የ2ኛ ነገሥት መግቢያ

በመጀመሪያ 1ኛና 2ኛ ነገሥት አንድ መጽሐፍ እንደነበሩ ታስታውሳለህ። በኋላ ወደ ሁለት መጻሕፍት የተከፈሉት መጽሐፉ እጅግ በመርዘሙ ምክንያት ነበር። የነገሥት መጽሐፍ ርዕስ የተገኘው በ1ኛና 2ኛ ነገሥት ከሰሎሞን ጀምሮ እስከ ሴዴቅያስ ድረስ በእስራኤልና በይሁዳ የነገሡ ነገሥታት አጫጭር ታሪኮች የሚገኝበት መጽሐፍ ከመሆኑ አንፃር ነው። 

የውይይት ጥያቄ፥ 2ኛ ነገሥት 17፡7-23 አንብብ። ሀ) እግዚአብሔር እስራኤልንና ይሁዳን ያጠፋው ለምንድን ነው? ለ) በዚህ ክፍል የተሰጡትን የተለያዩ ምክንያቶችን ዘርዝር።

እስራኤላውያን በእግዚአብሔር የተመረጡት ለእርሱ የተለዩ ሕዝብ እንዲሆኑ ነበር። በአብርሃም በኩል ከእግዚአብሔር ጋር የዘላለም ቃል ኪዳን ነበራቸው። በሲና ተራራ እግዚአብሔር በታላቅ መንገድ ተገናኛቸውና ትእዛዛቱን ሰጣቸው። እስራኤላውያን ለምን ጠፉ? ወደ ምርኮ የሄዱት ለምንድን ነው? ራብ፥ በሽታ፥ ሞት፣ ጦርነትና ምርኮ በእነርሱ ላይ የመጣው ለምንድን ነው?

የ1ኛና 2ኛ ነገሥት መጻሕፍት ሊመልሱት የሚሞክሩት ጥያቄ ይህ ነው። አዎን፥ የእስራኤል ሕዝብ የተለዩ ነበሩ። አዎን፥ እግዚአብሔር ቃል ኪዳኑን ከአብርሃም፥ ከእስራኤላውያንና ከዳዊት ጋር አድርጎ ነበር። የእግዚአብሔር ሕዝብ የጠፉበት ምክንያት ግን በእግዚአብሔር ሳይሆን በራሳቸው ጥፋትና ስሕተት ነበር። የእግዚአብሔር ቃል ነበራቸው፤ ስለዚህ ቃሉን ማወቅ ይጠበቅባቸው ነበር። ነገር ግን እያወቁ በግትርነት በእግዚአብሔር ላይ ዓመፁ። ቅዱሱ እግዚአብሔር ኃጢአታቸውን ሳይቆጣ ሊያልፋቸው ስላልቻለ አስቀድሞ በተደጋጋሚ ባስጠነቀቃቸው መሠረት አስማረካቸው።

ዛሬም እግዚአብሔር ተመሳሳይ ነገር በቤተ ክርስቲያኑ ሊያደርግ ይችላልን? በቤተ ክርስቲያኑ ላይ ራብ፥ በሽታና ጥፋት እንዲመጣ መፍቀድ ይችላልን? እግዚአብሔር እኛን ለምርኮ ማለትም ለሌላው ሃይማኖት ቁጥጥር አልፈን እንድንሰጥ ሊያደርግ ይችላልን? ለእነዚህ ሁሉ ጥያቄዎች መልሱ አዎን የሚል ነው። እኛም ልክ እንደ እስራኤላውያን ከሆንን፥ የእግዚአብሔርን ቃል ካላወቅንና ካልታዘዝን እንጠፋለን። የ2ኛ ነገሥት መልእክት ለእግዚአብሔር ካልታዘዝን፥ እግዚአብሔር በእስራኤላውያን ላይ እንደፈረደ፥ በእኛም ላይ እንደሚፈርድ የሚያመለክት ማስጠንቀቂያ ነው። ጉዳዩ እግዚአብሔር ባለፈው ዘመን እንዴት ተጠቀመብን የሚለው አይደለም። ቁም ነገሩ እግዚአብሔርን አሁንና ወደፊት እንዴት እንደምናገለግለውና ከእርሱም ጋር እንዴት እንደምንራመድ ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ 2ኛ ዜና 7፡14 አንብብ። ሀ) በዚህ ቁጥር እግዚአብሔር የገባቸው የተስፋ ቃሎች ምንድን ናቸው? ለ) ለዚህ የተስፋ ቃል የተሰጠው ቅድመ ሁኔታ ምንድን ነው? ሐ) አንተና ቤተ ክርስቲያንህ እነዚህን ቅድመ ሁኔታዎች እያሟላችሁ ያላችሁት እንዴት ነው? ይህንን ጥቅስ በቃልህ አጥና፡፡ 

የ2ኛ ነገሥት ታሪክ የተፈጸመበት የዘመን ርዝመት 

በ1ኛ ነገሥት የተጻፈው ታሪክ ከዳዊት ሞት ከ971 ዓ.ዓ. ጀምሮ እስከ 853 ዓ.ዓ. ድረስ በነበረው ጊዜ መፈጸሙን ተመልክተናል። በ1ኛ ነገሥት ታሪክ ጊዜ የሰሎሞንን መንግሥትና ቀጥሉም እስራኤል በሰሜን፥ ይሁዳ ደግሞ በደቡብ ሆኖ ለሁለት የተከፈለውን መንግሥት ተመልክተናል።

2ኛ ነገሥት የተከፈለውን የእስራኤል መንግሥት ታሪክ ይቀጥላል። የሚናገረውም ከ853-586 ዓ.ዓ. ስላለው ጊዜ ነው። በዚህ ጊዜ ውስጥ ከተፈጸሙ ድርጊቶች በጣም አስፈላጊዎቹ በ722ዓ.ዓ. የተፈጸመው የሰሜኑ መንግሥት ጥፋትና ከብዙ ዓመታት በኋላ በ586ዓ.ዓ የተከናወነው የደቡብ መንግሥት ጥፋት ነው። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “የ2ኛ ነገሥት መግቢያ”

Leave a Reply

%d bloggers like this: