የሰሎሞን ውድቀት (1ኛ ነገሥት 11)

ሰሎሞን በዓለም ዘንድ ምንም ያህል ጥበበኛ ይሁን፥ በእግዚአብሔር ዓይን ጥበበኛ አልነበረም። ሰሎሞን በወጣትነቱ ዘመን «የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው» (ምሳ. 1፡7) ሲል ጽፎ ነበር። ይህንን ሲል እውነተኛ ጥበብ የሚመጣው ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደሆነና የሚገለጠውም ለእግዚአብሔር ወደመታዘዝ በሚያመራው በፈሪሃ እግዚአብሐርነት ነው ማለት ነበር። የሚያሳዝነው ግን ሰሎሞን በሸመገለ ጊዜ ይህንን አልተከተለም። ይልቁንም እግዚአብሔርን ረሳ፤ የእስራኤልን አምልኮ አበላሸ፤ ለእስራኤል መንግሥት መከፈል ዋና ምክንያት ሆነ። 1ኛ ነገሥት 11 የሚያተኩረው በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ስለነበረው፥ ሰሎሞን ስላደረገውና በኋላም ዘሩ አድጎ የእስራኤልን ሕዝብ ስላጠፋው ኃጢአት ነው። የእስራኤል ሕዝብ ከሕደት እስኪጠፋና ወደ ምርኮ እስኪሄዱ ድረስ የቀጠለው ሥሩን ከሰሎሞን በማቆጥቆጥ ነው።

ሰሎሞንን ወደ ጥፋት የመሩትን የሚከተሉትን ነገሮች ተመልከት፡-

ሀ. ሰሎሞን ብዙ ሴቶችን አገባ። የአብዛኛው ጋብቻ ዓላማ ከሌሎች ሕዝቦች ጋር የፖለቲካ ስምምነት ለማድረግ ነበር። መጽሐፍ ቅዱስ ለሰሎሞን 700 ሚስቶችና 300 ቁባቶች እንደነበሩት ይናገራል። ሰሎሞን ይህንን ያደረገው ምናልባት ታላቅነቱን ለዓለም ለማሳየት ሊሆን ይችላል፤ ዳሩ ግን በምንም መንገድ ቢሆን የእግዚአብሔርን ሕግ በቀጥታ የጣሰ ነበር። (ዘዳ. 17፡17 ተመልከት)። በጥንት ዘመን ነገሥታት በመካከላቸው የሚያደርጉትን ስምምነት ወንዶችና ሴቶች ልጆቻቸውን ለጋብቻ በመለዋወጥ ያጸኑ ነበር። ሰሎሞን በርካታ ሚስቶች ያገባበት ምክንያት ይህ ለመሆኑ አንዳችም ጥርጥር የለም። 

ለ. አብዛኛዎቹ ሚስቶቹ የተሳሰተ አማልክትንና ጣዖቶችን የሚያመልኩ አሕዛብ ስለነበሩ፥ ሰሎሞን ለሚስቶቹ በኢየሩሳሌም ውስጥ የሐሰት አምልኮ የሚያካሄዱበትን ስፍራ እንዲኖራቸው ፈቀደላቸው (1ኛ ነገ. 11፡7-8)። ቀጥሎም ከእነርሱ ጋር እነዚህን የሐሰት አማልክት ማምለክ ጀመረ። ሰሎሞን ዛሬም ብዙ ክርስቲያኖች በሚጠመዱበት ወጥመድ ተያዘ። ሚስቶቻቸውን ወይም ቤተሰቦቻቸውን ለማስደሰት፥ ሰዎች እውነተኛውን አምላክና ሐሰተኛ አማልክትን ወይም የቀድሞ ሃይማኖታቸውን በአንድነት ያመልካሉ። ሰሎሞን ከኢየሩሳሌም ውጭ የገነባቸው የሐሰተኛ አማልክት ማምለኪያ ስፍራዎችን ኢዮስያስ እስኪያስወግዳቸው ድረስ ለ350 ዓመታት ቆዩ (2ኛ ነገ. 23፡13 ተመልከት)።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ይህ ነገር በአንዳንድ ክርስቲያኖች ሲፈጸም ያየኸው ነው? ለ) ስሕተት የሆነውስ ለምንድን ነው? ሐ) ሰሎሞን ሚስቶቹን ለማስደሰት ብሉ ጣዖትን ከማምለኩ ምን ልንማር እንችላለን?

ሐ. ሰሎሞን የአስተዳደር አሠራሩን በከፍተኛ ደረጃ ወደ ውስብስብ ሁኔታ አደረሰው። የመንግሥት ሠራተኞች እጅግ ብዙ ከመሆናቸው የተነሣ፥ በሰሎሞን መንግሥት ውስጥ ያሉ የአስተዳደር ሰዎችንና የተለያዩ ሥራዎችን ሕዝቡ ሊደግፍ ከማይችልበት ደረጃ ደረሰ።

መ. ሰሎሞን በአንድ ጊዜ ከመጠን በላይ የሆነ ነገሮችን ለመሥራት ሞከረ። አገሪቱ ቀስ በቀስ እንድታድግ ከማድረግ ይልቅ በርካታ ትላልቅ ከተሞችን በአንድ ጊዜ ሠራ። ይህም ነገር ሕዝቡ የመንግሥት ባሪያ እንዲሆን አደረገው። በምድሪቱ በሚኖሩ ሰዎች ሁሉ ላይ የኑሮ ጫና ፈጠረባቸው። ሕዝቡ እጅግ የጠሉት ነገር ይህ ነበር። ለዚህ ነው ከሰሎሞን ሞት በኋላ ስለ ግብርና ለመንግሥት በመሥራት ረጅም ጊዜ ስለማጥፋት ያጉረመረሙት።

ሠ. ሰሎሞን ዓለም አቀፍ ንግድንና ግንኙነትን ከፍ ለማድረግ ስለሞከረ፥ ከእርሱ ጋር ግንኙነት ያደርጉ በነበሩ አሕዛብ መንግሥታት ፍልስፍናና የሃይማኖት ተጽዕኖ ሥር ወደቀ። ይህም እስራኤል ዓለም አቀፍ ስምምንት እንዳያደርጉ እግዚአብሔር ከሰጣቸው ማስጠንቀቂያ ጋር በቀጥታ የሚፃረር ነበር (ዘጸ. 34፡ 12-15፤ ዘዳ. 7፡2)። በሰሎሞን ዘመነ መንግሥት መጨረሻ አካባቢ መንግሥቱ መውደቅ ጀመረ። እግዚአብሔር ግን ለአባቱ ለዳዊት በነበረው ፍቅር ምከንያት፥ በእርሱ የሕይወት ዘመን መንግሥቱ እንደማትከፈል ቃል ገብቶለት ነበር። እግዚአብሔር ግን በሰሎሞን ላይ ፍርድን አመጣ።

  1. እግዚአብሔር መንግሥቱ ለሁለት እንደምትከፈል ተናገረ። ነቢዩ አኪያ የመንግሥቱን መከፈል የሚመለከት መልእክት ተናገረ። አሥሩ ነገዶች እስራኤል ሲባሉ፥ ሁለቱ የደቡብ ነገዶች የይሁዳ መንግሥት እየተባሉ ይጠራሉ። እግዚአብሔር አሥሩን የእስራኤል ነገዶች ከዳዊት ዘር ላልሆነው ለኢዮርብዓም ሰጣቸው፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ለዳዊት ከነበረው ፍቅር የተነሣ የይሁዳን ሁለት ነገዶች (ይሁዳና ብንያምን) በዳዊት ልጆች አመራር ሥር እንዲቆዩ አደረገ። 
  2. የሰሎሞን መንግሥት በተለያዩ ዓመፆች መፈረካከስ ጀመረ።

ሀ. ከሰሎሞን አስተዳዳሪዎች አንዱ የነበረው ኢዮርብዓም በሰሎሞን ላይ ዓምዖ ወደ ግብፅ ኮበለለ። 

ለ. የኤዶም መንግሥት በሰሎሞን ላይ ዓመፀ። ግብፅ ለኢዮርብዓምና በሃዳድ መጠለያ በመስጠት ይህንን ዓመፅ እንዴት እንዳበረታታችና እንደደገፈች መመልከት የሚገርም ነው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እንደመሆናችን መጠን እንዴት መምራት እንዳለብን፥ ከሰሎሞን ሕይወት የምንማራቸውን ትምህርቶች ዘርዝር። ለ) ልንከተላቸው የሚገቡን መልካም ነገሮች የትኞቹ ናቸው? ሐ) ወደ ሕይወታችን እንዳይገቡ ልንከላከላቸው የሚገባን ነገሮች የትኞቹ ናቸው? 

አብዛኛዎቹን የብሉይ ኪዳን የጥበብ መጻሕፍት እንዲጽፍ እግዚአብሔር ሰሎሞንን ተጠቅሞበታል። እነዚህን በሚቀጥለው የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጥናት እንመለከታቸዋለን። ብዙ ምሁራን ሰሎሞን መጽሐፈ ምሳሌን የጻፈው ወጣት በነበረና ከጌታ ጋር በመልካም አካሄድ በነበረው ጊዜ ነው ይላሉ። መጽሐፈ መክብብን ደግሞ የጻፈው በሕይወቱ መጨረሻ አካባቢ ከእግዚአብሔር ርቆ የመኖርን መራራነት ከተለማመደ በኋላ ነው። መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ደግሞ ምናልባት ሰሎሞን ከሚስቶቹ መካከል አንዷን እንዴት እንዳገባ የሚገልጥ የግጥምና የፍቅር መጽሐፍ ይሆናል ብለው ያስባሉ። 

የውይይት ጥያቄ፥ 1ኛ ቆሮ. 9፡24-27 አንብብ። ጳውሎስ በሕይወቱ ለራሱ ይፈራው የነበረው ነገር በሰሎሞን ሕይወት ውስጥ የተፈጸመው እንዴት ነው? (ቁ. 27)። ጳውሎስ ከነበረው ታላላቅ ፍርሃቶች አንዱ፥ በዕድሜ በገፉ ጊዜ ለብዙዎች ከሰበከና ብዙዎችን ለክርስቶስ ከማረከ በኋላ እርሱ እንዳይወድቅና ለክርስቶስ የማይጠቅም የተጣለ እንዳይሆን ነበር፤ ስለዚህ ሕይወቱን አጥብቆ ሊቆጣጠር ወሰነ። በክርስትና ሕይወትም ሆነ በቤተ ክርስቲያን አመራር ዋናው ነገር መልካም ጅማሬ ሳይሆን ያማረ ፍጻሜ ነው። ሰሎሞን በመልካም ጀመረ፤ ነገር ግን በከፋ ሁኔታ ጨረሰ። ብዙ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እንደ ሰሎሞን ናቸው። አጀማመራቸው መልካም ነው። ዕድሜያቸው በገፋ ጊዜ ግን ከመንገዳቸው ፈቀቅ ይሉና ለቤተ ክርስቲያን የማይጠቅሙ ብቻ ሳይሆን የሚጎዱዋትም ይሆናሉ። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “የሰሎሞን ውድቀት (1ኛ ነገሥት 11)”

  1. እግዚአብሔር አምላክ ፀጋውን ያብዛላችሁ በጣም ሲበዛ ብዙ ነገር ቀረልኝ ።
    እራሴን እንዳይ አደረገኝ ጌታ ኢየሱስ ይባረክ ።

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading