መጽሐፈ ሩት (1-4)

  1. የሩት ታሪክ የተፈጸመበት ጊዜና ቦታ (ሩት 1)

መጽሐፈ ሩት የሚጀምረው ታሪኩ በዘመነ መሳፍንት ወቅት የተፈጸመ መሆኑን በመናገር ነው። በይሁዳ ግዛት ራብ እንደተነሣ ይናገራል። የዚህ መጽሐፍ ጸሐፊ ራብን የተጠቀመበት በአቤሜሌክ ቤተሰብ ላይ ስለመጣው ችግር ለመናገር ብቻ ሳይሆን፥ ሕዝቡ ከእግዚአብሔር ፍርድ በታች ስለመሆናቸውም ለማጋለጥ ነበር። ሕዝቡ ለእግዚአብሔር ባለመታዘዛቸው የራብን መርገም ጭምር እንደሚያመጣባቸው እግዚአብሔር አስቀድሞ ተናግሮአል (ዘዳ. 28፡23-24)።

የአቤሜሌክ ቤተሰብ ራቡን በመሸሽ ወደ ሞዓብ ሄደ። በዚያም ለብዙ ዓመታት ስለኖሩ፥ ሁለቱ ወንዶች ልጆቻቸው ሞዓባውያን የሆኑ ሴቶችን አገቡ፤ ነገር ግን ብዙም ሳይቆይ አቤሜሌክና ሁለቱ ልጆቹ ሞቱ።

የታሪኩ ዋና ትኩረት ኑኃሚን እንዴት ባዶና ድሀ እንደሆነች ለማሳየት ነው። ባልዋን እና ልጆችዋን አጣች። በእርጅናዋ ወራት እንክብካቤ የሚያደርግላት አንዳችም ወራሽ፥ ወይም ራሷን የምትደግፍበት መሬት አልነበራትም፤ ስለሆነም እጅግ ተማርራ ወደ ይሁዳ ለመመለስ ወሰነች። አንደኛዋ ምራቷ በሞዓብ ስትቀር፥ ሌላኛዋ ግን ማለትም ሩት አማትዋን ለመከተል አማልክትዋን፥ ቤተሰብዋንና አገሯን ሁሉ ተወች። ሩት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚገለጥ የታማኝ ፍቅር ምሳሌ ናት። ወደ እስራኤል ምድር እንደ እንግዳ ከመሄድ ይልቅ በአገሯ መቅረት፥ ከገዛ ሕዝቧ ጋር መኖር በቀለላትም ነበር።

  1. ለኑኃሚንና ለሩት እንክብካቤ ለማድረግ እግዚአብሔር የሠራው ሥራ (ሩት 2-3)

በዚህ ታሪክ ውስጥ እግዚአብሔር የተጠቀሰበት ቦታ ብዙ ባይሆንም፥ በታሪኩ ሁሉ የእግዚአብሔርን እጅ እንድናይ ለማድረግ ጽሐፊው እንደሞከረ ግልጥ ነው። ሩት እንዴት ወደ አማቷ ዘመድ የእርሻ ቦታ እንደሄደች ተመልከት። የኑኃሚን ዘመድ የሆነው ቦዔዝ ለሩት ልዩ የሆነ ትኩረትና ጥንቃቄ እንዴት እንዳደረገ እንመለከታለን። እግዚአብሔር ቦዔዝ የቤተሰብ ግዴታውን ለመፈጸም ብሎ አሕዛብ የሆነች ሴት እንዲያገባ እንዴት እንደገፋፋው ተመልከት።

ታሪኩ የሚያተኩረው በሁለት ዋና ዋና ገጸ-ባሕርያት ታማኝነት በተሞላ ፍቅር ላይ ነው። በመጀመሪያ፥ ሩት ለኑኃሚን የነበራት በታማኝት የተሞላ ፍቅር ነው። በሁለተኛው ደግሞ፥ ቦዔዝ ለሩትና ለኑኃሚን ያሳየው በታማኝነት የተሞላ ፍቅር ነው።

ነገር ግን ከሰው የታማኝነት ፍቅር ምሳሌነት ሁሉ በላይ እግዚአብሔር ለሁለት ድሀና ምስኪን ሴቶች የነበረውን ፍቅርና እንክብካቤ እናያለን።

  1. እግዚአብሔር የሩትንና የቦዔዝን ታማኝነት በማክበርና ለእርሱ ዋጋ በመስጠት ለኑኃሚን በረከቱን መለሰላት (ሩት 4)

ከሩት ታሪክ በስተጀርባ የአይሁድ ባሕል የሆነ «የመዋጀት» ተግባር እናያለን። መመሪያው በዘዳግ. 25፡5-10 ይገኛል። በዚህ ስፍራ የእግዚአብሔር ሕግ የሚለው አንድ ሰው ልጅ ሳይኖረው ቢሞት፥ ወንድሙ የሞተውን ሰው ሚስት በመውሰድ ከሴቲቱ ልጅ መውለድ እንደነበረበት ነው። በዚህ መንገድ የሚገኘው ልጅ የሟች ወንድሙ ወራሽ ይሆን ነበር፤ ደግሞም በዘሌ. 25፡25-31፥ 41-55 ሕጉ በተጨማሪ ድሀ የሆነ ሰው በድህነት ምክንያት መሬቱን ቢሸጠው፥ የዚህ ድሀ ሰው ዘመድ ገንዘቡን በመክፈል መሬቱን ሊያስመልስና በባዕድ እጅ እንዳይገባ ሊከላከል ይገባ ነበር። የእነዚህ ሁለት ሕግጋት ዓላማ የአንድን ሰው የቤተሰብና የመሬት ወራሽነት ለመጠበቅ ነበር። 

በመጽሐፈ ሩት፥ ይህ ሕግ በቅርብ ዘመድ ብቻ ሳይወሰን፥ በሩቅ ዘመድም ላይ የሚሠራ ሆነ። የመዋጀት ግዴታ የወደቀው በቅርብ ዘመድ ላይ ነበር። ይህ የቅርብ ዘመድ ግዴታውን ለመወጣት ፈቃደኛ ያልሆነ ወይም የማይችል ከሆነ ብቻ ኃላፊነቱ ወደ ሌላ ዘመድ ይተላለፍ ነበር። በዚሁ መሠረት ቦዔዝ ሩትን አገባና የአቤሜሌክና የልጆቹ ወራሽ የሚሆን ልጅ አስገኘ። ልጁ የአቤሜሌክ ምድር ወራሽ ሆነ፥ ቦዔዝ ደግሞ የአቤሜሌክ ምድር የተያዘበትን ዕዳ ሁሉ የመክፈል ግዴታ ነበረበት። 

ይህ ከሩት ምዕራፍ 4 ታሪክ በስተኋላ የሚገኝ ባሕላዊ ልማድ ክፍል ነው። ቦዔዝ የኑኃሚን የቅርብ ዘመድ የሆነውን ሰው ይፋ ፍርድ ወደሚሰጥበት ስፍራ አመጣው። በጥንት ዘመን የጎሣ ሽማግሌዎች በከተማይቱ በር ላይ ይገናኙና በጉዳዮች ላይ ውሳኔ በመስጠት ይፈርዱ ነበር። ወደዚህ የፍርድ ስፍራ የመጣው የቅርብ ዘመድ ለሩት ያለበትን ግዴታ ለመወጣት ፈቃደኛ አለመሆኑን ገለጠ። ይህንን ለማድረግ ያልፈለገው፥ የራሱ ልጆች ቢሞቱ ቀሪው ወራሽ ከሩት የሚወለደው ልጁ ስለሚሆን፥ የራሱንም ንብረት ለመቆጠብ ሳይሆን አይቀርም። ይህ ዘመድ ከቦዔዝ የሚለይበት ነገር ቢኖር ስለራሱ ብቻ የሚያስብ ስስታም ስለ ነበር ነው።

ቦዔዝ ሩትን የማግባት ግዴታውን ተወጣ። በዚህም ኢዮቤድ የተባለ ልጅ አገኙ። በኃዘኗ ምክንያት በብቸኝነት ተቆራምዳ የነበረችው ኑኃሚን፥ የተባረከች ኑኃሚን ሆነች። የልጅ ልጅ ማግኘቷ ብቻ ሳይሆን ምድሪቱ ለእርሷ ተመለሰችላት፤ በእርጅናዋ ወራት የሚጦራትንም አገኘች። 

በእግዚአብሔር ሉዓላዊ ጥበብ፥ የሩትና የቦዔዝ ልጅ የእስራኤል ታላቅ ንጉሥ የሆነው የዳዊት አያት ሆነ። 

የውይይት ጥያቄ፥ ስለ እግዚአብሔርና ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ስላለው ግንኙነት ከዚህ ታሪክ የተማርካቸው ዋና ዋና ነገሮች የትኞቹ ናቸው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: