የእግዚአብሔር ሕዝብ ነጻነት (ዘጸ. 5-12) 

በዚያን ጊዜ ግብፅ በምድር ላይ ካሉ መንግሥታት ሁሉ በላይ የሆነ ኃያል መንግሥት ነበር። ነገር ግን የሰዎች ሁሉ ፈጣሪ ከሆነው ከእግዚአብሔር የሚበልጥ ታላቅነት ነበረውን? እነዚህ ምዕራፎች እግዚአብሔርን ወክሎ በሚናገረው በሙሴና በግብፅ መሪ በነበረው በፈርዖን መካከል የተፈጠረውን ውዝግብ ያመለክታሉ። ምናልባት ሙሴ ከዚህ የግብፅ ንጉሥ ጋር በቂ ትውውቅ ያለውና አብረው ያደጉም ሳይሆኑ አይቀሩም። (ማስታወሻ፡- ፈርዖን የሚለው ቃል የአንድ የግብፅ ንጉሥ ስም አይደለም። የግብፅ መሪ የሚጠራበት የሥልጣን ስም ነው። «ንጉሥ» ከሚለው ቃል ጋር ተመሳሳይ ነው) በመጀመሪያ ፈርዖን ታላቅ ኃይል ነበረው። ሙሴ የእስራኤልን ሕዝብ እንዲለቅ ሲጠይቀው ፈርዖን እንዲህ ሲል መለሰ፡- «ቃሉን እሰማ ዘንድ፥ እስራኤልን እለቅቅ ዘንድ እግዚአብሔር ማን ነው? እግዚአብሔርን አላውቅም፥ እስራኤልንም ደግሞ አልለቅም» (ዘጸ. 5፡2)። ይህ ጥያቄ ከቀረበለት በኋላ ፈርዖን በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ቀንበርን ጨመረ።

ከዚያም እግዚአብሔር በግብፅ ላይ አሥር መቅሠፍቶችን ላከ። በአሥሩ መቅሠፍቶች ታሪክ ውስጥ የሚከተሉትን ነገሮች አስተውል፡-

ሀ. የግብፅ አስማተኞች ሊሠሩ የቻሉት ሙሴ ከሠራቸው ተአምራት ከፊሎቹን ብቻ ነበር። ሰይጣን ብዙ ኃይል ስላለው፥ ተአምራትን ማድረግ ይችላል። የሙሴ ተአምር፥ የግብፅ አስማተኞች በመጨረሻ ይህንን ማድረግ የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነው እስኪሉ ድረስ፥ ከእነርሱ ተአምር የሚበልጥ ነበር (ዘጸ. 8፡19 ተመልከት)። በመጀመሪያዎቹ ሁለት መቅሠፍቶች የግብፅ አስማተኞች የሙሴን ተአምራት አስመስለው አሳዩ፡ በሦስተኛው መቅሠፍት ላይ ግን ማስመሰል አልቻሉም። ከአራተኛው መቅሠፍት ጀምሮ ችግሩ የደረሰው በግብፃውያን ላይ ብቻ ነበር። እግዚአብሔር ስለጠበቃቸው በእስራኤላውያን ላይ የመቅሠፍቱ ችግር አይደርስም ነበር።

ለ. ፈርዖን ከእግዚአብሔር ዘንድ ተጨማሪ ፍርድን ያስከተለበትና በመጨረሻም በበኩር ልጁ ላይ ሞትን ያመጣው የልብ ድንዳኔ ቀስ በቀስ በሕይወቱ እየጨመረ ሄደ። መጽሐፍ ቅዱሳችን የሚናገረውን ነገር በትክክል ከተመለከትን፥ የሚከተሉትን ነገሮች እናገኛለን፡- 1) ፈርዖን በሕዝቡ ላይ የደረሱትን አምስት መቅሠፍቶች አስቀድሞ ቢመለከትም፥ ልቡን አደነደነ፤ (ዘጸ. 8:15፥32)። ፈርዖን እያወቀ እውነትን አልተቀበለም። 2) ከዚያም እግዚአብሔር የፈርዖንን ልብ የበለጠ አደነደነው (ዘጸ. 9፡12፤ 10:1፥ 27)። 

ከዚህ ታሪክ ውስጥ በጣም አስፈላጊ የሆነ መንፈሳዊ እውነት ለማየት እንችላለን። እግዚአብሔር በመጀመሪያ የሰውን ልብ በማደንደን ፍርድን በሰው ሕይወት ላይ አያመጣም፤ ነገር ግን በንስሐ ለመመለስ ወይም እግዚአብሔርን ለመታዘዝ እምቢ በማለት ልቡን ማደንደን የሚጀምረው ግለሰቡ ራሱ ነው። ያ ግለሰብ ባለመታዘዝና በፍርድ ለመኖር ሲወስን፥ እግዚአብሔር ሰውዬውን በጀመረው የልብ ድንዳኔ እንዲገፋበት ያደርገዋል። እግዚአብሔር ልቡን ይበልጥ እያደነደነው ሲሄድ፥ ሰውዬው ማመን ወደማይችልበት ደረጃ ላይ ያደርሳል። (በሮሜ 1፡24-28 ልባቸውን ያደነደኑና በእግዚአብሔር የተፈረደባቸው ሰዎች ለምሳሌ ታገኛለህና ተመልከት)።

የውይይት ጥያቄ፥ በዚህ ሁኔታ ልባቸው የደነደነባቸውን ሰዎች አስተውለህ ታውቃለህን? ምሳሌ ስጥ።

ሐ. መቅሠፍቶቹ ለፈርዖን፥ ለግብፃውያንና ለእስራኤላውያን የእግዚአብሔር ኃይል ምልክቶች ነበሩ።

መ. እግዚአብሔር በግብፃውያን ላይ ፍርድን ለማምጣት ተፈጥሮአዊ መቅሰፍቶችን ተጠቀመ። እግዚአብሔር ተፈጥሮአዊ የሆኑ የአካባቢያችን ነገሮች ሁሉ ተቆጣጣሪ ነው፡፡ እንደ እንቁራሪት፥ ውኃ፥ ድርቅ፥ በሽታ ወዘተ.።

ሠ. መቅሠፍቶቹ በሙሉ ፊታቸውን ያዞሩት በፈርዖን ላይ ብቻ ሳይሆን፥ በግብፅ አማልክትም ላይ ነበር። ግብፃውያን የዓባይን ወንዝ ከብቶችን፥ ወዘተ ያመልኩ ነበር። ግብፃውያን የተደገፉባቸውና ያለማቋረጥ ያመለኩአቸው የነበሩ አማልክት የማይጠቅሙና ዋጋ የሌላቸው ነበሩ። ፈርዖንም እንደ አምላክ የሚታይበት ሁኔታ ነበር። ሆኖም ልጁ በተገደለበት ጊዜ ኃይል የሌለው መሪ መሆኑ ታወቀ። እግዚአብሔር ከግብፅ አማልክት ሁሉ በላይ ኃያል ስለሆነ፥ እስራኤላውያን የግብፅን አማልክት ለማምለክ መፈተን እንደሌለባቸው ሊያስተምራቸው ፈለገ።

የውይይት ጥያቄ፥ እግዚአብሔር በመቅሠፍቶች አማካይነት ካሳየው ኃይል የምናገኛቸውን መንፈሳዊ ትምህርቶች ዘርዝር።

** በራእይ 6-17፥ በመጨረሻው ዘመን በሰው ልጆች ላይ የሚመጡ ፍርዶች በግብፅ ላይ ከወረዱት መቅሠፍቶች ጋር ተመሳሳይ መሆናቸው የሚያስገርም ነው።

የፋሲካ በዓል አከባበር (ዘጸ. 12)።

የፋሲካ በዓል በእርግጥ ሁለት በዓላትን ያካተተ ነበር። ከፋሲካ በዓል ቀጥሉ የቂጣ በዓል ይከበራል።

የመጀመሪያው በዓል፥ ፋሲካ ስያሜውን ያገኘው የእግዚአብሔር መልአክ የግብፃውያንን ቤት በኩራት በሙሉ ሲገድል፥ በመዝጊያ መቃኖቻቸው ላይ ደም ያደረጉትን የእስራኤልን ቤት «ከማለፍ» አንፃር ነው። ይህ የአንድ ቀን በዓል ነበር። በመጀመሪያው የማለፉ (የፋሲካ) በዓል፥ እያንዳንዱ ቤተሰብ ምንም ጉድለት የሌለበትን አንዳንድ ጠቦት ያርድ ነበር። ከዚያም የጠቦቱ ደም መቃንና በቤቱ በር ጎበን ላይ ይቀባ ነበር። የቀረው የጠቦቱ ሥጋ ደግሞ ተጠብሶ ማታ ይበላ ነበር።

ከእስራኤላውያን እጅግ የታወቁ በዓላት አንዱ ይህ የፋሲካ በዓል ነበር። ይህም ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሠራው ሥራ ምልክት ነበር። ኢየሱስ በመስቀል ላይ ስለሞተ፥ የእግዚአብሔር ፍርድ እኛን አለፈ። ክርስቶስ የፋሲካ በግ የተባለበት ምክንያት ይህ ነው (1ኛ ቆሮ. 5፡7፤ ዮሐ. 1፡29 ተመልከት)። ብዙ ክርስቲያኖች አይሁድ ደሙን በበሩ መቃንና ጎበን ላይ ማድረጋቸው የመስቀሉ ምልክት ነው ብለው ያምናሉ። እኛ በመታሰቢያነት የምናከብረው የጌታ እራት የተመሠረተው በፋሲካ በዓል ላይ ነው።

ከፋሲካ በዓል ቀጥሉ የቂጣ በዓል ይከበራል። አንድ ሳምንት የሚፈጅ በዓል ነው። አይሁድ እግዚአብሔርን ለማምለክ ራሳቸውን ያዘጋጁ ነበር። በመጀመሪያ በቤታቸው ያለውን ማንኛውንም እርሾ ያስወግዳሉ። እርሾ ያለበት ማንኛውም ነገር ወደ ውጭ ይጣላል። እርሾ የክፋት ምልክት ስለሆነ፥ ይህንን ሲያደርጉ በመንፈሳዊ ነገር ራሳቸውን ከክፋት ሁሉ ማንጻታቸው ነው። ቀጥሉ እርሾ የሌለበትን ቂጣ ይጋግራሉ። ይህም እግዚአብሔር ከግብፃውያን እንዴት ነፃ እንዳወጣቸውና እንዴት ግብፅን በጥድፊያ ትተው መውጣት እንደነበረባቸው ለትውልዶች ሁሉ ማስታወሻ ነበር፤ (ዘጸ. 12፡11 ተመልከት)።

እርሾ የሌለበት የቂጣ በዓል እኛም ደግሞ ያለማቋረጥ ከኃጢአት ራሳችንን በማንጻት ለእግዚአብሔር የተቀደስን ሆነን እግዚአብሔር በእኛ ውስጥና በእኛ በኩል እንዲሠራ መዘጋጀት እንዳለብን የሚያሳይ ምልክት ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- አሁን ልብህን ለመመርመር ጊዜ ይኑርህ። የኃጢአትን እርሾ ከሕይወትህ አስወግደሃልን? ካላስወገድክ ኃጢአትህን ለእግዚአብሔር ተናዘዝ። የፋሲካው በግ ደምም ከኃጢአት ያነጻሃል፥ (1ኛ ዮሐ. 1፡9 ተመልከት)።

ፈርዖን የበኩር ልጁ ከሞተ በኋላ እስራኤላዊያን እንዲሄዱ ፈቀደ። ግብፃውያን በጣም ተጨንቀው ስለነበር አይሁዳውያን ይሄዱላቸው ዘንድ ወርቃቸውን፡ ብራቸውንና ሌሎች ውድ ነገሮቻቸውን ሁሉ ሰጡአቸው። በዚህም አይሁድ ምንም ኃይል ሳይጠቀሙ ግብፃውያንን በዘበዙአቸው። (ይህም በዘፍ. 15፡14 ለተጻፈው ትንቢት መፈጸም ምክንያት ሆነ) ይህንን ጥቅስ አንብብ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “የእግዚአብሔር ሕዝብ ነጻነት (ዘጸ. 5-12) ”

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading