ከመጸሐፍ ነገሥት የተጠቀሱ በርካታ ጥቅሶች በአዲስ ኪዳን ውስጥ ባይኖሩም በ1ኛና በ2ኛ ነገሥት የተፈጸሙ ድርጊቶችን የመረዳት ጉዳይ ግን በአዲስ ኪዳን በአጠቃላይ እናገኛለን። በአዲስ ኪዳን ሰሎሞን በተደጋጋሚ ተጠቅሷል። ማቴ. 1፡1-17 ከአብርሃም ጀምሮ እስከ ኢየሱስ ያለውን የጌታን የዘር ግንድ ያሳየናል። በእነዚህ ጥቅሶች በመጽሐፈ ነገሥት የተጠቀሱት አብዛኞቹ ነገሥታት ተዘርዝረዋል። የሰሎሞን ጥበብና ሀብት አንዳንድ ጊዜ ተጠቅሷል (ለምሳሌ፡- ማቴ. 12፡42፤ ሉቃስ 12፡27)።
የ1ኛና የ2ኛ ነገሥት ታሪኮች በቀጥታ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ባያመላክቱም፥ ከቀረው የመጽሐፍ ቅዱስ አመለካከት ጠቃሚ እውነቶችን ማየት እንችላለን። በብሉይ ኪዳን የድነት (የደኅንነት) ግንድ የሆነውን የኢየሱስ ክርስቶስን የትንቢት መስመር እናገኛለን። ይህ ትንቢት የጀመረው የሰይጣንን ራስ እንደሚቀጠቅጥ የተነገረለት የሴቲቱ ዘር ጉዳይ ከተጠቀሰበት ከኦሪት ዘፍጥረት ነው (ዘፍ. 3፡15)። ይህ መስመር ከዚያ እስከ አብርሃም፥ ቀጥሎም እስከ ዳዊት፥ ከዚያም በይሁዳ ነገሥታት በኩል ያለፈ ነው።
ሰይጣን የአብርሃምና የይሁዳ የዘር ግንድ ልዩ እንደ ነበረና መሢሑ ከዚያ እንደሚመጣ ያውቅ ነበር። ስለዚህ በታሪክ መጻሕፍት በተደጋጋሚ ሰይጣን ይህንን የዘር ግንድ እንዴት ሊያጠፋ እንደሞከረ የሚያሳየውን የተደበቀ እውነት እናያለን። በዘፍጥረት ሰይጣን የግብፅን ንጉሥ በመጠቀም ሣራን እንደ ሚስቱ እንዲወስድና የአብርሃም የዘር ግንድ እንዲቋረጥ ለማድረግ ሞክሮ ነበር። ሰይጣን ድርቅና ራብን በመጠቀም የእስራኤልን ቤተሰብ ለማጥፋት ቢሞክርም፥ እግዚአብሔር በዮሴፍ ተጠቅሞ እንዴት ከራብ እንዳዳናቸው እይተናል።
በ2ኛ ሳሙኤል ለዳዊት ዘር የተሰጠውን የዘላለም ዙፋን ተስፋ ተመልክተናል። በመጽሐፈ ነገሥት በአጠቃላይ የምናየው፥ ለዘላለም ዙፋን የተሰጠው ቃል ኪዳን ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተላለፈ እንዴት እስከ ምርኮ ታሪክ ድረስ እንደመጣ ነው። ጎተልያ የተባለችው ክፉ ንግሥት ታሪክ የሚያሳየው፥ የዳዊትን ዝርያ እንዳለ በማጥፋት ሰይጣን የእግዚአብሔርን ዕቅድ ለማበላሸት እንዴት እንደሞከረ ነው። የዳዊት ንጉሣዊ ቤተሰብ በሙሉ የጠፋና ከእርሱ የዘር ግንድ አንድ ሰው ብቻ የቀረ ይመስላል። ሰይጣን ያንን የቀረውን ሰው ማስገደልና መስመሩ እንዲቋረጥ ማድረግ ቢችል ኖሮ መሢሑ በዳዊት ዘር በኩል መምጣቱን ሊያስቀር ይችል ነበር። እግዚአብሔር ግን አንድ ሰው እንዲቀርና የዳዊት የዘር ግንድም እንዲጠበቅ አደረገ። ኢየሱስ በቤተልሔም ትንሽ ሕፃን በነበረ ጊዜ ሄሮድስ ሊያስገድለው መሞከሩ በሰይጣንና በእግዚአብሔር መካከል የነበረው የዚያው ጦርነት ክፍል ነበር።
ሰይጣን እግዚአብሔርን ለማሸነፍ የቱንም ያህል ቢጥርም ሁልጊዜ በእግዚአብሔር ይሸነፋል። ሰይጣን ምንም ያህል ተግቶ ቢሠራም፥ እግዚአብሔር ለእኛና ለቤተ ክርስቲያን ያለውን ዕቅድ ሊደመሰስ አይችልም።
የውውይት ጥያቄ፥ በስደት፥ በሐሰት ትምህርት፥ ወዘተ በምንጠቃበትና የተሸነፍን በሚመስለን ሰዓት ይህ እውነት እንዴት ያበረታታናል?
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
geta tsegahun yabezale