መሳፍንት 1-16

ብዙ ጊዜ የቤተ ክርስቲያን ችግር በእግዚአብሔር ላይ የሚደረግ ግልጥ ዓመፅ ሳይሆን ለእግዚአብሔር ሙሉ ለሙሉ አለመታዘዝ ነው። እግዚአብሔርን ሙሉ ለሙሉ አላመልክም ማለት ሳይሆን፤ ነገር ግን ለእግዚአብሔር ፈቃድ በከፊል ብቻ መታዘዝ የእግዚአብሔር ሕዝብ ችግር ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ በቤተ ክርስቲያን ወይም በራስህ ሕይወት ውስጥ ይህ ነገር እውነት መሆኑን ያየኸው እንዴት ነው? ምሳሌዎችን ስጥ። 

ለእግዚአብሔር በከፊል መታዘዝ፥ ቆይቶ ወዳለመታዘዝ ያመራል። እግዚአብሔር ልንከተለው የሚገባንን ትእዛዝ ወይም ልናደርገው የሚያስፈልግ ነገር ሲሰጠንና ያንንም በከፊል ብቻ ስንከተል መንፈሳዊ ውድቀት በሕይወታችን ይጀምራል። በቤተ ክርስቲያንም ተመሳሳይ ነገር ይከሰታል። በከፊል መታዘዝ ከዓለም ጋር ጓደኝነት ወደ መፍጠር ነው የሚመራው። ቤተ ክርስቲያንም ሆነች ክርስቲያን በግሉ ዓለምን መምሰል ይጀምራል፤ ክርስቲያን ወይም ቤተ ክርስቲያን የሥነ ምግባር ንጽሕናቸውንና ልዩ መሆናቸውን እያጡ ይሄዳሉ። ይህም ነገር ወዲያውኑ ዓለምንና ቤተ ክርስቲያንን ወደ ቅልቅል አምልኮ ይመራል። በመጨረሻም እግዚአብሔርን ሙሉ ለሙሉ ወደ መካድና ወንጌልን ወደ መቃወም ያደርሳል።

መጽሐፈ መሳፍንት እስራኤላውያን ለእግዚአብሔር እንዴት ሙሉ በሙሉ እንዳልታዘዙና እርሱ እንዳዘዘውም ከነዓናውያንን እንዳላባረሩ ያሳየናል። ስለሆነም እግዚአብሔርን የመቃወም ሂደታቸው ተጀመረ። በመጀመሪያው እንደ ከነዓናውያን ማምለክ ጀመሩ። ይህም የእግዚአብሔርን ሕዝብ ወደ ከፍተኛ የሥነ-ምግባር ድቀት መራቸው። ወዲያውኑ ከነዓናውያን ይጨቁኗቸው ጀመር። እግዚአብሔር የእርሱ ወደሆነው ንጹሕ አምልኮ ሊመራቸው ጠላቶቻቸውን ድል ይነሣ ዘንድ ፈቀደ። ይህ ነገር ለጊዜው የሠራ ቢሆንም እንኳ እያንዳንዱ ተከታታይ ትውልድ እግዚአብሔርን በመተዉ እግዚአብሔር የሥነ-ሥርዓት እርምጃ ይወስድበት ጀመር።

የውይይት ጥያቄ፥ ምሳ. 1-16 አንብብ። ሀ) እስራኤላውያን ለእግዚአብሔር ያልታዘዙት እንዴት ነው? ለ) ሕዝቡ ባለመታዘዛቸው ምክንያት የጌታ መልአክ ያዘዘባቸው ፍርድ ምን ነበር፤ ሐ) በመሳ. 2፡10-19 የምታየውን የክሕደትን ዑደት፥ ፍርድና ነጻ መውጣት ግለጥ። መ) ከመሳፍንት 1-16 የእስራኤልን ሕዝብ ያሸንፉ ጠላቶችና በእነዚህ ጠላቶች ላይ ድልን ይሰጣቸው ዘንድ እግዚአብሔር ያስነሣቸውን መሳፍንት ዘርዝር። ሰ) መንፈስ ወረደባቸው ተብሎ የተጻፈላቸውን ሰዎች ዘርዝር።

  1. የዘመነ መሳፍንት መግቢያ (መሳ. 1-3፡6)። 

ሀ. እግዚአብሔር እስራኤላውያንን በጠላታቸው ሁሉ ላይ ድልን እንዴት እንደሰጣቸው ለማሳየት የቀረቡ ምሳሌዎች (መሳ.

1፡1-18)

አይሁዳውያን ጠላቶቻቸውን ለማሸነፍና ከምድሪቱ ለማባረር ያልቻሉበት ምክንያት ምንድን ነው? ኃይል ስላነሳቸው ነውን? ወይስ በጌታ ርዳታ ሊያባርሩአቸው ስላልሞከሩ ነው? ወይስ የጌታን ትእዛዝ በከፊል ብቻ በመታዘዝ ስለበደሉ? ወይስ እግዚአብሔር በከነዓናውያን ላይ ድልን እንደሚሰጣቸው የገባውን ተስፋ ስላጠፈ ነው?

በዚህ ክፍል የመጽሐፈ መሳፍንት ጸሐፊ ሊያሳየን የፈለገው፥ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ስለ ነበር አይሁድን ለመቋቋቋም የቻለ ማንም ሰው እንዳልነበረ ነው። በይሁዳና በከነዓናውያን መካከል የተደረገውን ጦርነት በምሳሌነት በማቅረብ፥ አይሁድ በቀላሉ እንዴት ሊያጠፏቸው እንደቻሉ ያሳየናል። እንዲሁም አንድ ሰው በእግዚአብሔር እርዳታ አንድን ከተማ እንዴት እንዳሸነፈ አሳይቷል። የካሌብ ልጅ የሆነው የናትናኤል ታሪክ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸውን ሁሉ ያሸንፉ ዘንድ ለማድረግ ፈቃደኛ እንደ ነበር የሚያሳይ ማረጋገጫ ነው።

ለ. አይሁድ ከነዓናውያንን ለማሸነፍና ለማጥፋት አልቻሉም ነበር (መሳ. 1፡18-36) አይሁድ ከነዓናውያንን ሊያሸንፉ ያልቻሉበትን ምክንያት በእግዚአብሔር ላይ ከማሳበብ ይልቅ እራሳቸው እግዚአብሔርን ሙሉ በሙሉ ለመታዘዝ አለመቻላቸው እንደሆነ መገንዘብ ነበረባቸው። ከእስራኤል ነገዶች ማናቸውም ቢሆኑ ለእግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ ለመታዘዝ አልቻሉም ነበር፤ ስለዚህ በእያንዳንዱ ነገድ አካባቢ ያልተሸነፉና ያልጠፉ የከነዓናውያን ከተሞች ነበሩ።

ሐ. ሕዝቡ ሙሉ በሙሉ ባለመታዘዛቸው ምክንያት እግዚአብሔር ያመጣው ፍርድ (መሳ. 1፡1-5) አንድ ቀን እግዚአብሔር በእስራኤላውያን ላይ ለመፍረድ ተነሣ። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑ የሚታመነው የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ባለመታዘዛቸው ምክንያት ከነዓናውያንን ከእንግዲህ ማሸነፍ እንደማይችሉ ነገራቸው። ከነዓናውያንንና የአምልኮ ስፍራቸውን በሙሉ ስላላጠፉ፥ ከእንግዲህ እግዚአብሔር በከነዓናውያን ላይ ሙሉ ድልን እንደማይሰጣቸው ነገራቸው።

የውይይት ጥያቄ፥ ለእግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ መታዘዝ እንዳለብን ይህ ነገር ብርቱ ማስጠንቀቂያ እንዴት ይሆነናል?

ለእግዚአብሔር በከፊል መታዘዝ ሙሉ በሙሉ አለመታዘዝ ነው። ያልታዘዝናቸው አንዳንድ ነገሮች መኖራቸውን እያወቅን፥ ለእግዚአብሔር በታዘዝንባቸው ነገሮች መመካት አንዳችም ረብ የለውም። በከፊል መታዘዝ አለመታዘዝ ስለሆነ፥ በእኛ ላይ የእግዚአብሔርን ፍርድ ያመጣል።

መ. የክሕደት፥ የፍርድና ነፃ የመውጣት ዑደት (መሳ. 2፡6-3፡6)

በመሳፍንት 3፡1-6 ከነዓናውያን ሙሉ በሙሉ እንዲጠፉ እግዚአብሔር ያልፈቀደበትን ሌላ ምክንያት እናገኛለን። እግዚአብሔር የሚቀጥለው የእስራኤል ትውልድ ለቃል ኪዳኑ ይታዘዝና ይከተለው ወይም አይከተለው እንደሆነ ለመፈተን ይህንን ሕዝብ ሊጠቀምበት ፈለገ። የሚያሳዝነው፥ እያንዳንዱ ትውልድ ዓለምን (ከነዓናውያንን) ወደ መምሰል አዘነበለ፤ በአምልኮውና በሥነ ምግባሩም የተበላሸ ሆነ።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዛሬም እግዚአብሔር ለእርሱ ያለንን ፍቅር የሚመዝንባቸው መንገዶች የትኞቹ ናቸው? ያ ብዙ ክርስቲያኖች በዚህ ፈተና የሚወድቁት ለምንድን ነው?

በዚህ ክፍል፥ የመጽሐፈ መሳፍንት ጸሐፊ በዚህ ዘመን ውስጥ የእስራኤል ሕዝብ ያለፈበትን የታሪክ ዑደት ያሳየናል። በመጀመሪያ፥ አይሁድ ሌሎች አማልክትን በማምለክ በእግዚአብሔር ላይ ዓመጹ። በሁለተኛ ደረጃ፥ እግዚአብሔር ሊቀጣቸውና ለእርሱ ወደሆነ አምልኮ ሊመልሳቸው ለጠላቶቻቸው አሳልፎ ሰጣቸው። ሦስተኛ፥ እስራኤላውያን ከጠላቶቻቸው ነፃ ያወጣቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ። አራተኛ ከጠላቶቻቸው የጭቆና አገዛዝ ነፃ የሚያወጡአቸውን መሳፍንት አስነሣላቸው። አምስተኛ፥ እስራኤላውያን በሰላም ጊዜ ደስ እያላቸው ኖሩ። በዚህ የሰላም ጊዜ ነበር እስራኤላውያን እንደገና በእግዚአብሔር ላይ ያመፁትና እርሱም ለጠላቶቻቸው ቀንበር አሳልፎ በመስጠት ይቀጣቸው።

  1. ዘመነ መሳፍንት (መሳ. 3፡7-16) 

ስማቸው ተጠቅሶ የምናገኘው 12 መሳፍንት ቢሆኑም፥ የተለየ ትኩረት የተሰጣቸው ስድስቱ ብቻ ናቸው።

  1. ጎቶንያል፡- የካሌብ ልጅ ሲሆን በቅድሚያ የተጠቀሰ ነው። የሌሎች መሳፍንት ተግባር የተመሠረተው በዚህ ሰው ምሳሌነት ላይ ነው። በጎቶንያል ታሪክ የመጽሐፈ መሳፍንት ጸሐፊ የሚተርከው የኃጢአት፥ የፍርድ፥ የንስሐና ነፃ የመውጣት ዑደትን ነው። ይህ ዑደት በመጽሐፈ መሳፍንት ሌላ ክፍል አምስት ጊዜ ተጠቅሶ ይገኛል። 
  2. ናዖድ፡- የዚህ ሰው ታሪክ በዝርዝር ተዘግቧል። እስራኤልን ነፃ ማውጣቱን ልዩ የሚያደርገው ሞዓባውያንን ለማሸነፍ ራሱ የሠራው ሥራ በመኖሩ ነው። ሌላው መለያው እጀ ግራኝ መሆኑ ነው፡፡
  3. የዲቦራና የባርቅን ታሪክ ልዩ የሚያደርገው ሴቶች በድሉ ውስጥ በተጫወቱት ልዩ ሚና ነው። ዲቦራ የእስራኤል መንፈሳዊ መሪ የነበረች ነቢይት ናት። ኢያዔል ደግሞ የከነዓንን ንጉሥ ኢያቢስን በመግደል የዚህ ድል ተሳታፊ ነበረች።
  4. በመጽሐፈ መሳፍንት ማዕከላዊ ታሪክ ላይ የጌዴዎንና የልጁን የአቤሜሌክን ታሪክ እናገኛለን። በዚህም ቦታ የጌታ መልአክ የተባለው (ክርስቶስ) ጌዴዎንን በመጥራትና በኃይል በማስታጠቅ ተግባር የተጫወተውን ሚና እንመለከታለን። በጌዴዎን ታሪክ ውስጥ ትኩረት የተሰጠው የእስራኤላውያንን ጦርነት እግዚአብሔር እንዴት እንዳሸነፈላቸው መናገር ነበር። ባደረጉት ነገር እንዳይመኩ፥ እግዚአብሔር ታላቅ ጦርን ለማሸነፍ 400 ሰዎችን ብቻ ተጠቀመ።

አይሁድ ለመጀመሪያ ጊዜ አንድን ሰው ንጉሥ ለማድረግ እንደሞከሩ እናያለን። ጌዴዎንን ንጉሣቸው እንዲሆን ጠየቁት፤ እርሱ ግን እምቢ አለ። ይህንን ያደረገው የሕዝቡ ንጉሥ መሆን ያለበት እግዚአብሔር ብቻ እንደሆነና እርሱም ሆነ ሕዝቡ፥ ሰብዓዊ ንጉሥ ከመፈለግ ይልቅ ለእግዚአብሔር ሥልጣን መገዛት እንዳለባቸው ያውቅ ስለነበረ ነው (መሳ. 8፡22-23)።

በጌዴዎን ታሪክ ውስጥ ሦስት የሚያሳዝኑ ነገሮች ተፈጽመዋል፡-

ሀ. መጀመሪያ፥ ጌዴዎን ከጠላቶቼ በተዋጋሁ ጊዜ አልረዳችሁኝም ብሉ የሱኮትን ከተማ ሲቀጣ እናያለን።

ለ. ሁለተኛው ጌዴዎን የወርቅ ኤፉድ መሥራቱ ነበር። ኤፉድ ካህናት የሚለብሱት በተለያየ ሕብር ያሸበረቀ ልብስ ነበር። ኤፉድ ብዙ ጊዜ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ የሚያገለግል መሣሪያ ነበር፤ (1ኛ ሳሙ. 23፡6-12)። ጌዴዎን ኤፉድ ለምን እንደሠራ ግልጽ አይደለም። ምናልባት የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ ተጠቅሞበት ይሆናል። በምንም መንገድ ይሁን ብቻ ወዲያውኑ ወደ አምልኮ ዕቃነት ተለወጠ። የእግዚአብሔር አምሳል ተደርጎ ተመልኳል፤ ወይም አንዳንድ ምሁራን እንደሚያስቡት፥ ኤፉድ በአንድ ጣዖት ላይ ይደረግና ሰዎች ወደዚያ በመምጣት ኤፉዱ የአማልክቶቻቸውን ፈቃድ እንደሚወስንላቸው ያምኑ ነበር።

እግዚአብሔር ጌዴዎንን በከፍተኛ ሁኔታ የተጠቀመበት ቢሆንም ይህ ነገር ለእርሱና ለቤተሰቡ የማሰናከያ ዓለት ሆነባቸው።

ሐ. የጌዴዎን ልጅ የሆነው አቤሜሌክ ራሱን አነገሠ። ይህም በእስራኤል ውስጥ የእርስ በርስ ጦርነት አስነሣ። አቤሜሌክንም አንዲት ሴት የወፍጮ ድንጋይ በራሱ ላይ ለቃ ገደለችው።

  1. ዮፍታሔ፡- በኅብረተሰቡ ተንቆና ተጠልቶ የነበረ ሰው ሲሆን የሚቀጥለው ዋና መስፍን ሆነ። በእርሱም ጊዜ ሁለት የሚያሳዝኑ ነገሮች ሆኑ። በመጀመሪያ፥ ከጦርነት አሸንፎ በሚመጣበት ጊዜ የሚያገኘውን የመጀመሪያውን ነገር ለእግዚአብሔር ለመሠዋት አደገኛ ስእለት ተሳለ። ጦርነቱን አሸንፎ በመጣ ጊዜ ያገኘው የመጀመሪያ ነገር ሴት ልጁ ስለነበረች፥ ስእለቱን መፈጸም ነበረበት። በዮፍታሔ ሴት ልጅ ላይ ስለተፈጸመው ትክክለኛ ነገር ምሁራን ይከራከራሉ። አንዳንዶች ዮፍታሔ ልጁን ለእግዚአብሔር ስለሰጠ፥ ድንግል ሆና በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የምታገለግል ሆነች ይላሉ። ሌሎች ደግሞ ዮፍታሔ ልጁን ለእግዚአብሔር ሠውቶ መሥዋዕት አቅርቧል ይላሉ። ሰውን በመሥዋዕትነት ማቅረብ በብሉይ ኪዳን የተከለከለ ቢሆንም (ዘሌ. 18፡21፤ ዘዳ. 18፡10-12)፥ ዮፍታሔ በልጁ ላይ ያደረገው ይህን ሳይሆን አይቀርም።

ሁለተኛ፡በዮፍታሔና በኤፍሬም ነገዶች መካከል ጦርነት ተቀሰቀሰ። በዚህም ከኤፍሬም ነገድ 42000 ሰዎች ሞቱ።

  1. በመጽሐፈ መሳፍንት ውስጥ የምናገኘው የመጨረሻው ትልቅ መስፍን ሶምሶን ነው። ሶምሶን ናዝራዊ ሆኖ እንደሚወለድ እግዚአብሔር ለወላጆቹ ስለነገራቸው ልደቱ ልዩ ነበር። ናዝራዊ ለተወሰነ ጊዜ ራሱን ለእግዚአብሔር አገልግሉት የለየ ሰው መሆኑን ታስታውሳለህ። የሶምሶን ናዝራዊነት ልዩ የሆነው የዕድሜ ልክ በመሆኑ ነው። ናዝራዊ በመሆኑም የወይን ፍሬ ውጤት የሆነ ማንኛውንም ነገር የማይበላ፥ ምንም ዓይነት ሬሳ የማይነካና ጠጉሩን የማይቆረጥ ነበር፤ (ዘኁ. 6፡1-21 ተመልከት)። የሚያሳዝነው ግን ሶምሶን እነዚህን ትእዛዝት ሁሉ አፍርሷል። ከፍልስጥኤማውያን ጋር ወይንን ሳይጠጣ አልቀረም፤ የሞተ አንበሳ ሬሳ ነክቷል።ጠጉሩን በተቆረጠ ጊዜ ግን እግዚአብሔር የሰጠው ኃይል ከእርሱ ተወሰደ። ሶምሶን መንፈስ ቅዱስና ታላቅ ኃይል የነበረው ቢሆንም፥ የሥነ ምግባር ሕይወቱ ግን በጣም የተበላሸ ነበር፤ ስለዚህ እግዚአብሔር እስራኤልን ለማዳን በሶምሶን ለመጠቀም ያሰበውን ያህል አልተጠቀመበትም። ለዚህ ነው ሶምሶን በእስራኤል ሕዝብ ላይ የነበረው መሪነት ፍልስጥኤማውያንን ማሸነፍና እንደገና በእነርሱ እጅ መውደቅና መገዛት የተደጋገመበት። ፍልስጥኤማውያን በእስራኤል ላይ የነበራቸው የበላይነት እስከ ዳዊት ዘመን ድረስ ቀጥሎአል።

የውይይት ጥያቄ፥ የእግዚአብሔርን ዓላማዎች ከግብ ለማድረስ መሪዎች ራሳቸውን በእግዚአብሔር ፊት በንጽሕና መጠበቃቸው አስፈላጊ እንደሆነ የሶምሶን ታሪክ እንዴት ያስጠነቅቀናል? 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ከተለያዩ መሳፍንት የምናገኛቸው አንዳንድ መንፈሳዊ ትምህርቶች ምንድን ናቸው? ለ) በእነዚህ ምዕራፎች ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ የምንማረው ነገር ምንድን ነው? 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “መሳፍንት 1-16”

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading