ዘሌዋውያን 23-27

ሰዎች እግዚአብሔርን የሚያመልኩባቸው የተለዩ ቀናት ከሌሏቸው በቀር፥ የሳምንቱን ቀናት በሙሉ በሥራ ወደ ማሳለፍ በማዘንበል፥ ስለ መንፈሳዊ ነገር ለማሰብና እግዚአብሔርን ለማምለክ ጊዜ ሊያጡ ይችላሉ። ለአይሁድ ከተለመደው ዕለታዊ ተግባራቸው ዞር የሚሉባቸውንና ስለ እግዚአብሔር በማሰብ እርሱን የሚያመልኩባቸው የተለያዩ ሃይማኖታዊ በዓላትን ሰጣቸው። አይሁድ ሳምንታዊ የአምልኮ ቀን፥ ወርኃዊ የአምልኮ ቀን፥ በየዓመቱ የሚደረጉ ሰባት የአምልኮ ቀናት፥ በየሰባት ዓመቱ የሚሆን የአምልኮ ዓመትና በየ50 ዓመቱ የሚፈጸም ልዩ የአምልኮ ጊዜ ነበራቸው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እኛ የምንጠቀምባቸው ዋና ዋና ሃይማኖታዊ በዓላት የትኞቹ ናቸው? ለ) ትኩረታችንን የበለጠ በእግዚአብሔር ላይ እንድናደርግ የሚረዱን እንዴት ነው?

የውይይት ጥያቄ፦ ዘሌ. 23-27 አንብብ። ሀ) የተለያዩ የአምልኮ ቀናትንና ዓላማቸውን ዘርዝር። ለ) እግዚአብሔርን በመታዘዝ የሚገኙ በረከቶችና ባለመታዘዝ የሚመጡ ቅጣቶች ምንድን ናቸው? ለእግዚአብሔር የተገባ ስዕለትን ወይም ቃል ኪዳንን ስለመጠበቅ በዚህ ስፍራ የተሰጠው ትምህርት ምንድን ነው? 

  1. ሃይማኖታዊ በዓላት (ዘሌ. 23)

አይሁድ እርሱን ለማምለክ መለየት ስለሚገባቸው ቀናት እግዚአብሔር በግልጥ አዞአቸዋል። በመጀመሪያ፥ ሳምንታዊ የአምልኮ ቀን የሆነው ሰንበት ወይም ቅዳሜ ነው። እግዚአብሔር ከመፍጠር ሥራው ያረፈበትን የሰንበት ቀን ማንም ሰው በማክበር ማረፍና እግዚአብሔርን ማምለክ ስላለበት፥ በሰንበት እንዲሠራ አይፈቀድለትም ነበር።

ሁለተኛ፥ የወር መባቻ የተባለው ወርሐዊ የአምልኮ ቀን ነበር፤ (ዘኁል. 10፡10)። ይህ ቀን እግዚአብሔር ለአይሁዳውያን ሌላ ወር ስለሰጣቸው ለመታሰቢያ የሚያከብሩት ዕለት ነው።

ሦስተኛ፣ ዓመታዊ የአምልኮ ቀናት ነበሩ። 

ፋሲካ (ዘጸ. 12፡1-4፣ ዘሌ 23፡5፣ 1ቆሮ 5፡7)

ቀኑ፡- አንደኛ ወር (መጋቢትና ሚያዝያ) 

የበዓሉ አላማ፡- እስራኤላውያን ከግብጽ ነጻ የወጡበት ቀን መታሰቢያ (ለአንድ ቀን)  

በዓሉ የሚያመለክተው ትንቢት፡- ክርስቶስ የፋሲካው በግ መሆኑን ለማሳየት

የቂጣ በዓል (ዘጸ. 12፡15-20፣ ዘሌ ዘጸ. 23፡6-8)

ቀኑ፡- አንደኛ ወር ከፋሲካ ወር በኋላ ወዲያውኑ 

የበዓሉ አላማ፡- እግዚአብሔር ከግብጽ አቻኩሎ ነጻ እንዳወጣቸው (ለ1 ሣምንት)

በዓሉ የሚያመለክተው ትንቢት፡- ክርስቶስ ሃጢአት የሌለበት የእግዚአብሔር በግ መሆኑንና እኛም እንዴት ቅዱሳን መሆን እንዳለብን ለማሳየት (1ቆሮ 5፡6-8)

የበኩራት በዓል (ዘሌ. 23፡9-14)

ቀኑ፡- በቂጣ በዓል ጊዜ ውስጥ (1ኛ ወር)

የበዓሉ አላማ፡- ምርቱንና የሚያስፈልጋቸውን የሚሰጣቸው እግዚአብሔር እንደሆነ ለማሳሰብ (ለ1 ቀን)

በዓሉ የሚያመለክተው ትንቢት፡- የክርስቶስ ትንሣኤ የበኩራት መሆኑን ለማሳየት (1ቆሮ 15፡20-23)

በዓለ ኅምሣ (ዘሌ. 23፡9-14)

ቀኑ፡- ከፋሲካ በኋላ 50ኛ ቀናት (ግንቦት-ሰኔ)

የበዓሉ አላማ፡- የመከር መጨረሻንና የእግዚአብሔር የለጋስነት ስጦታን ለማክበር (ለ1ቀን)

በዓሉ የሚያመለክተው ትንቢት፡- የቤተ ክርስቲያን ጅማሬ (ሐዋ 2)

የመለኮት ድምጽ (ዘሌ. 23፡23-25)

ቀኑ፡- የሰባተኛው ወር የመጀመሪያ ቀን (መስከረም-ጥቅምት)

የበዓሉ አላማ፡- ከሁሉም በላይ የተቀደሰውን ሰባተኛ ወር ለመጀመር፣ ሃይማኖታዊ አዲስ አመት ለመጀመር፣ እስራኤልን ለእግዚአብሔር በጎነት ለማቅረብ (ለ1 ቀን) 

በዓሉ የሚያመለክተው ትንቢት፡- የወደፊቱን የእስራኤልን መሰብሰብ ለማመልከት

የስርየት ቀን (ዘሌ. 16፡23፣ 26-32)

ቀኑ፡- በሰባተኛው ወር (መስከረም-ጥቅምት)

የበዓሉ አላማ፡- ለሕዝቡ ሃጢአት መሥዋዕት ለማቅረብ፣ ቤተ መቅደሱን ለአምልኮ ለማንጻት

በዓሉ የሚያመለክተው ትንቢት፡- የክርስቶስን ሞት ለማመልከት (ሮሜ 3፡24-26) የወደፊቱን የእስራኤል ንስሐ ለማመልከት (ዘካ 12)

የዳስ በዓል (ዘሌ. 23-33-36)

ቀኑ፡-በሰባተኛው ወር (መስከረም-ጥቅምት)

የበዓሉ አላማ፡- ለምርቱ ምስጋናን ለማቅረብ፣ የአርባ አመት የምድረበዳ ኑሮን ለማስታወስ፣ (1ኛ ሳምንት)

በዓሉ የሚያመለክተው ትንቢት፡- የወደፊቱን የእስራኤል መንግሥት ለማመልከት

አንዳንዶቹ የበዓል ቀናት ክርስቶስን የሚያመለክቱ መሆናቸው ግልጥ የሆነው ከአዲስ ኪዳን ትምህርት ነው። ነገር ግን አንዳንዶቹ በዓላት ስለ ክርስቶስ የሚያሳዩ ናቸው የሚለውን ግምታዊ አስተሳሰብ አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ሲስማሙባቸው በሌሎቹ ግን ተቀባይነትን አላገኙም።

አራተኛ፥ ዓመታዊ ሰንበት የሚባል በየሰባት ዓመቱ የሚመጣ አንድ ልዩ በዓል ነበር (ዘሌ. 25፡1-7)። በዚህ ዓመት ሊያርሱም ሆነ መከር ሊሰበስቡ አይችሉም ነበር። ይህ ለእስራኤላውያን የሚያስተምረው መከሩ የሚመጣው ከእግዚአብሔር እንደሆነና ለምግባቸውም መታመን ያለባቸው በእግዚአብሔር እንጂ በራሳቸው ሥራ አለመሆኑን ነው።

አምስተኛ፥ የኢዮቤልዩ ዓመት የሚባልም ነበር (ዘሌ. 25፡8-55)። ይህ አምሳኛው ዓመት ወይም እንደ አይሁድ አቆጣጠር፥ የዓመታት ሰንበት ሰባተኛ ዙር ነው። በዚህ ዓመት ከማምረትና መከርን ከመሰብሰብ ማረፍ ብቻ ሳይሆን፥ ባሪያዎች ሁሉ ነፃ ይሆናሉ። መሬት በሙሉ ለባለቤቱ ይመለሳል። ይህም እነርሱም ባሪያዎች እንደነበሩ በማሰብ ለባሮች መራራት እንዳለባቸው እስራኤላውያንን ለማስተማር ነበር። መሬትን ለቀድሞ ባለንብረቶች የመመለሱ ሥርዓትም፥ ሀብታሞች የበለጠ እየበለጸጉ እንዳይሄዱና ድሆችም ምድራቸውን ሁሉ በማጣት የበለጠ ድሆች እንዳይሆኑ የሚከላከል ነው። እንዲሁም መሬት የእግዚአብሔር እንጂ የራሳቸው እንዳልሆነ ተገንዝበው፥ ለረጅም ጊዜ ማከራየት እንጂ መሸጥ እንደሌለባቸው ለማሳሰብ ነው።

ስለ ሃይማኖታዊ ቀናት የሚከተሉትን ነገሮች አስተውል፡- 1. በቁጥር 7 ላይ ትኩረት አለ። ሰባት በዓላት አሉ፤ አብዛኛዎቹ በዓላት ደግሞ በሰባተኛው ወር የሚከበሩ ናቸው። እያንዳንዱ ሰባተኛው ዓመትና የዓመታቱ ሰባት ሱባዔዎች በሙሉ የተቀደሱ ናቸው፤ ምክንያቱም በአይሁዳውያን አእምሮ ሰባት ፍጹምነትንና ብቃትን የሚያመለክት ልዩ ቁጥር ነው። 

  1. አይሁዳውያን ወንዶች ሁሉ ወደ ቤተ መቅደስ ሄደው እንዲያከብሩ የሚፈለግባቸው ሦስት በዓላት ነበሩ። እነርሱም ፋሲካ፥ በዓለ ኃምሳና የዳስ በዓል ነበሩ።
  2. እነዚህ በዓላት ለአይሁዳውያን የማስተማሪያ መሣሪያዎች ነበሩ። እያንዳንዱ በዓል እግዚአብሔር ለልጆቻቸው ቀድሞ ምን እንዳደረገላቸው ለማስተማርና ራሳቸውንም ለማሳሰብ አመቺ ጊዜያት ነበሩ (ለምሳሌ፡- በግብፅ በባርነት የነበሩበትን ጊዜና እንዴት ነጻ እንደወጡ) ደግሞም ለየዕለቱ በሚያስፈልጋቸው ነገር በእግዚአብሔር ላይ ያለማቋረጥ እንዴት ይደገፉ እንደነበር የሚያሳስቧቸው ነበሩ። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የእኛ የገናና (የልደት) የፋሲካ (የትንሣኤ) በዓላት ከእነዚህ በዓላት ጋር የሚመሳሰሉት እንዴት ነው? ለ) ቀድሞ እስራኤላውያን ያደርጉት ከነበረው አከባበር ስለእነዚህ በዓላት ዓላማ ምን ልንማር እንችላለን? 

  1. በመታዘዝ የሚገኝ በረከትና አለመታዘዝ የሚያስከትለው ቅጣት (ዘሌ. 26) 

በሲና ተራራ የተሰጠው ቃል ኪዳን በቅድመ ሁኔታ ላይ የተመሠረተ ነበር። እግዚአብሔር፥ ሕዝቡን ሊባርካቸው ቃል የገባላቸው፥ የሚታዘዙትና የሚከተሉት ከሆነ ብቻ ነበር። ከታዘዙት እግዚአብሔር ምድሪቱን በልግሥናው በሰብል እንደሚባርካት፥ ሰላምን እንደሚሰጣት፥ ለሕዝቡ በጠላቶቻቸው ላይ ድልን እንደሚያቀዳጃቸው፥ እነርሱንና ከብቶቻቸውንም ፍሬያማ እንደሚያደርጋቸው፥ ከሁሉም በላይ በመካከላቸው እንደሚሆንና በልዩ መንገድ እንደሚገናኛቸው ገለጠላቸው።

የማይታዘዙት ከሆነ ግን እነዚህን ነገሮች ሁሉ አያገኙም ነበር። በዘሌ. 26፡14-45 የተጠቀሱት ቅጣቶች፥ በኤርምያስ ዘመን በአይሁድ ላይ ስለደረሱት ነገሮች አስቀድመው የተነገሩ ትንቢቶች መሆናቸውን መመልከት የሚያስገርም ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ 2ኛ ዜና 36፡20-21፤ ኤር. 26፡9-11 አንብብ። እነዚህ ጥቅሶች በዘሌ. 26 የተጠቀሱትን አንዳንድ ቅጣቶች የሚገልጹት እንዴት ነው?

መታዘዝ ከእግዚአብሔር ጋር ላለን ኅብረትና በረከቱን ለመቀበላችን መሠረት ነው። እግዚአብሔርን ከታዘዝን ይባርከናል። በከፍተኛ ሥጋዊ በረከት ሊባርከን ይችላል፤ የየዕለት ምግባችንን ይሰጠናል፤ ሰላምን በልባችን ያፈሳል፤ የእርሱ መሆናችንን ያረጋግጥልናል፤ ወዘተ። እርሱን ካልታዘዝነው ግን በአንድ ወቅት ሐሴት ስናደርግበት የነበረውን በረከት ከእኛ በመውሰድ ይቀጣናል። ውስጣዊ ሰላማችንና እርሱን የማወቃችንን ደስታ ይወስድብናል፤ ወዘተ። አንድ ጊዜ አንድ ሰው እንዲህ ብሏል፡- «እግዚአብሔርን ባለመታዘዝ ከሚመላለስ ክርስቲያን የበለጠ ምስኪን በምድር ላይ የለም።»

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የዚህን ነገር እውነተኛነት በሕይወትህ ምን ያህል አይተሃል? ለ) በሕይወትህ ምን ዓይነት የተደበቀ ኃጢአት እንዳለ ለመረዳት አሁን ራስህን መርምር። እግዚአብሔር ይቅር እንዲልህና በረከቱን እንዲመልስልህ ጸልይ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

2 thoughts on “ዘሌዋውያን 23-27”

  1. አባይነህ የኔዓለም

    ውድ የወንጌልን በድኅረገፅ አዘጋጆች በዝግጅታችሁ ብዙ ያላወቅኳቸውን ነገሮች ለማወቅ ችያለሁ መንፈሳዊ ህይቴም በቃል እውቀት እየታነፀ እየተለወጥኩ መሆኔ ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ። ጌታ ይባርካችሁ አገልግሎታችሁን ይባርክ።

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading