የ1ኛ ነገሥት አስተዋጽኦ እና ዓላማዎች

  1. የ1ኛ ነገሥት አስተዋጽኦ
  2. ሰሎሞን (1-11) 
  3. ሮብዓም (12) 
  4. የተከፋፈለው የእስራኤልና የይሁዳ መንግሥት [13-22] (931-853 ዓ.ዓ.) 

ሀ. ቀዳማዊ ኢዮርብዓም (12፡22-14፡20) 

ለ. ሮብዓም (14፡21-33) 

ሐ. አብያ (15፡1-8) 

መ. አሳ (15፡9-24) 

ሠ. ናዳብ (15፡25-32) 

ረ. በአሳ (15፡33-16፡7) 

ሰ. ኤላ (16፡8-14) 

ሸ. ዘምሪ (16፡15-20)

ቀ. ዘንበሪ (16፡21-28) 

በ. አክዓብ (16፡29-34) 

  1. ኤልያስና ነገሥታት

ሀ. ኤልያስና አክዓብ (17፡1-22፡40) 

ለ. ኢዮሣፍጥ (22፡41-50)

ሐ. አካዝያስ (22፡51-53) 

  1. የ1ኛ ነገሥት ዓላማዎች 
  2. በሰሎሞን ጊዜና ከተከፋፈለ በኋላ ማለት ከ931-853 ዓ.ዓ. የነበረውን የእስራኤልን መንግሥት ታሪክ ባጭሩ ለመናገር ጸሐፊው በነገሥታት ጊዜ የነበረውን አጠቃላይና የተሟላ ታሪክ ለመናገር አይፈልግም። በእያንዳንዱ ንጉሥ ዘመን የተፈጸመውን ነገር የሚናገሩ ዝርዝር መዛግብት በቤተ መንግሥቱ ጽሑፎች ውስጥ ይገኙ ነበር፤ ስለዚህ የዚህ መጽሐፍ ጸሐፊ፥ እያንዳንዱ ንጉሥ በነገሠበት ዘመን ስለተፈጸመው ነገር እጅግ አጠር ያለ ማጠቃለያ በመስጠት፥ በተለይም ንጉሡ እንደ ዳዊት እንደነበረ ወይም እንዳልነበረ በሚያሳይ መልኩ ብቻ ባሕርዩን ለመዳሰስ ሞክሯል።

የነገሥታቱን ታሪክ በሚናገርበት ጊዜ፥ ጸሐፊው የሚከተለውን መሠረታዊ አወቃቀር ተከትሏል፡-

ሀ. የንጉሡ ማንነት ይነገርና የአባቱ ስም ይጠቀስ ነበር። 

ለ. ንጉሡ ወደዚህ ሥልጣን የመጣበት ዕድሜ ተጠቅሷል። ከይሁዳ ክፍለ መንግሥት ከሆነ ብዙ ጊዜ የንጉሡ እናት ስም ተጠቅሷል። 

ሐ. በንጉሡ ዘመን የተፈጸሙ ዐበይት ክስተቶች ተጠቅሰዋል።

መ. ጸሐፊው የንጉሡን የሥነ-ምግባር ባሕርይና በሕዝቡ ላይ የነበረውን መንፈሳዊ አመራርም ባጭሩ ይገመግማል። ንጉሡ ከይሁዳ ከሆነ ሕይወቱን ከዳዊት ጋር ማወዳደር፥ ከእስራኤል ከሆነ ደግሞ ከቀዳማዊ ኢዮርብዓም ጋር ማወዳደር የተለመደ

ነው።

  1. እግዚአብሔር በእስራኤል ላይ ለምን እንደፈረደ ለማሳየት። ጸሐፊው የ1ኛ ነገሥትን መጽሐፍ በሚጽፍበት ጊዜ፥ ሙሴ በዘዳ. 27-28 የሰጣቸው ተስፋዎች በአእምሮው ነበሩ። ጸሐፊው እስራኤል ለእግዚአብሔር በመታዘዝ በኖረችበት ጊዜ፥ እርሱ የሰጠውን የተስፋ ቃል በሙሉ እንዴት እንደፈጸመ ይናገራል፤ ነገር ግን እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ላይ በሚያምፁበት ጊዜና ግዴታቸውን ሳይወጡ ሲቀሩ፥ በተስፋ ቃሉ የሰጠውን ፍርድ ያመጣባቸው ነበር። 

የውይይት ጥያቄ፥ ዘዳ. 27-28 አንብብ። ሀ) ለቃል ኪዳኑ ባለመታዘዝ ስለሚመጡ ፍርዶች (መርገሞች) የተነገረውን ነገር ዘርዝር። ለ) ለቃል ኪዳኑ በመታዘዝ ስለሚገኙ በረከቶች የተሰጠውንም ነገር ዘርዝር።

  1. እግዚአብሔር ነቢያትን የእርሱ አፈቀላጤ አድርጎ ወደ ነገሥታቱ እንዴት ይልካቸው እንደ ነበር ለማሳየት። እግዚአብሔር ሕዝቡን ተግባራቸው ምን ውጤት እንዳለው ሳይገነዘቡ፣ ኮብልለው እንዲሄዱ አይፈልግም ነበር። በመሆኑም እግዚአብሔር ነቢያትን እያስነሣ ድርጊታቸውን እንዴት እንደሚመለከትና እንደሚፈርድባቸው ሕዝቡን ሁሉ በተለይም ነገሥታትን እንዲያስጠነቅቁአቸው ያደርግ ነበር። እነዚህ ነቢያት እግዚአብሔር በመለኮታዊ መንገዱ የመረጣቸውና ሕዝቡን የሥነ-ምግባር እውቀት እንዲኖራቸው የሚያደርጉ ነበሩ። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዛሬም ክርስቲያኖች ለኅብረተሰባቸው የሥነ-ምግባር እውቀት (ብርሃን) መሆን የሚችሉት እንዴት ነው? ለ) ለኅብረተሰባቸው የእግዚአብሔር አፈቀላጤ የሚሆኑትስ እንዴት ነው? ሐ) ቤተ ክርስቲያንህ ይህንን ሚና እየተጫወተች ያለችው እንዴት ነው? ግልጥ የሆኑ መግለጫዎችን ስጥ።

  1. ዓመፀኞች፥ የማይታዘዙና ጣዖት አምላኪዎች የሆኑ የእግዚአብሔር ሕዝብ መሪዎችና ነገሥታት እንዴት በሕዝቡ ሁሉ ላይ የእግዚአብሔርን ፍርድ እንዳመጡ ለማሳየት ነው። ብዙ ጊዜ በኃጢአት የሚወድቁት ሕዝቡ አይደሉም። የአንድ ሕዝብ መሪ የሆነው ንጉሡ በኃጢአት በሚወድቅበት ጊዜ፥ በራሱ ተጽዕኖ ሕዝቡንም ወደ ኃጢአት ይመራቸዋል። በሌላ በኩል ደግሞ ንጉሡ ጻድቅ ከሆነና ለእግዚአብሔር በመታዘዝ ከኖረ፥ ሕዝቡ እግዚአብሔርን በሚገባ እንዲያመልኩና ለእግዚአብሔር በመታዘዝ እንዲኖሩ ሊያደርግ ይችላል። 

የውይይት ጥያቄ፥ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች በቤተ ክርስቲያናቸው አባላት መንፈሳዊና ሥነ-ምግባራዊ ሕይወት ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድሩ ስለመቻላቸው ከዚህ ምን ለመማር እንችላለን? 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: