ዘሌዋውያን 11-22

እግዚአብሔር ሕዝቡን የጠራው በፊቱ ቅዱሳን እንዲሆኑ ነው። ከዓለም የተለዩ መሆን አለባቸው። ይህ ልዩ መሆን በውስጣዊ ሕይወታችን ከሚኖር ለውጥ ይጀምራል። እኛ አዲስ ፍጥረት ነን (2ኛ ቆሮ. 5፡17)። ለውጥ ሁልጊዜ መጀመር ያለበት ከውስጥ (ከልብ) እንጂ ከድርጊት አይደለም። ይህም ማለት ልባችን በፍቅር፥ በደስታ፥ በሰላም፥ በትዕግሥት፥ ወዘተ. (ገላ. 5፡22-23) መሞላት አለበት ማለት ነው። የተለዩ ዝንባሌዎችና ዓላማዎች ሊኖሩን ይገባል። ደግሞም ይህ ልዩነት ውጫዊ በሆኑ ተግባራት ራሱን ይገልጣል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በጌታችን ባመንክ ጊዜ፥ እግዚአብሔር ልብህን የለወጠባቸው መንገዶች ምንድን ናቸው? ለ) በጌታ ባመንክ ጊዜ፥ እግዚአብሔር ተግባርህን የለወጠባቸው መንገዶች ምንድን ናቸው? (ሐ) አንዳንድ ክርስቲያኖች በውስጣዊ ሳይሆን በውጫዊ ለውጥ ላይ ብቻ የሚያተኩሩት ለምንድን ነው? ይህ ትክክል ነውን?

የእስራኤል ሕዝብ የተለዩ መሆን ነበረባቸው፤ ቅዱሳን መሆን ነበረባቸው። ስለዚህ ልዩ መሆናቸውን ለማጠናከር፥ እግዚአብሔር በርካታ ሕግጋት ሰጣቸው። ሆኖም እነዚህ ሕግጋት የተሰጧቸው እንዲያው በዘፈቀደ አልነበረም። አብዛኛዎቹ ለእስራኤል ሕዝብ ጥቅም የዋሉ ግልጽ የሆኑ ዓላማዎች ነበራቸው፡፡

የውይይት ጥያቄ፥ ዘሌ. 11-22 አንብብ። ሀ) በእነዚህ ቁጥሮች የተጠቀሱ የተለያዩ የሕግ ዓይነቶችን ወይም ክፍሎችን ጥቀስ። ለ) የማስተስርያ ቀን በዓል ዓላማ ምን ነበር? ሐ) ዘሌ. 18፡1-5 አንብብ። እነዚህ ቁጥሮች የኦሪት ዘሌዋውያንን ትምህርት የሚያጠቃልሉት እንዴት ነው? መ) ከእነዚህ ምዕራፎች ስለተቀደሰ ኑሮ የምንማራቸው አንዳንድ መመሪያዎች ምንድን ናቸው?

ዘሌ. 11-22 የእስራኤላውያንን የሕይወት ክፍል ሁሉ የሚነኩ በርካታ የሆኑ የተለያዩ ዓይነት ሕግጋትን ይዟል። እነዚህ ሕግጋት ጊዜያዊ ነበሩ። በአዲስ ኪዳን ዘመን ለምንኖር ለእኛ ግዴታዎች አይደሉም (ማር. 7፡14-22 አንብብ)።

  1. ስለምግብ የተሰጡ ሕግጋት (ዘሌ. 11)፡- እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን እንዲበሉ የተፈቀዱላቸው ምግቦች ምን ዓይነት እንደሆኑ ነገራቸው። በመሬት ላይ የሚኖሩ፥ ሣር በልተው የሚያመሰኩትና ሸኮናቸው የተሰነጠቀ እንስሳት ብቻ ለምግብነት ተፈቅደው ነበር። እነዚህ እንስሳት ብቻ «ንጹሐን» ሲባሉ የቀሩት ግን «ርኩሳን» ተብለው ነበር። ከዓሣ ዓይነቶች ክንፍና ቅርፊት ያላቸው ብቻ ለምግብነት ተፈቅደው ነበር። ከበራሪ እንስሳትና ከወፎች እንዲበሉ የተፈቀዱት የተወሰኑት ብቻ ነበሩ።
  2. ሴቶች ከወለዱ በኋላ የሚጠብቁት የመንጻት ሥርዓት (ዘሉ. 12)፡- ሴት ከሰውነትዋ ደም በሚፈሳት በማንኛውም ጊዜ በሃይማኖታዊ ሥርዓት ያልነጻች (ርኩስ) ትሆናለች። ስለዚህ ደም ከሰውነትዋ የሚፈስባት ልጅ የመውለጃዋ ጊዜ ስለሆነ ከተጠቀሰው ጊዜ በኋላ መሥዋዕት በማቅረብ እስክትነጻ ድረስ የረከሰች ትሆን ነበር።
  3. ስለ ቆዳ በሽታ፥ በልብስ፥ ወይም በቤት ግድግዳ ላይ ስለሚታዩ ያልተለመዱ ምልክቶች የተሰጠ ሕግ (ዘሌ. 13-14)፡-

እንደምታስታውሰው፥ በአይሁዳውያን አስተሳሰብ ያልተለመደ ማንኛውም ዓይነት ነገር የኃጢአት ምልክት ወይም ምሳሌ ነው። ይህ በራሱ ኃጢአት ወይም የኃጢአት ውጤት አልነበረም። ያልተለመዱ የቆዳ በሽታዎችና በልብስ ወይም በቤት ግድግዳ ላይ የሚታዩ ምልከቶች ኃጢአትን የሚያመለክቱ ስለነበሩ፥ በተሰጠው ሕግ መሠረት የመንጻት ሥርዓቶች መፈጸም ነበረባቸው።

  1. ከሰውነት የሚወጣ ያልተለመደ ፈሳሽ (ዘሌ. 15)፡- ከወንድም ሆነ ከሴት የሚወጡ የፍትወት ፈሳሾች ያልተለመዱ ሆነው ስለሚቆጠሩ፥ ሰውየውን (ሴትዮዋን) ያረክሳሉ። ስለዚህ እነዚህን ነገሮች የነካ ሰው ወይም በእነዚህ ሰዎች የተነካ ዕቃ መልሶ እስኪነጻ ድረስ የሚቆይበት የተወሰነ ጊዜ ነበር።
  2. የማስተስርያ ቀን በአይሁዳውያን የቀን መቁጠሪያ ከሁሉም የሚበልጥ ሃይማኖታዊ በዓል ነው (ዘሌ. 16)። ስለዚህ እንዴት ሊጠብቁት እንደሚገባ የተሰጡ በጥንቃቄ የተሞሉ ትእዛዛት ነበሩ። የማስተስርያ ቀን ዓላማ ሕዝቡንም ሆነ የመገናኛውን ድንኳን በየዓመቱ ውስጥ ከገጠማቸው ከማናቸውም ዓይነት ዕርኩሰት ማንጻት ነው። ያለፈውን ዓመት ኃጢአት በማንጻት ሕዝቡ በእግዚአብሔር ፊት ንጹሕ የሆነ አዲስ የሃይማኖት ዓመት ይጀምሩ ዘንድ ነው። የማስተስርያ ቀን ሃይማኖታዊ ሥርዓት ኃጢአት በእነርሱ ላይ ያመጣውን አጠቃላይ ተጽዕኖ በማሳሰብ በእግዚአብሔር ፊት ያለማቋረጥ መንጻታቸው ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ለአይሁድ የሚያሳይ ሃይማኖታዊ ሥርዓት ነበር። እግዚአብሔር በጸጋው ኃጢአታቸውን ይቅር እንዳለና ከእነርሱም እንዳራቀው ሕያው በሆነ መግለጫ ለእስራኤላውያን በማሳየት፥ ፍየልን ወደ በረሃ የመስደድ ሥርዓት ነበር። በቃል ኪዳኑ ታቦት የስርየት መክደኛ ላይ ደምን ይረጭ ዘንድ ሊቀ ካህኑ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን የሚገባበት ብቸኛ ዓመታዊ ቀን ይህ የሥርዓት ቀን ነበር።
  3. እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ስለ እንስሳት ደም ግልጽ የሆነ መመሪያ ሰጣቸው። እንደምታስታውሰው ደም የእንስሳት ሕይወት ምልክት ነበር (ዘሌ. 17፡11)። ስለዚህ እንስሳትን በሚያርዱበት ጊዜ ደማቸውን ምን ማድረግ እንዳለባቸው እንዲጠነቀቁ ግልጥ የሆነ ትእዛዝ ተሰጥቶአቸው ነበር።
  4. እግዚአብሔር፥ አንድ ሰው ማንን ማግባት እንዳለበትና ማንንስ ማግባት እንደሌለበት ግልጥ የሆነ ትእዛዝ ሰጥቷል (ዘሌ. 18)። በተጨማሪ ወንድና ሴት የግብረ ሥጋ ግንኙነት መፈጸም የሌለባቸውን ጊዜያት በሚመለከት ትእዛዛት ተሰጥተዋል።
  5. እግዚአብሔር፥ ሕዝቡ ከእርሱ ጋርና እርስ በርስ ስለሚኖራቸው ግንኙነት ግልጥ የሆኑ ትእዛዛትን ሰጥቷል። የእግዚአብሔርን ሕግ በግልጥ የማይታዘዙ ሰዎች ሊደርስባቸው ስላለው ቅጣትም ተናግሯል (ዘሌ. 19-20)።
  6. በመጨረሻም እግዚአብሔር ለካህናት የሚሆኑ ግልጥ ትእዛዛትን ሰጠ። እነዚህ ትእዛዛት ማን ካህን ሊሆን እንደሚችል፥ ካህን ማንን ማግባት እንደሚችልና እግዚአብሔርን እንዴት ማገልገል እንዳለበት የሚገልጡ ነበሩ (ዘሌ. 21-22)። የተቀደሰውን አምልኮ በመምራት ረገድ ዋናው ኃላፊነታቸው መሥዋዕትን ማቅረብ ስለነበር፥ በተለይ ይህን በሚመለከት እግዚአብሔር ለካህናት ግልጥ የሆነ ትእዛዝን ሰጣቸው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ስለ እግዚአብሔር፥ ስለ ኃጢአት፥ ከእግዚአብሔር ጋርና እርስ በርስ ሊኖረን ስለሚገባ ግንኙነት ከእነዚህ ምዕራፎች የምንማራቸው ነገሮች ምንድን ናቸው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “ዘሌዋውያን 11-22”

Leave a Reply

%d bloggers like this: