Site icon

መጽሐፈ ሩት መግቢያ

በየትኛውም ዘመን፥ ምንም ያህል ጊዜው ጨለማ ቢሆን፥ እግዚአብሔር የራሱ የሆኑ የተመረጡ ሕዝቦች አሉት። አብዛኛው ሕዝብ የሚኖረውን ኑሮ እየተቃወሙ፥ እግዚአብሔርን የሚያስከብርና ከፍ ከፍ የሚያደርግ ሕይወት የሚኖሩ ጥቂት ታማኞች አሉ፤ በመጽሐፈ ሩት ውስጥ የምናየው ነገር ይህ ነው። ዘመነ መሳፍንት በአጠቃላይ ሲታይ እጅግ የከፋ ቢሆንም፥ በእስራኤል ውስጥ እግዚአብሔርን ያከበሩ ጥቂት ሰዎች ነበሩ። መጽሐፈ ሩት የእነዚህን ጥቂት ሰዎች እምነትና እግዚአብሔር እንዴት ለእነርሱ መልካም እንዳደረገላቸው የሚያሳይ ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ በማንኛውም አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ለእግዚአብሔር የሆኑ ቅሬታዎች ወይም ጥቂት ታማኞች የመኖራቸውን እውነትነት በሕይወትህ እንዴት አየኸው? 

የውይይት ጥያቄ፥ በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ውስጥ መጽሐፈ ሩትን ተመልከት፤ ስለዚህ መጽሐፍ የሚናገራቸውን ዋና ዋና ነገሮች ዘርዝር። 

የመጽሐፈ ሩት ስያሜ

መጽሐፈ ሩት የተሰየመው በመጽሐፉ ታሪክ ዋና ገጸ ባሕርይ በሆነችው በሩት ነው። አስቴርን ጨምሮ በሴት ስም ከተሰየሙ ሁለት መጻሕፍት መካከል መጽሐፈ ሩት አንዱ ነው። 

የመጽሐፈ ሩት ጸሐፊ

የመጽሐፈ ሩት ጸሐፊ ማን እንደሆነ ከመጽሐፍ ቅዱስ የምናገኘው ምንም መረጃ የለም። የአይሁድ ትውፊት መጽሐፉን የጻፈው ሳሙኤል ነው ይላል። የመጽሐፉ የመጨረሻ ትኩረት በዳዊት ላይ ስለሆነ፣ ጸሐፊው ሳሙኤል አይመስልም። ስለዚህ በዳዊት ዘመነ መንግሥት፥ ወይም ከዚያ ጥቂት ራቅ ብሎ፥ እግዚአብሔር የዳዊትን የዘር ግንድ ለመጠበቅ እንዴት እንደሠራ ለመግለጽ የሚፈልግ አንድ ሰው እንደጻፈው ይገመታል። ሩት 1፡1 የዘመነ መሳፍንት ፍጻሜን የሚያሳይ ይመስላል። የዳዊት ስም በመጽሐፉ መጨረሻ መጠቀሱ ሕዝቡ ዳዊትን ያውቁት እንደነበር ያሳያል። 

የመጽሐፈ ሩት ታሪክ የተፈጸመበት ጊዜ

የመጽሐፈ ሩት ታሪክ የተፈጸመው በዘመነ መሳፍንት ነው። በዘመነ መሳፍንት በየትኛው ጊዜ እንደተፈጸመ የምናውቀው ነገር የለም። አንዳንድ ምሁራን ዮፍታሔ በነበረበት ዘመን አካባቢ የተፈጸመ ነው ብለው ይገምታሉ። 

የመጽሐፈ ሩት አስተዋጽኦ

  1. በአቤሜሌክ ቤተሰብ ላይ የደረሰው መከራና ኃዘን (1፡1-5) 
  2. ኑኃሚንና ሩት ወደ ቤተልሔም ተመለሱ (1፡6-22) 
  3. ሩት ቦዔዝን በመከር መሰብሰቢያ ስፍራ አገኘችው (2) 
  4. ሩት ወደ ቦዔዝ የአውድማ ስፍራ በመሄድ እንዲያገባት ጠየቀችው (3) 
  5. ቦዔዝ ሩትን አገባ፤ ወንድ ልጅም ወለዱ (4፡1-17) 
  6. የዳዊት የዘር ሐረግ (4፡18-22)።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version