ቅድስናም ምልክት ነበር። በፊቱ በቆመ ጊዜ በአይሁድ ልማድ መሠረት ጫማውን በማውለቅ አክብሮቱን እንዲገልጥ እግዚአብሔር ለሙሴ ነገረው።

በሙሴ ጥሪ ውስጥ የሚከተሉትን ነገሮች አስተውል፡-

1) እግዚአብሔር ሙሴን መረጠውና እስራኤልን ከባርነት ነፃ ለማውጣት መሪ እንደሚሆን ነገረው። 

2) እግዚአብሔር ለሙሴ «እኔ እኔ ነኝ» ወይም ያህዌ በማለት ልዩ ስሙን ነገረው። ይህ ስም የእግዚአብሔርን ኃይልና በሕዝቡ በእስራኤል ላይ ያለውን የበላይ ተቆጣጣሪነት የሚገልጽ ነው። 

3) ሙሴ በእግዚአብሔር የተመረጠ መሪ መሆኑን ያውቁ ዘንድ ለእስራኤላውያን እንዲያሳያቸው ሦስት ምልክቶችን ሰጠው፡

ሀ) እግዚአብሔር የሙሴን በትር ወደ እባብ፥ እባቡን ደግሞ መልሶ ወደ በትር ለወጠው። 

ለ) እግዚአብሔር የሙሴን እጅ በለምጽ መታውና ወዲያው ደግሞ ወደ ተለመደው መልኩ መለሰው። 

ሐ) እግዚአብሔር ለሙሴ፥ «አንተ በእኔ የተመረጥክ መሪ መሆንህን እስራኤላውያን ካላመኑ ከዓባይ ወንዝ ውኃን ውሰድና ወደ ደምነት ለውጠው» አለው።

4) ሙሴ በ40 ዓመታት የምድረ በዳ ቆይታው ጊዜ በጣም ተለውጦ ነበር በራሱ ብርታት መቆሙና መተማመኑ አብቅቶ ነበር። ስለዚህ አሁን ፈራና እኔ መናገር አልችልም ብሎ ለእግዚአብሔር መልስ ሰጠ። ይህም ሙሴ በእግዚአብሔር ለመታመን ፈቃደኛ አለመሆኑን የሚያሳይ ምልክት ነበር። እግዚአብሔር ለሙሴ ጥያቄዎች በሙሉ በትዕግሥት መልስ ሰጠና ለመታዘዝ ፈቃደኛ አለመሆኑን ሲያይ ተቆጣ። እኛም ብንሆን ያልገባንን ነገር ከእግዚአብሔር የመጠየቅ መብት አለን። ነገር ግን እግዚአብሔርን ለመታዘዝ እንድንችል ሁልጊዜ ጥንቃቄ ማድረግ አለብን። ከዚያም ወንድሙ አሮን ከእርሱ ጋር እንደሚሠራና አፈቀላጤው እንደሚሆን እግዚአብሔር ለሙሴ ነገረው። 

5) ሙሴ ሊነጻና እግዚአብሔርን የመታዘዝ አስፈላጊነትን ሊማር ይገባው ነበር።

ወንዶች ልጆች ሁሉ እንዲገረዙ እግዚአብሔር ያዘዘ ቢሆንም (ዘፍጥ. 17 ተመልከት) ሙሴ ግን አልታዘዘም ነበር። ወንዶች ልጆቹ አልተገረዙም ነበር። ስለዚህ እግዚአብሔር ሊፈርድበት ተዘጋጀ። እግዚአብሔር ሙሴን በአንድ ዓይነት በሽታ የመታው ይመስላል። የሙሴ ሚስት የወሰደችው ፈጣን እርምጃ ሙሴን ከሞት አዳነው። ልጇን ገረዘች። «አንተ ለእኔ የደም ሙሽራ ነህ» ብላ የተናገረችውን ቃል ምንነት መረዳት በጣም አስቸጋሪ ነው። አንዳንድ ምሁራን እንዲህ ይላሉ፡- ሲፓራ አይሁዳዊት ስላልነበረች ይህ የግዝረት ባሕል ለእርሷ እንግዳ ነበር፤ ስለዚህ ሙሴ ልጆቹን እንዲገርዝ ሳትፈቅድ ቀረች። ነገር ግን ሙሴን ለማዳን ስትል ግትርነትዋን ተወችና ልጇን ገረዘች። ይህንን በማድረጓ በመጀመሪያ ለሙሴ የገባችውን ቃል ኪዳን በማደስ እንደ አዲስ ሙሽራ ቆጠረችው። ይህንን ያረጋገጠው በመገረዙ ምክንያት ከልጇ የፈሰሰው ደም ነው። ሆኖም የዚህ ሐረግ ትርጉም ግልጽ አይደለም። የታሪኩ ትርጉም ግን ግልጽ ነው። በታሪኩ ውስጥ ሁለት ዋና ዋና ነገሮች ትኩረት ተሰጥቷቸዋል፡-

ሀ) ሙሴ የእግዚአብሔር ሕዝብ መሪ ይሆን ዘንድ መሆን ቤተሰቡም መንጻትና እግዚአብሔርን ለማገልገል የተዘጋጀ ነበረበት። ግዝረት እግዚአብሔር ደስ የማያሰኙ ነገሮችን ሁሉ ከሕይወት የማስወገድና ለእግዚአብሔር ቃል ኪዳን አልፎ የመሰጠት ምልክት ነው። ለ) ምንም ያህል ትንሽና ኢምንት ቢመስሉም እንኳ ለእግዚአብሔር ትእዛዛት ሙሉ ለሙሉ መታዘዝ አስፈላጊ እንደሆነ ሙሴን ማስተማር አስፈላጊ ነበር።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እነዚህን ሁለት እውነቶች ማወቅ ለሙሴ ለምን ያስፈልገው ነበር? ለ) ዛሬም ቢሆን የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እነዚህን እውነቶች ማስታወስ ለምን ይጠቅማቸዋል? ሐ) በዚህ ዘመን ያሉ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እግዚአብሔርን በከፊል ብቻ የሚታዘዙባቸውን ሁኔታዎች ግለጽ። መ) ይህ ነገር በአመራራቸው ላይ እንዴት ተጽዕኖ ያደርጋል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading