ዘዳግም 12-26

ብዙ ሰዎች እግዚአብሔርን የሚገደው ለእርሱ ስላለን አምልኮ ብቻ ነው ይላሉ። በአእምሮአቸው «መንፈሳዊ» የሆነውን ነገር «ሥጋዊ» ከሆነ ነገር ይለያያሉ። እግዚአብሔር ግን ይህንን ልዩነት አላደረገም። እንዲያውም የምናደርጋቸው ነገሮች በሙሉ በእግዚአብሔር ዓይን መንፈሳዊ ናቸው። በ1ኛ ቆሮ.10፡31 ጳውሎስ “እንግዲህ የምትበሉ ወይም የምትጠጡ ብትሆኑ፥ ወይም ማናቸውንም ነገር ብታደርጉ ሁሉን ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” ይላል። ስለዚህ እግዚአብሔር ግድ የሚለው አምልኮአችን ብቻ ሳይሆን ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር ስላለን ግንኙነትም ነው። ከማያምኑ ጋር ባለንም ግንኙነት ደስ ይለዋል። እግዚአብሔር እንዴት እንደምንሠራና እንደምናስተዳድር ያያል። እግዚአብሔርን የማይመለከተውና መመሪያ ያልሰጠበት አንዳችም የሕይወት ክፍል የለም። በኦሪት ዘዳም፥ ስለ አምልኮና ስለ ሃይማኖታዊ በዓላት የተሰጡ ሕግጋትን እናገኛለን። ስለ ንግድ፣ ጋብቻ፣ ምግብ፣ ከምድር ስለሚገኝ ፍሬ፥ ስለ ቤተሰብ ሕይወት፥ ወደ ጦርነት ስለ መሄድ፥ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ስለ መምራት ወዘተ የሚናገሩ ሕግጋትንም እናገኛለን። እኛ ግን ብዙ ጊዜ እግዚአብሔርን የሚያከብር ወይም የማያከብር ነገር እናደርጋለን፤ ልዩነቱ የሚመነጨው በውስጣችን ካለው ስሜታችን ነው። አንድ ነገር በእግዚአብሔር ተቀባይነት እንዲያገኝ ከተፈለገ ድርጊት ብቻ ሳይሆን የድርጊቱ ዓላማም ጭምር በእግዚአብሔር ፊት የተስተካከለ መሆን ይኖርበታል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ብዙ ጊዜ የምናደርጋቸውና እግዚአብሔር አያገባውም የምንላቸው የተለመዱ ነገሮችን ዘርዝር። ለ) እነዚህ ነገሮች እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ እንዴት ሊደረጉ እንደሚችሉ መግለጫ ስጥ። ሐ) ለእግዚአብሔር ክብር በማያመጣ መንገድም እንዴት ሊፈጸሙ እንደሚችሉ ምሳሌዎችን ስጥ። 

የዉይይት ጥያቄ፥ ዘዳግ. 12-26 አንብብ። ሀ) እግዚአብሔር መመሪያ የሚሰጥባቸውን የተለያዩ የሕይወት እንቅስቃሴዎችን ከእነዚህ ትእዛዛት አንዳንዶቹን ዛሬም እንዴት ከሕይወታችን ጋር እንደምናዛምድ ምሳሌ ሰጥ።

እነዚህን ትእዛዛት ለማብራራት ጊዜ አንወስድም። ነገር ግን ያልተረዳሃቸው አንዳንድ ቢኖሩ፥ ዝርዝራቸውን ጻፍና በሳምንታዊው የስብሰባ ወቅት ከቡድን አባላት ጋር ተወያይባቸው።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: