Site icon

የኦሪት ዘሌዋውያን መግቢያ

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ልንረዳቸው በጣም አስፈላጊ ከሆኑት አሳቦች አንዱ «የቅድስና» አሳብ ነው። ይህም የእግዚአብሔር ባሕርይ መሠረት ነው። እግዚአብሔር በኦሪት ዘሌዋውያን ውስጥ ቅዱስ እንደሆነ በመደጋገም ይናገራል። የእግዚአብሔር ሕዝቦች ማንነትና እግዚአብሔር ሕዝቦቹን ሊሆኑ የሚገባቸውን የሚያስረዳ መሠረታዊ አሳብ የቅድስና አሳብ ነው። የእግዚአብሔር ሕዝብ እንደ መሆናችን መጠን እግዚአብሔርን መምሰል አለብን። ዘሌዋ. 11፡44፡- «እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝና፤ ሰውነታችሁን ቀድሱ፥ ቅዱሳንም ሁኑ» ይላል።

የውይይት ጥያቄ፥ «ቅዱስ» እና «መቀደስ» የሚሉትን ቃላት ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት እይ። የእነዚህን ቃላት ትርጉም ጻፍ። ሀ) እግዚአብሔር ቅዱስ የሆነው በምን መንገድ ነው? ለ) የእግዚአብሔር ሕዝብ ቅዱስ መሆን ያለብን በምን መንገድ ነው? ሐ) ቤተ ክርስቲያንህ ቅድስት ነችን? ግለጽ። መ) ብዙ አብያተ ክርስቲያናት እንዲሁም ክርስቲያኖች ለመቀደስ ያለባችው ችግር ምንድን ነው? ሠ) ዘሌዋ. 11፡44ን በቃልህ አጥና።

ኦሪት ዘሌዋውያን ስለ ቅድስና የሚናገር መጽሐፍ ነው። ይህ መጽሐፍ ለመረዳትና ለመተርጎም በጣም አስቸጋሪ ቢሆንም፥ በእግዚአብሔር ቅድስና ላይ የሚያተኩር በመሆኑና መመለክም ያለበት በቅዱሳን ሰዎች መሆኑን ከተገነዘብን፥ የኦሪት ዘሌዋውያንን መልእክት የበለጠ እንረዳለን። 

የኦሪት ዘሌዋውያን ርእስ

እንደሌሎቹ የፔንታቱክ መጻሕፍት ርእሶች ሁሉ የኦሪት ዘሌዋውያን – የአማርኛው ርእስም የተገኘው በግሪክ ከተጻፈው የብሉይ ኪዳን ትርጉም ከሴፕቱዋጀንት ነው። «ዘሌዋውያን» ማለት «የሌዋውያን ጉዳይ» ወይም «ስለ ሌዋውያን የተነገረ» ማለት ነው። ከጥናታችን እንደምናስታውሰው ሌዋውያን ከእስራኤል ነገዶች አንዱ ነበሩ። ዋናው ኃላፊነታቸው በብሉይ ኪዳን ዘመን ሁሉ በቤተ መቅደስ ውስጥ እግዚአብሔርን ማገልገል ነበር። ከእነዚህ ተግባራት አብዛኛዎቹ የሌዋውያን አካል የሆኑት የአሮን ቤተሰቦች ቢሆኑም ሁሉም ሌዋውያን በቤተ መቅደስ ሥራ ውስጥ የማገልገልና የመርዳት ኃላፊነት ነበረባቸው፤ ስለዚህ ይህ ስም የሚያመለክተው፥ የዚህ መጽሐፍ አብዛኛው ክፍል የእግዚአብሔር ሕዝብ አምልኮ እንዴት እንደሚመሩ ለካህናት ትእዛዝንና መመሪያን ለመስጠት ትኩረት የሚያደርግ እንደሆነ ነው። ኦሪት ዘሌዋውያን የሚያተኩረው በአምልኮ ሕግጋትና ደንቦች ላይ ነው። 

አይሁድ ለፔንታቱክ ሦስተኛ መጽሐፍ የሰጡት ስም የተለየ ነው። እንደልማዳቸው የመጽሐፉን ርእስ «እርሱም ጠራ» በማለት ሰይመውታል (ዘሌ. 1፡1)። 

የኦሪት ዘሌዋውያን ጸሐፊ

በኦሪት ዘፍጥረትና በዘጸአት ጥናታችን እንደተመለከትነው፥ ምሁራን የፔንታቱክ ጸሐፊ ማን እንደሆነና የተጻፈበት ጊዜ መቼ እንደሆነ የተለያዩ አሳብ በመስጠት ይከራከራሉ። ስለዚህ በትምህርት ሦስት ስለ ፔንታቱክ ጸሐፊ የተሰጠውን ገለጻ ተመልከት። የኦሪት ዘሌዋውያን ጸሐፊ ሙሴ እንደሆነ መጽሐፉ ባይናገርም፥ ከ25 ጊዜ በላይ «እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ ሲል ተናገረው» የሚል ቃል አለ። ስለዚህ ጸሐፊው ሥጋ ለባሹ ሙሴ እንደሆነ መገመቱ ትክክል ነው። 

