Site icon

ታሪካዊ መጻሕፍትን እንዴት እንደምንተረጉማቸው?

ብዙ ክርስቲያኖች የመጽሐፍ ቅዱስን ታሪካዊ መጻሕፍት እንዴት እንደሚተረጉሙና በተለይም ከሕይወታቸው ጋር እንዴት እንደሚያዛምዱ ባለማወቅ ይቸገራሉ። ከእኛ ባሕል ጨርሶ ልዩ በሆነ ባሕል ውስጥ ብዙ ያልተለመዱ ስሞች፥ ቦታዎችና ክስተቶች ይኖራሉ። ስለዚህ ብዙ ጊዜ በቀላሉ ከሕይወታችን ጋር ልናዛምዳቸው የምንችላቸውን ታሪኮች የመምረጥና የቀረውን የመጽሐፍ ቅዱስ የሥነ መለኮት ትምህርት ቸል የማለት ዝንባሌ ይታይብናል።

እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን እንዲጽፉ ሰዎችን ሲመራ፥ ከሁሉም በላይ የተጠቀመበት የተለመደው መንገድ (የሥነ ጽሑፍ ዓይነት) ታሪክ ነው፤ ስለዚህ እግዚአብሔር ራሱን የሚገልጥበት ከሁሉ የተሻለው መንገድ ይህ ከሆነ፥ እነዚህ ታሪኮች ዛሬም ለሕይወታችን ጠቃሚ የሚሆኑበትን መንገድ መረዳት በጣም አስፈላጊ ነው። የታሪክ መጻሕፍትን በምታጠናበትና ከሕይወትህ ጋር ለማዛመድ በምትሞክርበት ጊዜ ልትከተላቸው የሚገቡ መመሪያዎች ከዚህ በታች ቀርበዋል፡-

  1. የቅዱሳት መጻሕፍት (የታሪክን መጻሕፍት ጨምሮ) ዓላማ የእግዚአብሔርን ዓላማዎችና ባሕርያት ለእኛ መግለጥ ነው። በእያንዳንዱ ታሪክ ውስጥ በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ ስለ እግዚአብሔር ወይም ከሰዎች ጋር ስላለው ግንኙነት አንድ ነገር እንማራለን። የቀድሞ ሰዎች እግዚአብሔርን እንዴት ደስ እንዳሰኙት በማየት እግዚአብሔርን እንዴት ደስ እንደምናሰኝ እንማራለን። ኃጢአት የቀድሞ ሰዎችን እንዴት እንዳጠፋቸውና እግዚአብሔር ኃጢአተኛን እንዴት እንደቀጣ በመመልከት ኃጢአት ስለሚያመጣው ነገር እንማራለን።
  2. በታሪክ መጻሕፍት ውስጥ በተናጠል ሊታዩ የሚችሉ የተለያዩ በርካታ ታሪኮች ቢኖሩም፥ እነዚህ ታሪኮች በመጽሐፍ ቅዱስ ወይም በእያንዳንዱ መጽሐፍ ውስጥ የአንድ ትልቅ ዓላማ አካል መሆናቸውን መረዳት በጣም አስፈላጊ ነው። ለምሳሌ፡- 2ኛ ሳሙኤል የተጻፈው የዳዊትን ታሪክ ለመናገር ብቻ አይደለም። ነገር ግን ስለ ዳዊት ታሪክ በምናነብበት ጊዜ፥ ስለ እግዚአብሔር፥ ስለ ኃጢአትና እግዚአብሔር፥ ስለ ሕዝቡ ዓላማ በርካታ ታላላቅ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶችን እንድንማር ነው። የታሪክ መጻሕፍትን በምታነብበት ጊዜ፥ እያንዳንዱ ታሪክ በሦስት ደረጃ የሚታዩ እውነቶችን እንደሚያስተምር አስታውስ፤ እነዚህም፡-

ሀ. በጣም አስፈላጊው (በከፍተኛው ደረጃ)፡- በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙ ታሪኮች እያንዳንዳቸው መጽሐፉ እግዚአብሔርንና አጠቃላይ ዕቅዱን የሚገልጥባቸው አካል ናቸው። ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን በምናጠናበት ጊዜ ልንወስደው የሚገባ የመጀመሪያ እርምጃ፡- ያ የምናጠናው ታሪክ እግዚአብሔር በድነት (ደኅንነት) ውስጥ ባለው ዓላማ፥ የእግዚአብሔርን ባሕርይ በመግለጥ ረገድ ባለን ግንዛቤ፣ እርሱ ከሰዎች ጋር ስላለው ግንኙነት ባለን መረዳት ወዘተ. ላይ የሚጨምረው ነገር ምን እንደሆነ መመልከት ነው። 

የውይይት ጥያቄ፥ መጽሐፈ ኢያሱ 6ን ተመልከት። ይህ ታሪክ በዘመናት ሁሉ ያለውን የእግዚአብሔርን ባሕርይና ዓላማ ለመረዳት እንዴት ይጠቅማል?

ለ. የታሪኩ መካከለኛ ደረጃ የመጽሐፍ ቅዱስን ዋና ዋና አሳቦችን ያመለክታል። ለምሳሌ፡- ይህ መካከለኛ ደረጃ በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ሕዝብ እነማን እንደነበሩና (እስራኤላውያን) የእግዚአብሔር ዓላማ ለእነርሱ ምን እንደነበረ ይናገራል። አዲስ ኪዳን ደግሞ ስለ ቤተ ክርስቲያንና እግዚአብሔር ለእርስዋ ስላለው ዓላማ ይናገራል። የአብርሃም ጥሪ፥ ቀይ ባሕርን መሻገር፥ የጰንጠቆስጤ ቀን ወዘተ.፥ ስለ እግዚአብሔርና ስለ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ግንዛቤ እንዲኖረን ደግሞም እግዚአብሔር ለእነርሱ ያለውን ዓላማና እያደረገላቸው ያለውን ነገር ለመረዳት በጣም ይረዳናል። ስለዚህ በሁለተኛ ደረጃ አንድን ታሪክ በምንተረጉምበት ጊዜ፥ መወሰን ያለብን እነዚህ ታሪኮች ለእነዚህ ዋና ዋና አሳቦች የሚያበረክቱት አስተዋጽኦ ምን እንደሆነ ነው፤ (ለምሳሌ፡- ድነት (ደኅንነት)፥ የሰው ልጅ ኃጢአት፥ ኃጢአት በዓለም ላይ ስላመጣው ነገርና የመታዘዝ በረከት ወዘተ. ናቸው)። 

የውይይት ጥያቄ፥ መጽሐፈ መሳፍንትን አንብብ። ይህ ታሪክ እግዚአብሔር ለእስራኤል ሕዝብ ስላለው ዓላማ ባለን ግንዛቤ ላይ የሚጨምረው ነገር ምንድን ነው?

ሐ. ዝቅተኛው የታሪክ ደረጃ የሚያመለክተው በተለይ በእያንዳንዱ ታሪክ ውስጥ ያለውን ትምህርት ነው፤ ለምሳሌ፡- በሳምሶን ታሪክ ውስጥ የእግዚአብሔርን ሥራ በምንሠራበት ጊዜ ስለ ቅድስና አስፈላጊነት ጸሐፊው ሊያስተምረን የፈለገው ነገር ምን እንደሆነ ወዘተ.።

የውይይት ጥያቄ፥ መጽሐፈ ሩት ምዕ. 2ን አንብብ። ይህ ታሪክ ሊያስተምረን የሚሞክረው ነገር ምንድን ነው?

በታሪኩ ውስጥ በተናጠል የምናገኘውን ትምህርት (መመሪያ) መፈለግ ያለብን ታሪኩ የሚያስተምራቸውን ታላላቅ እውነቶች አስቀድመን ከተረዳን በኋላ መሆን አለበት። ታሪካዊ መጻሕፍትን በተገቢ ሁኔታ ለመተርጎም ከፍተኛውን፥ መካከለኛውንና የመጨረሻውን የታሪክ ደረጃ ትርጉም መረዳታችንን ማረጋገጥ አለብን። 

ታሪካዊ መጻሕፍትና ታሪኮች በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ የተጨመሩበት የራሳቸው የሆነ ልዩ ዓላማ አላቸው። ዓላማቸው በተናጠል ታሪኮቹን እንድናውቅ ብቻ አይደለም። ይልቁንም እነዚህ ታሪኮች እያንዳንዳቸው ትላልቅ እውነቶችን እንድንረዳ ሊያደርጉን የታሰቡ ናቸው። ስለዚህ ታሪካዊ መጻሕፍትን በምናጠናበት ጊዜ በታሪኮች ውስጥ በተደጋጋሚ የሚመጡትን ዋና ዋና ሐሳቦች ወይም እውነቶች መፈለግ አለብን። ይህ ሲሆን ብቻ ነው የታሪኩን ዓላማ ለመረዳት የምንችለው።

  1. እያንዳንዱ የብሉይ ኪዳን ታሪክ ለአንድ ለተለየ ዓላማ የተመረጠና ስለ እግዚአብሔርና ስለ ብሉይ ኪዳን ታሪክ ባለን መረዳት ላይ ልዩ የሆነ ሚና የሚጫወት ወይም ተጨማሪ ነገርን የሚያክል ነው። የቅዱሳት መጻሕፍት ጸሐፊዎች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሊያካትቱት የሚችሉዋቸው በርካታ ታሪኮች ቢኖሯቸውም እነዚህን ተጨማሪ ታሪኮችን ዘልለዋቸዋል። ለምን? ምክንያቱ ሌሉቹ ታሪኮች፥ ለአጠቃላዩ የሥነ መለኮት ትምህርት ዓላማ፥ ለመጽሐፉ የሚያበርክቱት አስተዋጽኦ ስላልነበራቸው ነው። ጸሐፊዎቹ ሁሉ እያንዳንዱን ታሪክ በከፍተኛ ጥንቃቄ መረጡ፤ ስለዚህ በእያንዳንዱ ታሪክ ውስጥ ያለው ይህ ልዩ ዓላማ ምን እንደሆነ ለመረዳት መሞከር አለብን። አንዳንዶቹ ታሪኮች ለመረዳት አስቸጋሪ ቢሆኑም እንኳ፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተካተቱበትን ምክንያት ከተረዳን እግዚአብሔርን የበለጠ እንረዳዋለን።
  2. የታሪክ መጻሕፍት ዓላማ እንደ ሰምና ወርቅ ያሉ የተደበቁ እውነተችን ለማስተማር አይደለም። ነገር ግን መንፈሳዊ እውነተችን በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ውስጥ ለመግለጥ ነው። ስለዚህ መፈለግ ያለብን የተደበቁ ምሥጢሮችን ሳይሆን፥ በታሪኩ ውስጥ የሚገኙ ግልጥ የሆኑ ጠቅላላ መንፈሳዊ የሥነ – ምግባር ሕግጋትን ወይም እምነቶችን ነው። እግዚአብሔር እነዚህን ጠቅላላ የሥነ ምግባር ሕግጋት ወይም እምነቶች በቀጥታ ከመስጠት ይልቅ በግለሰቦች ተግባራዊ ሕይወት ውስጥ መግለጥ እንደሚሻል ያውቅ ነበር። ይህ መንገድ እነዚህ መንፈሳዊ የሥነ – ምግባር ሕግጋት ወይም እምነቶች አኗኗራችንን እንዴት እንደሚለውጡት ለማወቅ የሚረዳ ነው።
  3. ታሪኮችን በምንተረጉምበት ጊዜ ታሪኩ የሚያስተምረን በአዎንታዊ ወይም በአሉታዊ ምሳሌነት እንደሆነ አስቀድመን መወሰን አለብን። አንዳንዶቹ ታሪኮች በእምነት እንዴት መኖር እንደሚቻል ምሳሌዎችን ይሰጣሉ፤ ስለዚህ በሕይወታችን ልናካትተው የሚገባ አዎንታዊ ምሳሌ ነው። ሌሎች ምሳሌዎች ለምሳሌ በመጽሐፈ መሳፍንት 19 ስለ አንድ ሌዋዊና ቁባቱ የተጻፈው ነገር የሚያስተምረን በአሉታዊ ምሳሌነቱ ነው። በታሪኩ ውስጥ እግዚአብሔር የሰዎቹን ተግባር በምንም ዓይነት እየደገፈ አይደለም። ይልቁንም እግዚአብሔር የተፈጸመውን ተግባር በግልጥ ይናገራል። የተፈጸመውን ታሪክ ምሳሌነት መከተል እንዳለብንና እንደሌለብን የምንወስነው ከተግባሩ ውጤት ነው። 
  4. በታሪክ መጻሕፍት ውስጥ የምናገኛቸው ታሪኮች የቀረቡት በአጭሩ ነው። ስለ ተፈጸሙት ድርጊቶች የሚኖረንን ጥያቄ ሁሉ ለመመለስ የቀረቡ አይደሉም፤ ጠቃሚ ትምህርቶችን ለማቅረብ ብቻ የተጻፉ ናቸው። በታሪኩ ውስጥ በግልጥ ስላልተነገሩ ነገሮች አትጨነቅ (ለምሳሌ፡- ቃየል ሚስት ያገኘው ከየት ነው?) ይልቁንም፥ አስፈላጊ የሆነው ነገር በታሪኩ ውስጥ የሚገኙትን ዋና ዋና ትምህርቶች መረዳትና ከሕይወት ጋር ማዛመድ ነው።
  5. አብዛኛዎቹ የብሉይ ኪዳን ታሪኮች ለእኛ ያልተለመዱ ባሕላዊ ነገሮችን ያካተቱ ስለሆኑ ታሪኩን ለመረዳት በምናደርገው ሙከራ፥ ለእኛ ያልተለመዱ ባሕላዊ ነገሮችን መረዳታችንን ማረጋገጡ አስፈላጊ ነው (ለምሳሌ፡- ሩት ቦኤዝን «ልብስህን በባሪያህ ላይ ዘርጋ» [ሩት 3፡9] ስትለው ምን ማለቷ እንደ ነበር …)። በተጨማሪ ከራሳችን ባሕል ጋር ተመሳሳይ የሆነ፥ በዕብራውያን ባሕል ግን የተለየ ትርጉም ያለውን ነገር መረዳታችንን ማረጋገጥ አለብን፤ (ለምሳሌ፡- ለአይሁድ የእረኝነት ሥራ የተከበረ ነው፤ በብዙ ኢትዮጵያውያን ዘንድ ግን ያልተማሩ ሰዎች ወይም የልጆች ኃላፊነት እንደሆነ ስለሚቆጠር ይህን ያህል የተከበረ አይደለም)።

ታሪካዊ መጻሕፍትን በምታነብበትም ሆነ በምትተረጉምበት፥ ደግሞም ከመጻሕፍቱ በምታስተምርበት ጊዜ እነዚህን መመሪያዎች ተጠቀም፡- እግዚአብሔር እነዚህን የታሪክ መጻሕፍት ሲሰጥ ምን ሊያስተምረን እንደሆነ በመጀመሪያ ማወቅ አስፈላጊ መሆኑን አስታውስ። ይህ ሲሆን ብቻ ትርጉማችን የእግዚአብሔር ቃል መሆኑንና ስናስተምረውም የእግዚአብሔር ሥልጣን እንዳለው እርግጠኞች መሆን እንችላለን። 

የውይይት ጥያቄ፤ ሀ) የእግዚአብሔር ቃል በተገቢው መንገድ መተርጎም የሚያስፈልገው ለምንድን ነው? ለ) አንድን ታሪክ በተሳሳተ መንገድ በመተርጎም በርካታ ስሕተቶችና ሐሰተኛ ትምህርቶች ሊጀምሩ የሚችሉት እንዴት ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version