Site icon

ዘኍልቁ 1-12

የእግዚአብሔርን ሕዝብ በጥሩ ሁኔታ ለመምራት ጥሩ አደረጃጀት ያስፈልጋል። ጥሩ አደረጃጀት ከሌለ መምራት በጣም አስቸጋሪ ይሆናል፤ ሕዝቡም ስለሚምታታበት፥ የእግዚአብሔር ሥራ እንደሚጠበቀው ስኬታማ አይሆንም። ስለዚህ የእስራኤል ሕዝብ የሲና ተራራን ለቆ ወደ ቃዴስ በርኔ፥ ከዚያም ወደ ተስፋይቱ ምድር ከመሄዱ በፊት ሕዝቡን ለማደራጀት ይረዳው ዘንድ እግዚአብሔር ግልጥ ትእዛዛትን ሰጠ። ይህም ግራ መጋባትንና ውጤት አልባነትን ተከላከለ።

የውይይት ጥያቄ ሀ) ደካማ አደረጃጀት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዴት ግራ መጋባትን እንደሚፈጥር አይተህ ታውቃለህ? ለ) የእግዚአብሔር ሥራ በሚገባ ከግብ እንዲደርስ መልካም አደረጃጀት የሚጫወተውን ሚና ጥቀስ ሐ) ቤተ ክርስቲያንህ እንዴት እንደተደራጀች ግለጥ። ) ከዚህ በተሻለ ሁኔታ እንዴት ልትደራጅ እንደምትችል አብራራ። 

የውይይት ጥያቄ፥ ዘኁልቁ 1-12 አንብብ ሀ) እግዚአብሔር ሕዝቡ ይቆጠር ዘንድ ሙሴን ያዘዘው ለምን ነበር? ለ) የእያንዳንዱ ነገድ ሕዝብ ብዛት ምን ያህል እንደነበር ግለጥ። ሐ) ሕዝቡ በአጠቃላይ ምን ያህል ነበር? መ) ይህንን ዝርዝር በዘኁልቁ ምዕራፍ 26 ከሚገኘው ቁጥር ጋር አወዳድር። ሠ) በዘኁልቁ 26 ያለው ጠቅላላ ቁጥራቸውስ ምን ያህል ነበር?

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የእስራኤላውያን አሰፋፈር እንዴት ሊሆን እንደሚገባ እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት አደረጃጀቱን የሚገልጥ ሥዕላዊ መግለጫ አቅርብ። ለ) የመገናኛው ድንኳን አቀማመጥና የእያንዳንዱ ነገድ አሰፋፈር እንዴት ነበር? ሐ) የተለያዩት የሌዋውያን ብድኖች ኃላፊነት ምን ነበር? መ) እስራኤላውያን ወደ ቃዴስ በርኔ በሚጓዙበት ጊዜ ያለፉባቸውን የተለያዩ ቦታዎችና በእያንዳንዱም ቦታ ምን እንደተፈጸመ ተናገር። ሠ) አሮንና ማርያም እግዚአብሔርን ያሳዘነ ምን ነገር ፈጸሙ? 

  1. እስራኤላውያን በሲና ተራራ ሰፈሩ (ዘኅ. 1-10)

ሀ. የእስርኤላውያን መቆጠር (ዘኁ. 1) 

እንደምናስታውሰው፥ አራተኛው የፔንታቱክ መጽሐፍ ርዕስ በአማርኛ «ዘኁልቁ» የሚል ነው። ዘኁ. ምዕ. 1ና 26 የእስራኤል ሕዝብ ሁለት ጊዜ መቆጠራቸውን ያሳያሉ። ዘኁ. 1 የመጀመሪያው የእስራኤል ትውልድ ወደ ተስፋይቱ ምድር ጉዞ ከመጀመራቸው ጥቂት ቀደም ብሉ የተደረገውን ቆጠራ የሚያሳይ ሲሆን ዘኁ. 26 ደግሞ ሁለተኛው የእስራኤል ትውልድ ወደ ከነዓን ከመግባታቸው በፊት የተደረገ ቆጠራ ነው።

የቆጠራው ዓላማ ምን ነበር? አራት ዋና ዋና ምክንያቶች ነበሩ? 1) ለመዋጋት የሚችሉ ስንት ወንዶች እንዳሉ ለማዋወቅ (ዘኁ. 1፡3 ተመልከት)፤ 2) የተለያዩ ተግባራት እንዲያከናውኑ ለማድረግ ስንት ሰዎች እንዳሉ ለማወቅ (ዘኁ. 3፡4፤ 3) የእግዚአብሔር ሕዝብ ለሥራው አስራት እንዲሰጡ ለማድረግ (ዘጸ. 30፡11-16)፤ 4) የከነዓንን ምድር እንደየነገዱ ብዛት ለመከፋፈል (ዘኁ. 26፡53)።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አንተ ባለህበት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስንት ክርስቲያኖች እንዳሉ ማወቅ መልካም የሚሆነው ለምንድን ነው? ለ) የቤተ ክርስቲያንህን አባሎች ጠቅላላ ቁጥር አግኝ። 2ኛ ሳሙ.24፡1-10 አንብብ። በዚህ ስፍራ የዳዊት ሕዝቡን መቁጠር ስሕተት የሆነው ለምንድነው? መ) የቤተ ክርስቲያናችንን አባሎች ስለ መቁጠር ይህ ምን ማስጠንቀቂያ ይሰጠናል?

በቤተ ክርስቲያንህ ያሉትን ሰዎች ብዛት መቁጠር ስሕተት አይደለም። የዚህ ዓይነት እውነታዎችን ማወቅ እንዲያውም ብዙ ጊዜ ጠቃሚ ነው። በዚህ መንገድ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ደካማ የሆኑትን የቤተ ክርስቲያኒቱን ልዩ ልዩ አካባቢዎች ለመርዳት ያስችላቸዋል። በአንድ አካባቢ ችግሮች እንዳሉ ለማወቅም ይረዳቸዋል። ለምሳሌ፥ የቤተ ክርስቲያን አባሎች ቁጥር እየቀነሰ ከሄደ፥ በዚያ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ አንድ ችግር እንዳለ ግልጥ ይሆንልናል። በሌላ አንጻር አባሎችን የምንቆጥረው ብዛታችንን ለማወቅ ከሆነ፣ በቤተ ክርስቲያን አባሎቻችን ብዛት ወደ መታበይ፥ ከእግዚአብሔር ይልቅ በእነርሱ ቁጥር ወደ መመካት፥ ወዘተ ይመራናል። እግዚአብሔር ዳዊትን ባካሄደው ቆጠራ የቀጣው ባለው የተዋጊ ኃይል ለመመካት በመፈለጉ ብቻ ነበር። ድልን የሚሰጠው እግዚአብሔር መሆኑን ረስቶ በእርሱ ተዋጊ ኃይል ብዛት ተደገፈ።

በዘኁ.1 ና 26 ከተደረገው የእስራኤል ሕዝብ ቆጠራ፥ የሚከተሉትን ነገሮች መመልከት እንችላለን፡-

  1. በሲና ተራራ በተካሄደው ቆጠራ ከ20 ዓመት በላይ የነበሩ ወንዶች ብዛት 603550 ሲሆን ከ38 ዓመታት በኋላ ደግሞ ከዚሁ ከ20 ዓመት በላይ የነበሩ ወንዶች ቁጥር 601730 ብቻ ነበር። ቁጥሩ በከፍተኛ ሁኔታ ይጨምራል ብለን ስንጠብቅ፥ መቀነሱ አስገራሚ ነገር ነው። በ38 ዓመት ውስጥ ቁጥራቸው ዕጥፍ ይሆናል ተብሎ ነበር የተጠበቀው፤ ነገር ግን መጀመሪያ ከነበሩት እስራኤላውያን ከ38 ዓመታት በኋላ ሲቆጠሩ እጅግ አንሰው የተገኙ ሆኑ። ይህም እግዚአብሔር በአይሁዶች ላይ ያመጣው ፍርድ ውጤትና ምልክት ነው። 
  2. 20 ና ከዚያም በላይ ዕድሜ የነበራቸው ወንዶች ብቻ ተቆጠሩ። ይህም የሆነበት ምክንያት የቆጠራው ዋና ዓላማ ሊጋጠሟቸው ከሚችሉት ጠላቶቻቸው ጋር ሊዋጋ የሚችል ምን ያህል ኃይል እንደነበር ለማወቅ ነው። በምድረ በዳ የነበረው የእስራኤል ሕዝብ ብዛት ከ 2-3 ሚሊዮን እንደሚደርስ ምሁራን ይገምታሉ።

ይህ ከፍተኛ ቁጥር አንዳንዶች እውነተኛነቱን እንዲጠራጠሩ አድርጎአቸዋል። እነዚህ ሁሉ በምድረ በዳ እንዴት ለመኖር ቻሉ? ይህን ያህል ብዙዎች ከነበሩ፥ ከእነርሱ ጋር ሲነጻጸሩ በቁጥር እጅግ ጥቂቶች የነበሩትን ከነዓናውያን ፈጽመው ለማጥፋት ለምን አልቻሉልም? (መሳ.1 ተመልከት)። ከዚህ የተነሣ አንዳንድ ሰዎች የዚህን ቁጥር ትክክለኛነት ይጠራጠራሉ። የሕዝቡን ብዛት ለመቀየር የተሰጡ ሁለት አሳቦች ነበሩ፡- የመጀመሪያው፥ እግዚአብሔር ምን ያህል ሕዝብ ነፃ እንዳወጣ ለማሳየት የቀረበ ምሳሌ ብቻ ነው እንጂ ቁጥሩ ትክክለኛ ቁጥር አይደለም የሚል ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ፡ «አንድ ሺህ» የሚለው የዕብራይስጥ ቃል «ነገድ»፥ «ጎሣ»፥ «ክፍል» እንደሚል ተደርጎ መተርጎም አለበት የሚል ነው፤ ስለዚህ አንዳንድ ሰዎች ይህ ቁጥር በእስራኤል ውስጥ የነበረው ክፍል ቁጥር እንጂ የህዝቡ ብዛት አይደለም ይላሉ። ስለዚህ እንደ ቃሉ አተረጓጎም ከ18000-100000 ተዋጊ ኃይላት እንዲሁም በአጠቃላይ ከ72000-400000 የሚደርሱ እስራኤላውያን ነበሩ። ሆኖም ግን ይህን ለሚያህል ሕዝብ እግዚአብሔር ሊጠነቀቅና የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ ሊሰጥ እንደሚችል ለመጠራጠር ምንም በቂ ምክንያት የለም፤ ስለዚህ ቀደም ብሎ ከላይ የተጠቀሰው ቁጥራቸው ትክክል እንደሆነ በመቀበል፥ በእስራኤል ምን ያህል ሕዝብ እንደ ነበር የሚያሳይ መሆኑን ማመን ተገቢ ነው። 

  1. በ38 ዓመታት ውስጥ በተካሄዱት ሁለት ቆጠራዎች የአብዛኛዎቹ ነገዶች ቁጥር በግምት እንደ መጀመሪያው ሆኖ የቆየ ሲሆን፥ ሁለት ነገዶች ብቻ ከፍተኛ ለውጥ አሳይተዋል። የምናሴ ነገድ በ20500 የጨመረ ሲሆን፥ የስምዖን ነገድ ግን በ37100 ቀንሷል። በእነዚህ ሁለት ነገዶች ውስጥ ይህ ከፍተኛ ለውጥ የታየው ለምን እንደሆነ አናውቅም። 
  2. ሌዋውያን በሕዝብ ቆጠራ ውስጥ አልገቡም ነበር፤ ምክንያቱም ወደ ጦርነት መሄድ አይጠበቅባቸውም ነበር፤ የእነርሱ ኃላፊነት በቤተ መቅደስ ውስጥ ማገልገል ነበር። 

ለ. የእስራኤላውያንን ሰፈር ማደራጀት (ዘኁ. 2)

ምናልባት ቁጥራቸው ወደ 2 ሚሊዮን የሚጠጋው የእስራኤል ሕዝብ እያንዳንዱ ሰውና እያንዳንዱ ቤተሰብ የት መሆንና ድንኳኑን የት መትከል እንዳለበት በሚገልጥ መንገድ መደራጀት ነበረባቸው። የመገናኛው ድንኳን ያለው በእስራኤላውያን መሀል እንደ ነበረ አስተውል። ልክ እንደዚሁ፥ እግዚአብሔር የሕይወታችን፣ የአምልኮአችንና የፍላጎታችን ሁሉ፥ ወዘተ. እምብርት ነው (ማቴ.6፡33፣ ሉቃ.10፡27)።

ሐ. የሌዋውያን አሰፋፈርና ተግባር (ዘኍ.3-4)

እግዚአብሔር የሌዋውያንን ልዩ ልዩ ጎሣዎች በመገናኛው ድንኳን አካባቢ አሰፈራቸው። በምሥራቅ አሮን፥ ልጆቹና የእርሱ ዝርያዎች ነበሩ። እነርሱ ካህናት ስለ ነበሩ፥ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የሚካሄደውን አምልኮ በበላይነት የመምራት ኃላፊነት ነበረባቸው። ሌዋውያን ከዚህ በተጨማሪ በሦስት ይከፈሉ ነበር፤ በደቡብ በኩል ቀዓታውያን ነበሩ። የመገናኛው ድንኳን በሚንቀሳቀስበት ጊዜ በውስጡ ባሉት የተለያዩ ዕቃዎች ላይ ኃላፊነት ነበረባቸው። በምዕራብ ደግሞ ጌርሶናውያን ነበሩ፡፡ እነርሱም የመገናኛው ድንኳን፥ በሚንቀሳቀስበት ጊዜ የመገናኛው ድንኳን አልባሳትንና መጋረጃውን የማንቀሳቀስ ኃላፊነት ነበረባቸው። በሰሜን በኩል ደግሞ ሜራሪዓውያን ነበሩ። የመገናኛውን ድንኳን ምሰሶዎችና ግድግዳዎች የማንቀሳቀስ ኃላፊነት የእነርሱ ነበረ።

መ. የሰፈሩን ንጽሕና መጠበቅ (ዘኁ.5)

በዚህ ምዕራፍ እስራኤላውያን የሰፈሩበትን ቦታ ስለ መጠበቅ በርካታ ትእዛዛት ተሰጥተዋል። አንደኛ፥ እስራኤላውያን ቅርብ ለቅርብ ሆነው በአንድነት ይኖሩ ነበር። ስለዚህ በሽታ በቀላሉ ይዛመት ነበር፤ በመሆኑም ያልተለመዱ በሽታዎች ያሉባቸው ሰዎች እስኪፈወሱ ድረስ በሰፈሩ ውጪ እንዲቆዩ እግዚአብሔር አዘዘ።

ሁለተኛ፥ ሕዝቡ የሚኖረው ተቀራርቦ ስለ ነበር፥ ክርክርና ጠብ ሊነሣ ይችል ነበር፤ ስለዚህ እግዚአብሔር በጎረቤቶቻቸው ላይ የማይገባ ነገር ቢያደርጉ፥ ይቅርታ መጠየቅና በወሰዱት ወይም ባጠፉት ነገር ላይ ከአምስት አንድ እጅ ጨምረው ካሣ እንዲከፍሉ አዘዛቸው። 

ሦስተኛ፥ እግዚአብሐር የኃጢአት መስፋፋት እንዴት መገታት እንዳለበት መመሪያዎችን ሰጠ። አንዲት ሴት በዝሙት ኃጢአት ተጠያቂ መሆን አለመሆኗን ለመወሰን የሚያስችል ያልተለመደ አደራረግ ተዘርዝሮአል። ይህ አደራረግ በብሉይ ኪዳን ውስጥ በየትኛውም ስፍራ በተግባር ሲውል አለመታየቱ፥ እስራኤላውያን በምድረ በዳ በነበሩበት ጊዜ ብቻ እንዲጠቀሙበት የተሰጠ ጊዜያዊ ትእዛዝ ይመስላል። እግዚአብሔር ሰው በአመንዝራነት ተጠያቂ መሆኑን ለመወሰን እርሱ ራሱ ዳኛ የሚሆንበትንና የሚወስንበት መንገድ ለእስራኤላውያን ሰጣቸው። ጥፋተኛ ያልሆነው ሰው «በመራራ ውኃ» እንዳይሞት የሚጠብቅና ጥፋተኛ የሆነውን ደግሞ እንዲሞት የሚያደርግ እርሱ ብቻ ነበር። 

ሠ. የናዝራዊነት ስእለት (ዘኁ.6፡1-2)

ራሱን ለተወሰነ ጊዜ ለእግዚአብሔር ለመስጠት ለሚፈልግ ሰው፥ እግዚአብሔር ልዩ መመሪያዎችን ሰጠ። ራሱን ለእግዚአብሔር የለየ ሰው «የናዝራዊነትን ስእለት» ፈጽሟል ይባል ነበር። ሰው ለእግዚአብሔር የገባውን ስእለት ለመፈጸምና ከእግዚአብሔር ልዩ ጥበቃ እንዲሁም በረከት ለማግኘት ራሱን የመስጠት ጊዜ ይኖረዋል። የናዝራዊነትን ስእለት የሚያደርግ ሰው ሦስት ነገሮችን ማሟላት አለበት፡-

ሀ) የወይን ተክል ውጤት የሆነውን ማንኛውንም መብላት አይችልም ነበር። በእስራኤል ምድር የሚገኝ ዋነኛው ፍራፍሬና መጠጥም የወይን ፍሬ ውጤት ነው።

ለ) በናዝራዊነት ስእለት ሥር መሆኑን የሚያሳይበት ውጫዊ መንገድ ጸጉሩን ማሳደግ ነበር። 

ሐ) ማንኛውንም አስከሬን መንካት አይፈቅድለትም ነበር። 

ይህ አደራረግ በፍጹም ፈቃደኝነት የሚፈጸም መሆኑን ማስተዋል ጠቃሚ ነው። በእግዚእብሔር ግፊት ሳይሆን፥ በሰውዬው ፈቃደኝነት የሚፈጸም ነው። ደግሞም ጊዜያዊና ሰውዬው ለስእለቱ እስከተለየ ድረስ ብቻ የሚቆይ ነው።

ሳምሶን በናዝራዊነት ስእለት ሥር ለነበሩ ሰዎች ጥሩ ምሳሌ ነው። የእርሱ ስእለት ቋሚ በመሆኑ፥ ጉዳዩን የተለየ ያደርገዋል። አንዳንድ ሰዎች ኢየሱስ የናዝሬቱ ኢየሱስ ተብሎ ስለሚጠራ፥ በዚህ ስእለት ሥር ነበረ ይላሉ። ይህ ግን ሊሆን እንደማይችል የምናየው ኢየሱስ ወይን እንደጠጣ የተገለጠ ነገር ስላለ ነው (ሉቃ.1፡33-34)። ይልቁንም ናዝራዊ የተባለው እርሱ ከናዝሬት ከተማ ስለነበረ ነው።

ረ. በመገናኘው ድንኳን ስለሚደረግ አምልኮ የተሰጡ ልዩ መመሪያዎች (ዘኁ.6፡22-8፡26) 

ሰ. እስራኤላውያን ሊመሩበት የሚገባ መንገድ (ዘኁ. 9፡15-10፡10) 

በምድረ በዳ በነበሩበት ጊዜ፥ እግዚአብሔር ሕዝቡን ለመምራት ሁለት ዋና ዋና መሣሪያዎችን ሰጥቷቸው ነበር፡፡ የመጀመሪያው፥ የእግዚአብሔር የደመና ክብር ነበር። ይህ ደመና የእግዚአብሔር ሕልውና ምልክት ነበር። በቀን ደመና፥ በማታ ደግሞ እሳት ይሆን ነበር። ደመናው የመገናኛውን ድንኳን ለቆ በሰማይ ላይ በሚሆንበት ጊዜ፥ ሕዝቡ የነበሩበትን ስፍራ ለቀው፥ ደመናውን እየተከተሉ በመሄድ የሚቀጥለውን የሰፈራ ስፍራ እስኪያገኙ ድረስ መንቀሳቀስ፥ ደመናው ከመገናኘው ድንኳን ላይ እስካልተነሣ ድረስ ግን በዚያው መቆየት እንዳለባቸው ያውቁ ነበር።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔር እንመራበት ዘንድ ለእኛ የሰጠን ምንድን ነው? ለ) እግዚአብሔር አንድን ጉዳይ በሚመለከት ግልጽ የሆነ መመሪያ ለአንተ የሰጠበትን ጊዜ ጥቀስ። ሐ) ምን ዓይነት የአመራር መንገድ በመስጠት ነበር የተጠቀመው?

ሁለት ልዩ መለከቶችን ሠርቶ ለካህናቱ እንዲሰጥ እግዚአብሔር ሙሴን አዝዞት ነበር። ሁለቱም መለከቶች በሚነፉበት ጊዜ ሕዝቡ ሙሴ ወደሚገኝበት ወደ መገናኛው ድንኳን ይመጣል። አንዱ መለከት ብቻ ሲነፋ፥ ወደ ሙሴ የሚመጡት መሪዎች ብቻ ነበሩ። እነዚህ መለከቶች ጉዞ ለመጀመር ምልክት ለመስጠትና በተጨማሪ ጠላቶች ካሉ ለውጊያ ለማዘጋጀት ይጠቀሙ ነበር፤ እንዲሁም ለተለዩ ሃይማኖታዊ በዓላት ምልክት በመሆንም ያገለግሉ ነበር። 

  1. እስራኤል ከሲና ተራራ ተነሥተው ወደ ቃዴስ በርኔ እንደተጓዙ (10፡11-12፡16)

ሕዝቡ በሲና ተራራ 11 ወራት ከቆዩ በኋላ፥ ወደ ከነዓን ለመሄድ ጉዞ ጀመሩ። ይህ ጉዞ ጥቂት ወራት ብቻ የሚፈጅ ነበር። ነገር ግን 38 ዓመታት ፈጀ። እስራኤላውያን ከሲና ተራራ የከነዓን ምድር ደቡባዊ ጫፍ ወደ ሆነችው ወደ ቃዴስ በርኔ ለመድረስ የፈጀባቸው 11 ቀናት ብቻ ነበር። ነገር ግን እነዚህ 11 ቀናት በኃዘንና በእግዚአብሔር ላይ በማመፅ የተሞሉ ነበሩ። እስራኤላውያን ወደ ቃዴስ በሚጓዙበት ጊዜ ስለተፈጸሙት ነገሮች የሚከተሉትን አስተውል፡-

ሀ. የሲና ተራራ፡- ሰፈሩ ከተደራጀና የጉዞ ትእዛዝ ከተላለፈ በኋላ፥ የእግዚአብሔር ደመና ከመገናኘው ድንኳን ላይ ተነሥቶ ሕዝቡ ለጉዞ ተዘጋጀ። ሙሴም ሕዝቡን ወደ ከነዓን እንዲመራ የአማቱን የራጉኤልን ልጅ ኦቦብን ጠየቀው። (ማስታወሻ፡- ራጉኤል የዮቶር ሌላው ስም ነው) (ዘጸ.2፡18፤ 3፡)። 

ለ. ተቤራ ወይም የምኞት መቃብር (ዘኁ.10፡33-11፡35)፣ በዚህ ስፍራ ሦስት ዋና ዋና ነገሮች ተፈጸሙ፡-

  1. ሕዝቡ በእግዚአብሔር ላይ ስላጉረመረሙ ከሰማይ የመጣ የእግዚአብሔር እሳት አንዳንዶቹን ገደለ። 
  2. ሕዝቡ ከመና ሌላ የሚበላ ነገር ስለፈለጉ በእግዚአብሔር ላይ አጉረመረሙ። የእግዚአብሔር የቸርነት ስጦታ የሆነውን መና እምቢ በማለታቸው እግዚአብሔር ይበሉ ዘንድ ድርጭትን ላከላቸው፤ ነገር ግን «ከግብፅ ለምን ወጣን» በማለት ጌታን ስላልፈለጉ ብዙዎቹ ሞቱ።

iii. ሙሴ ሕዝቡን በመምራት ይረዱት ዘንድ ሰባ ሰዎችን መረጠ። የተመረጡት በሙሴ ብቻ ሳይሆን በእግዚአብሔር መሆኑን ለማረጋገጥ የእግዚአብሔር መንፈስ ወረደባቸው። 

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ከእነዚህ ቁጥሮች ስለ እግዚአብሔር የምንማረው ነገር ምንድን ነው? ) እኛም ራሳችን አንዳንድ ጊዜ የእግዚአብሔርን የጸጋ ስጦታዎች በመቃወም ጥፋተኞች የምንሆነው እንዴት ነው?

  1. ሐዴሮት (12፡1-16)

በሐዴሮት አንድ ያልታሰበ ነገር ተፈጸመ። የእስራኤልን ሕዝብ ለመምራት እግዚአብሔር በሙሴ ስለ ተጠቀመ፣ ወንድሙ አሮንና እኅቱ ማርያም ቀኑበት። በከፊል የቀኑበት ምክንያት ኢትዮጵያዊ በማግባቱ ነበር። አንዳንድ ምሁራን ሙሴ ኢትዮጵያዊቱን (ኩሻዊቱን) ያገባው የመጀመሪያ ሚስቱ ስለሞተችበት ነው ይላሉ። (ማስታወሻ፡- በብሉይ ኪዳን ኢትዮጵያ (ኩሽ) የተባለው ስፍራ ዛሬ የምናውቀው የኢትዮጵያ ክፍል ሳይሆን በደቡብ ግብፅ የሚገኝ ክፍል ነው።) በተጨማሪም ክብሩን ሁሉ ሙሴ ማግኝቱ ትክክል አይደለም ብለው አሰቡ። እግዚአብሔር ከእነርሱም ጋር ተነጋግሯልና!

የእግዚአብሔር ምላሽ ጠንከር ያለ ነበር። ወደ መገናኛው ድንኳን ጠራቸውና በሙሴ ላይ ለመናገር መብት እንደሌላቸው ነገራቸው። ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ፊት ለፊት በመነጋገር የተለየ ዕድል ነበረው። ስለዚህ በሙሴ ላይ ለተፈጸመው ዓመፅ አነሣሽ እንደሆነች የምንጠራጠራትን ማርያምን እግዚአብሔር ቀጣት። ማርያምም ለምፃም ሆነችና እስራእላውያን ከሰፈሩበት ሰፈር ውጭ ለ7 ቀናት እንድትቆይ ሆነ፡፡ ሙሴም ስለ ጸለየላት እግዚአብሔር በምሕረቱ ፈወሳት።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በመሪዎች መካከል ስለሚሆነው መቀናናት ከዚህ ታሪክ የምንማረው ነገር ምንድን ነው? ) አንዳንድ መሪዎች በሌሎች ላይ የሚቀኑት ለምንድን ነው? ሐ) በአመራር ስፍራ ላይ በምንሆንበት ጊዜ ክብርን ለራሳችን የምንፈልገው ለምንድን ነው? መ) ቅንዓት ክፉ ለለመሆኑ ከዚህ ታሪክ ምን መማር እንችላለን?

መ.በፋራን ምድረ በዳ የሚገኘው ቃዴስ በርኔ (ዘኁ.12፡16) 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version