ኦሪት ዘሌዋውያን 1-10

መሥዋዕቶችንና ዓላማቸውን በትክክል መረዳት እግዚአብሔር የኃጢአት ይቅርታ ያዘጋጀበትን መንገድ ለመረዳት ይጠቅማል። ኦሪት ዘሌዋውያን ኃጢአተኛ የሆነው የእስራኤል ሕዝብ የተቀደሰውን እግዚአብሔርን እንዴት ማምለክ እንዳለበት ዝርዝር መመሪያ ይሰጣል። እግዚአብሔር ቅዱስ ባይሆን ኖሮ፥ መሥዋዕት የሚባል ነገር ባላስፈለገም ነበር፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ቅዱስ ስለሆነና ኃጢአትን ሳይቀጣ ስለማያልፍ፥ እንዲሁም መሐሪ ስለሆነ፥ ለእስራኤላውያን ወደ እርሱ እንዴት እንደሚመጡና የኃጢአታቸውን ይቅርታ እንደሚያገኙ ዝርዝር መመሪያ ሰጣቸው።

የውይይት ጥያቄ፥ ዘሌ. 1-10 አንብብ። ሀ) አምስቱን ዋና ዋና የመሥዋዕት ዓይነቶች ዘርዝር። ለ) የእያንዳንዱ መሥዋዕት ዓላማ ምን ነበር? ሐ) ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ ከመሥዋዕቶች የምንማረው ነገር ምንድን ነው? መ) መሥዋዕት ስለ ኃጢአት ክፉነት የሚያስተምሩት ምንድን ነው? ሠ) ከካህናት ለአገልግሎት መለየትና ከአሮን ልጆች ሞት የምንማረው ምንድን ነው? 

ዘሌ. 1-10 በሁለት የተለያዩ ርእሶች ያተኩራል። አጠቃላይ ክፍሉ የእግዚአብሔር ሕዝብ የሆኑት እስራኤላውያን እንዴት እግዚአብሔርን ማምለክ እንደ ነበረባቸው የሚናገር ቢሆንም፥ ዘሌ. 1-7 እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ሊያመልኩ ስለሚችሉበት አምስት መሥዋዕተች ይናገራል። ዘሌ. 8-10 ደግሞ የአምልኮ መሪዎች የሆኑት ካህናት ቅዱስ እግዚአብሔር የሚመለክበትን የአምልኮ ፕሮግራም ለመምራት እንዴት በጥንቃቄ እንደሚዘጋጁ ይናገራል። 

  1. ይቅርታን ለማግኘትና እግዚአብሔርን ለማምለክ የሚያስፈልጉ መሥዋዕቶች (ዘሌ. 1-7)። 

በእነዚህ ዘሌዋውያን ምዕራፎች ለእግዚአብሔር ትክክለኛ የሆነ መሥዋዕትን በትከክለኛ መንገድ ስለ መሠዋት በርካታ ሕጎች ተሰጥተዋል። የሚከተሉት ሕግጋት መሥዋዕቶቹን ሁሉ ከሚመለከቱ መካከል ጥቂቶቹ ናቸው፡-

ሀ. መሥዋዕቶቹ ሁሉ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ፥ በነሐስ መሠዊያው ላይ መቅረብ ነበረባቸው።

ለ. እንስሶቹ ከመሠዋታቸው በፊት፥ መሥዋዕቱን የሚያቀርበው ሰው በእንስሳው ራስ ላይ እጆቹን ይጭናል። ይህም የሚደረገው ለሁለት ዓላማ ነው፡፡ የመጀመሪያው፥ እንስሳው ራስ ላይ እጆቹን መጫኑ ምትክ መሆኑን ሰውዬው ተገንዝቧል ማለት ሲሆን፥ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ሰውዬው በዚህ ጊዜ ኃጢአቱን በመናዘዝ ምሳሌያዊ በሆነ መንገድ ኃጢአቱን ሁሉ በእንስሳው ላይ ያኖራል።