ኦሪት ዘሌዋውያን የተጻፈበት ጊዜ

ኦሪት ዘሌዋውያን የተጻፈበት ጊዜ፥ ሕዝቡ ከግብፅ የወጡበትን ጊዜ አርቀው በሚገምቱ (1440 ዓ.ዓ.) እና አቅርበው በሚገምቱ (1220 ዓ.ዓ.) መካከል ይለያያል። ሆኖም ከሁለቱ ጊዜያት 1440 ዓ.ዓ. ትክክል ይመስላል።

በኦሪት ዘሌዋውያን መጽሐፍ ውስጥ የተጠቀሱት ነገሮች ሁሉ የተፈጸሙት በሲና ተራራ ነው። ስለዚህ ሙሴ እስራኤላውያን በሲና ተራራ በነበሩበት ጊዜ ሕግጋትን በሙሉ ተቀብሎአል ብሎ መገመቱ ትክክል ነው። የጻፋቸውም በዚያው ጊዜ ሳይሆን አይቀርም። 

የኦሪት ዘሌዋውያን አስተዋጽኦ

ኦሪት ዘሌዋውያን በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች ይከፈላል። 

  1. የተቀደሰውን አምላክ እንዴት ማምለክ እንደሚቻል (ዘሌ. 1-10)፡- በዚህ ክፍል እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን፥ ምን ዓይነት መሥዋዕት፥ በምን ምክንያት ማቅረብ እንዳለባችው ይነግራቸዋል። በተጨማሪ እግዚአብሔርን ለማምለክ ብቁ ይሆኑ ዘንድ ቄሶች እንዴት እንደሚለዩም ተጽፏል።
  2. በእግዚአብሔር ፊት እንዴት ቅዱስ ሕዝብ ሆኖ መኖር እንደሚቻልና የእግዚአብሔርን በረከት እንዴት መቀበል እንደሚቻል (ዘሌ. 11-27)፡- በዚህ ክፍል እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን የተለያዩ ትእዛዛትን ይሰጣል። እነዚህም ትእዛዛት የእግዚአብሔር እንደመሆናቸው መጠን በእግዚአብሔር ፊት በቅድስና እንዴት መኖር እንደሚችሉ ይገልጽላቸዋል። 

የውይይት ጥያቄ፥ እነዚህ ሁለት ዓበይት ነጥቦች በዚህ ዘመን ላሉ ክርስቲያኖች የሚያስፈልጉት እንዴት ነው? ከዚህ በታች የኦሪት 1 ዘሌዋውያን ዝርዝር አስተዋጽኦ ተሰጥቶአል? 

  1. በመሥዋዕቶች አማካይነት የተቀደሰውን አምላክ ማምለክ (ዘሌ. 1-7)

ሀ. የሚቃጠል መሥዋዕት (ዘሌ. 1)፥ 

ለ. የእህል ቁርባን (ዘሌ. 2)፥

ሐ. የድነት (ደኅንነት) መሥዋዕት (ዘሌ. 3)፥

መ. የኃጢአት መሥዋዕት (ዘሌ. 4)፥ 

ሠ. የበደል መሥዋዕት (ዘሌ. 5)፥ ረ. ስለ መሥዋዕቶች የቀረቡ ልዩ ልዩ ሕግጋት (ዘሌ. 6-) ናቸው።

  1. የተቀደሰውን የእግዚአብሔርን አምልኮ ለመምራት ካህናትን  መለየት (ዘሌ. 8-10)፡

ሀ. ካህናት ለአገልግሉት ተለዩ (ዘሌ. 8)፤ 

ለ. ካህናት አገልግሎታቸውን ጀመሩ (ዘሌ. 9)፤ 

ሐ. የአሮን ልጆች ናዳብና አቢዩድ ለፈጸሙት በደል ፍርድ ተሰጣቸው (ዘሌ. 10)።

  1. በተቀደሰው እግዚአብሔር ፊት የቅድስና አንዋኗር (ዘሌ. 11-27)፡

ሀ, በሃይማኖታዊ ሥርዓት ሰውን «ስለሚያነጹት» እና «ስለሚያረክሱት» ነገሮች የተደረጉ ሕግጋት (ዘሌ. 11-15)፥ 

ለ. በእግዚአብሔር ፊት በቅድስና ስለመኖር የተደነገጉ ሕግጋት (ዘሌ. 16-25)፥ 

ሐ. የእግዚአብሔርን ሕግ በመታዘዝ የሚገኝ በረከትና ባለመታዘዝ የሚመጣ መርገም (ዘሌ. 26)፥ 

መ. በእግዚአብሔር ፊት ስለትን ስለ መፈጸም የተደነገጉ ሕግጋት (ዘሌ. 27) ናቸው። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version