ሐ. ካህኑ እንስሳውን ያርዳል።

መ. የእንስሳው ደም በመሠዊያው ላይ ይረጫል።

ሠ. እንስሳው ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል ይቃጠላል።

እስራኤላውያን በአምልኳቸው ለእግዚአብሔር የሚሠዏቸው የአምስት መስዋዕቶች ዝርዝር

  1. የሚቃጠል መሥዋዕት (ዘሌ 1)

የሚቃጠለው ክፍል፡- ሁሉም

የሚሰዋው እንስሳ፡- ተባዕት ሆኖ ነውር የሌለበት፣ መስዋዕቱን በሚያቀርበው ሰው አቅም

የሚሰዋበት ምክንያት፡- ለአጠቃላይ ሃጢአት፣ ለእግዚአብሔር መሰጠትን ያሳያል

  1. የእህል ቁርባን (ዘሌ 2)

የሚቃጠለው ክፍል፡- ከፊሉ፣ ሌሎች ክፍሎችን ካህናት ይበሉታል

የሚሰዋው እንስሳ፡- እርሾ የሌለበት ቂጣ፣ ጨው ያለበት የዳቦ ሙልሙል 

የሚሰዋበት ምክንያት፡- የበኩራት ፍሬን ለእግዚአብሔር በመስጠት ስለሰብሉ እግዚአብሔርን ማመስገን

  1. ስለደኅንነት (ዘሌ 3 እና 22፡18-30)
  • ሀ) የምስጋና መስዋዕት
  • ለ) የስዕለት መስዋዕት
  • ሐ) የበጎ ፈቃድ መስዋዕት

የሚቃጠለው ክፍል፡- ስቡ፣ ሌሎች ክፍሎች በካህናትና መስዋዕቱን ባቀረበው በሕብረት ይበላል

የሚሰዋው እንስሳ፡- ተባዕት ወይም እንስት እንደ አቅራቢው አቅም 

የሚሰዋበት ምክንያት፡- 

  • ሀ) ላልተጠበቀ በረከት ምስጋናን ለማቅረብ
  • ለ) ከችግር ስለመዳን ስዕለትን ለመክፈል
  • ሐ) በአጠቃላይ ምስጋናን ለመግለጥ
  1. የሃጢአት መሥዋዕት (ዘሌ 4)

የሚቃጠለው ክፍል፡- ስቡ፣ ሌሎች ክፍሎችን ካህናት ይበሉታል 

የሚሰዋው እንስሳ፡- 

  • ካህናት ወይም ሕዝቡ፡- በሬ
  • ንጉሡ፡- ወንድ ፍየል
  • ግለሰቦች፡- ሴት ፍየል   

የሚሰዋበት ምክንያት፡- አጠቃላይ መንጻት ሲያስፈልግና ለተለያዩ የግል ሃጢአቶች ይቀርባል 

  1. የበደል መሥዋዕት (ዘሌ 5፡1-6፡7)

የሚቃጠለው ክፍል፡- ስቡ፣ ሌሎች ክፍሎችን ካህናት ይበሉታል

የሚሰዋው እንስሳ፡- ነውር የሌለበት አውራ በግ 

የሚሰዋበት ምክንያት፡- እግዚአብሔርን ወይም ሰውን ሲበድል

ስለተለያዩ መሥዋዕቶች የሚከተሉትን እውነቶች አስተውል፡-

  1. የሚቃጠል መሥዋዕት በመሠዊያው ላይ ሙሉ ለሙሉ ይቃጠላል። ብዙዎች ይህ ስለ ኃጢአታችን መስዋዕት ይሆን ዘንድ ራሱን ሙሉ በሙሉ ለእግዚአብሔር የሰጠው የክርስቶስ ምሳሌ እንደሆነ ያስባሉ። በሮሜ 12፡1 ላይ ክርስቲያኖች ራሳቸውን ሕያው መሥዋዕት አድርገው እንዲያቀርቡ ሲጠይቅ በጳውሎስ አእምሮ የነበረው መሥዋዕት ይህ ሳይሆን አይቀርም። 
  2. እንደ አቅራቢው ሰው ዓይነቱ ይለያያል። በሥልጣን ላይ ያሉ ከፍተኛ መሥዋዕት ያቀርባሉ። ሀብታም የሆኑ ሰዎችም ትልቅ መሥዋዕት ያቀርቡ ነበር። ድሀ ሰው ርግብ ወይም እህል ብቻ ቢሆን እንኳ እንዲያቀርብ እግዚአብሔር ፈቅዶ ነበር። ምሕረቱን ሰዎች ሁሉ ሊቀበሉት የሚችሉ እንዲሆን የይቅርታ ማግኛ መንገድ አደረገው።
  3. የበደል መሥዋዕት የሚቀርበው ካሣ ስለሚጠየቅባቸው ኃጢአቶች ነበር። ለምሳሌ፡- አንድ ሰው አሥራቱን ለእግዚአብሔር ካልከፈለ፥ የበደል መሥዋዕት እንዲያቀርብ ይጠበቅበት ነበር። ወይም አንድ ሰው የራሱ ያልሆነውን ነገር ከጎረቤቱ ሲወስድ፥ የበደል መሥዋዕት እንዲያቀርብ ይፈለግበት ነበር። ነገር ግን የበደሉን ይቅርታ ያገኝ ዘንድ፥ መሥዋዕቱን ከማቅረቡ በፊት፥ ዕዳውን ለእግዚአብሔርም ሆነ ለሰው እንዲከፍል ይጠበቅበት ነበር። ዕዳውን ሲከፍል በዕዳው ላይ አንድ አምስተኛ እጅ መጨመር ነበረበት። ይህ በሌላ ሰው ላይ በደል በምንፈጽምበት ጊዜ ካሣ እንዴት መክፈል እንዳለብን የሚያሳይ ጥሩ ምሳሌ ነው። ገንዘብ ሰርቀን እንደሆነ ይቅርታ መጠየቅ ብቻ ሳይሆን፥ ገንዘቡን መመለስም አለብን። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ብዙ ጊዜ ክርስቲያን ገንዘብ ወይም ሌላ ነገር በሚሰርቅበትና ይቅርታ ለማግኘት በሚፈልግበት ጊዜ፥ የሰረቀውን ነገር ይመልሳል ወይስ ይቅርታ ብቻ ይጠይቃል? መልስህን አብራራ። ለ) የበደል መሥዋዕት ይቅርታ ከመጠየቅ በፊት ገንዘቡን ስለ መክፈል ምን ያስተምረናል? ሐ) የእግዚአብሔርን ይቅርታ ከማግኘት በፊት ከሌሎች ጋር ስለ መታረቅ ማቴ. 5፡23-24 ምን ይላል? 

  1. የካህናት ለእግዚአብሔር አገልግሎት መለየት (ዘሌ. 8-10)

በእግዚአብሔር ፊት ማገልገል በቀላሉ የምናየው ነገር አይደለም። በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በመሪነት ማገልገል በርካታ ኃላፊነትንና ከእግዚአብሔር ዘንድ ከባድ ፍርድን የሚያመጣ ነው (ያዕ. 3፡1፤ ዕብ. 13፡17)፡፡፡ ስለዚህ አሮንና ልጆቹ የእግዚአብሔርን ሕዝብ በተቀደሰ አምልኮ ለመምራት ሲዘጋጁ፥ እነርሱ ራሳቸውም ሆኑ የአምልኮ ዕቃዎቹ በሙሉ በጥንቃቄ እንዲነጹ ያስፈልግ ነበር። እነዚህ ምዕራፎች በአምልኮ ሰዓት እንዴት መጠንቀቅ እንዳለብንና የቤተ ክርስቲያን አመራር ምን ያህል ከፍተኛ ነገር እንደሆነ የሚያስገነዝበን ነው።

ቀጥሎ በእነዚህ ምዕራፎች ውስጥ የሚገኙ ዋና ዋና ነገሮች ተጠቅሰዋል፡-

  1. ሙሴ የአምልኮ ሥርዓት ከመጀመሩ በፊት ካህናትንና የአምልኮ ዕቃዎችን በሙሉ ያነጻቸው ነበር። ከኃጢአት ያነጻቸው ዘንድ የሚቃጠልና ባለማወቅ ስለተፈጸመ በደል የሚቀርብ መሥዋዕት ያቀርብ ነበር። ልዩ የሆነ አውራ በግ ያርድና በደሙ ቀኝ ጆሮን፥ የቀኝ እጅ አውራ ጣትና የቀኝ እግር አውራ ጣትን ለማስነካት ይጠቀም ነበር። ይህም እግዚአብሔርን ለመስማት፥ ሥራውን ለመሥራትና በመንገዱ ለመሄድ ዝግጁ መሆናቸውን ያመለክት ነበር። ከዚያም ሥራውን ከመጀመራቸውም በፊት ለአንድ ሳምንት ይቆዩ ነበር። አሮንና ልጆቹ በዝግጅት ለአንድ ሳምንት ከቆዩ በኋላ፥ ሁሉንም የመሥዋዕት ዓይነቶች በማቅረብ አገልግሎታቸውን ይጀምሩ ነበር። እግዚአብሔር ነሐስ መሠዊያ ላይ ያለውን መሥዋዕት የሚያቃጥል እሳት በመላክ አገልግሎታቸውንና አምልኮአቸውን መቀበሉን ያላይ ነበር።
  2. ሁለቱ የአሮን ልጆች በመገናኛው ድንኳን ውስጥ አገልግሎት ጀምረው ብዙም ሳይቆዩ እግዚአብሔር በሞት ቀጣቸው። የተሰጠው ምክንያት በጌታ ፊት የማይገባ እሳት ይዘው መቅረባቸው ነው። የናዳብና የአብድዩ ኃጢአት ምን እንደሆነ ግልጽ አይደለም። በተገደሉ ጊዜ ለዕጣን መሠዊያ የሚሆን ዕጣን ይዘው ወደ ቅድስት የገቡ ይመስላል። ፍርዱ በርካታ ምክንያቶች ሊኖሩት ይችላሉ፡- ሀ) እግዚአብሔር ያልፈቀደውን ከሰል ወይም ዕጣን ተጠቅመው ይሆናል። ለ) ለሊቀ ካህኑ ብቻ የተፈቀደውን ሥራ ሠርተው ሊሆን ይችላል። ) ያለ አሮንና ሙሴ ፈቃድ ዕጣን አጥነው ይሆናል። መ) ሰክረው ሊሆን ይችላል። ምናልባት ከእነዚህ ልጆች ሞት በኋላ፥ እግዚአብሔር ወዲያውኑ ለአሮንና ለካህናቱ በመገናኛው ድንኳን ከማገልገላቸው በፊት እንዳይጠጡ ያዘዛቸው ስለዚህ ይሆናል። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር በእነዚህ ሰዎች ላይ ወዲያውኑ ከባድ ፍርድ የሰጠው ለምን ይመስልሃል? ለ) የእግዚአብሔርን ሕዝብ ስንመራ ልንወስደው ስለሚገባን ጥንቃቄ ይህ ምን ያስተምረናል?

በእስራኤላውያንም ሆነ በቤተ ክርስቲያን የአምልኮ መጀመሪያ፥ እግዚአብሔር ፍጹም የሆነ ቅድስናን እንደሚፈልግ በኃጢአት ላይ ከባድ ፍርድ በመፍረድ ገልጧል (የሐዋ. 5፡1-11)። እግዚአብሔር ለእስራኤላውያንና ለአሮን በተለይም ለሕዝቡ ምሳሌ ይሆኑ ዘንድ ለመሪዎች የቅድስናን አስፈላጊነት ለማስተማር ፈለገ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: