የ1ኛና 2ኛ ዜና መዋዕል መግቢያ

1ኛና 2ኛ ዜና፥ ከዳዊት ጊዜ ጀምሮ የይሁዳ መንግሥት በባቢሎን እጅ እስከ ወደቀበት ድረስ ያለውን የነገሥታትን ዘመን ታሪክ እንደገና ይናገራሉ። ብዙ ሰዎች እነዚህ ታሪኮች ለሁለተኛ ጊዜ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ለምን እንደገቡ በማሰብ ይገረማሉ። ሁለት ሰዎች የመኪና አደጋን የመሰለ ክስተት ቢመለከቱ፥ የሚሰጡት ገለጣ አንድ ዓይነት እንደማይሆን ሁሉ መጽሐፈ ዜና መዋዕልም የብሉይ ኪዳን ነገሥታትን ታሪክ የጻፈበት የራሱ የሆነ የተለየ ዓላማ አለው። 1ኛና 2ኛ ዜናን በመረዳት ስለ ዳዊት፥ ስለ ሰሎሞንና ስለ ሌሎች የይሁዳ ነገሥታት ከፍተኛ ግንዛቤን እናገኛለን።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የአንድን ታሪክ የተለያዩ አመለካከቶች ማየት ጥሩ የሚሆነው ለምንድ ነው? ለ) ስለተፈጸመው ነገር እውነተኛውን ለመረዳት ይህ የሚጠቅመን እንዴት ነው?

ቀደም ሲል ከተመለከትነው ጥናታችን እንደምታስታውሰው፥ የሳሙኤልን፥ የነገሥታትንና የመሳሰሉትን የታሪክ መጻሕፍት የጻፉ ጸሐፊዎች ዓላማቸው በዚያ ዘመን የተፈጸሙትን ነገሮች ሁሉ መተንተን አልነበረም። ይልቁንም የጻፉት ነገር ሕዝቡ አባቶቻቸው በወደቁበት ተመሳሳይ ኃጢአት እንዳይወድቁ ለማስተግር ግልጥ ዓላማዎች ነበሯቸው። የ1ኛና 2ኛ ዜና መጻሕፍት ጸሐፊም የመጽሐፈ ነገሥት ታሪክ የያዘውን የነገሥታት ታሪክ የደገመበት ምክንያት ነበረ። ይህም ዓላማ ከምርኮ በኋላ የነበሩ አይሁዳውያን እግዚአብሔርን እንዴት እንደሚያመልኩና ለእርሱ እንዴት ታማኝ ሆነው ሊቆዩ እንደሚችሉ፥ በዚህም ዓይነት በእግዚአብሔር መባረክን ማግኘት እንደሚችሉ ለማስተማር ነበር።

የ1ኛና 2ኛ ዜና መጻሕፍት አብዛኛውን የ2ኛ ሳሙኤል፥ የ1ኛና 2ኛ ነገሥት ታሪክ ይደግሙታል። ከሳኦል ሞት በኋላ ስለ ነበረውና በሉዓላዊነቱ ስለ ቆየው የእስራኤል መንግሥት ይተርኩልናል። 1ኛ ዜና መዋዕል የእስራኤል ታላቅ ንጉሥ በነበረው በዳዊት ላይ ያተኩራል። አንድ መልካም የሆነ የአይሁድ ሕዝብ መሪ ምን እንደሚመስል በማሳየት፥ የአይሁድ ሕዝብ መሪዎችና የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ምሳሌነቱን ይከተሉ ዘንድ የዳዊትን ታሪክ እንደገና ይነግረናል። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ክርስቲያኖች አርዓያነቱን መከተል ይችሉ ዘንድ መልካም ምሳሌነት ያለው ሰው የሚያስፈልጋቸው ለምንድን ነው? 1ኛ 1ቆሮ 11፣1 ተመልከት። ለ) ጳውሎስ ለክርስቲያኖች የሰጠው ትእዛዝ ምንድን ነው? ሐ) ይህ ትእዛዝ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች በሙሉ ለአባሎቻቸው ሊናገሩት ከሚገባው ትእዛዝ የሚመሳሰለው እንዴት ነው?

2ኛ ዜና መዋዕል በድጋሚ የሚናገረው የመጽሐፈ ነገሥት የመጀመሪያውንና ሁለተኛውን ታሪኮች ነው። ይህም ታሪክ በድጋሚ የሚያወሳው የንጉሥ ሰሎሞንና የይሁዳን ነገሥታት ታሪክ ነው። ታሪኩ የሚያበቃውም የይሁዳ ሕዝቦች ወደ ምርኮ እስከተወሰዱ ድረስ ያለውን በመናገር ነው። 

2ኛ ዜና የ2ኛ ሳሙኤል እንዲሁም የ1ኛና የ2ኛ ነገሥት ታሪክ በድጋሚ የቀረበበት ቢሆንም፥ የመጽሐፈ ዜና መዋዕል ዓላማ ከመጽሐፈ ነገሥት ዓላማ የተለየ ነበር፤ ስለዚህ ጉዳይ በኋላ እናጠናለን። 

የውይይት ጥያቄ፥ 1ኛና 2ኛ ዜና መዋዕልን ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ተመልከት። ስለ መጻሕፍቱ የተጠቀሱትን አስፈላጊ የሆኑ እውነቶች ዘርዝር።

1ኛና 2ኛ ዜና መዋዕል ርዕስ

እንደ 1ኛና 2ኛ ሳሙኤልና እንዲሁም እንደ 1ኛና 2ኛ ነገሥት ሁሉ፥ 1ኛና 2ኛ ዜና መዋዕል በመጀመሪያ አንድ መጽሐፍ ነበር። ልክ እንደ ሌሎቹ መጻሕፍት ሁሉ መጽሐፈ ዜና መዋዕል ለሁለት የተከፈለው የዕብራይስጡ ብሉይ ኪዳን፥ ወደ ግሪክ ቋንቋ በተተረጎመበት ጊዜ ነው። በዕብራይስጥ መጽሐፍ ቅዱስ የዚህ መጽሐፍ ርዕስ ከመጽሐፉ መጀመሪያ ዐረፍተ ነገር ላይ የተገኘ ሲሆን፥ የነገሥታት «ዘመን ቃላት» ወይም «ድርጊቶች» የሚል ነው። «ዜና መዋዕል» የሚለው የእንግሊዝኛው ቃል ትርጉም «ዘገባ» ማለት ሲሆን፥ በነገሥታት ዘመን የነበረው መለኮታዊ ታሪክ ዘገባ ማለት ነው። በአማርኛ «ክስተቶች ወይም ታሪክ» ማለት ነው። 

የመጽሐፈ ዜና መዋዕል ጸሐፊ 

መጽሐፍ ቅዱስ የዚህ መጽሐፍ ጸሐፊ ማን እንደሆነ ጨርሶ ስለማይናገር፥ በበኩላችንም የምንሰጠው አስተያየት ግምታዊ ነው። የዕብራውያን ትውፊት የመጽሐፉ ጸሐፊ ታሪኩን በመጽሐፈ ዕዝራ ያነበብነው ካህን ዕዝራ ነው ይላል። መጽሐፈ ዕዝራ፥ ነህምያና ዜና መዋዕል በአንድ ጸሐፊ መጻፋቸውን የሚያመለክት በርካታ ተመሳሳይነት አለ በማለት ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ይስማማሉ፤ ነገር ግን ሌሎች ምሁራን ደግሞ በርካታ ልዩነትም ስላለ ጸሐፊው ዕዝራ አይደለም ይላሉ። 1ኛና 2ኛ ዜና የተጻፉት በአንድ ሰው ነው።

ጸሐፊው ማን እንደሆነ ባናውቅም ዳሩ ግን የታሪክ ሰው፥ የሥነ መለኮት ትምህርት አዋቂና ሃይማኖታዊ መምህር መሆኑን ከጻፈው መጽሐፉ እንገነዘባለን። ይህንን የምንመለከተው የጻፋቸውን ነገሮች በመረጠበት ሁኔታ ነው። በአንድ በኩል መጽሐፈ ዜና መዋዕል “ስብከት” እንደሆነ መመልከት እንችላለን፤ ምክንያቱም ጸሐፊው ለእግዚአብሔር በታማኝነት ስለ መቆምና እርሱን በቅድስና ስለማምለክ አንዳንድ እውነቶችን ለሕዝቡ ለማስተማር እንደተጠቀመበት ስለምናይ ነው። የብሉይ ኪዳን ታሪኮችን የማስተማርያ መሣሪያዎች አድርጎ ተጠቅሞባቸዋል።

መጽሐፈ ዜና መዋዕል የተጻፈበት ጊዜ

የመጽሐፈ ዜና መዋዕል ታሪኮች ከዳዊት ዘመን ከ1020 ዓ.ዓ. ጀምሮ የይሁዳ ሕዝብ እስከተበተኑበት እስከ 538 ዓ.ዓ. ያለውን ጊዜ ያጠቃልላል። ጸሐፊው ማን እንደሆነ ስላላወቅን፥ ይህ መጽሐፍ መቼ እንደተጻፈ በእርግጠኝነት መናገር አንችልም። ከመጽሐፉ በግልጽ የምንመለከተው ግን፥ ባቢሎን ከወደቀች ከብዙ ዓመታት በኋላ የተጻፈ ሳይሆን እንደማይቀር ነው። ይህ የተጻፈው አይሁዶች ከስደት ወደ ይሁዳ በ538 ዓመተ ዓለም ከተመለሱ በኋላ ነው። ጸሐፊው ዕዝራ ከሆነ የተጻፈው በ450 ዓ.ዓ. ነው። አንዳንድ ምሁራን መጽሐፉ የተጻፈው በ300 ዓ.ዓ. ነው ብለው ቢያስቡም፥ ከዘሩባቤል በኋላ በ400 ዓ.ዓ. ሳይሆን አይቀርም (1ኛ ዜና 3፡17-21)። 

የመጽሐፈ ዜና መዋዕል ጸሐፊ የተጠቀመባቸው ምንጮች 

የመጽሐፈ ዜና መዋዕልን ታሪክ የጻፈው አንድ ጸሐፊ ብቻ ቢሆንም መጽሐፉን ለመጻፍ ግን የተለያዩ ነገሮችን አልተጠቀመም ማለት አይደለም። በዚህ ዘመን ያሉ ምሁራን የተለያዩ መጻሕፍትን እንደሚያነቡና ሲጽፉም እንደሚጠቅሱ ሁሉ የዜና መዋዕል ጸሐፊም በተለያዩ መረጃዎች ተጠቅሞአል። የዜና መዋዕል ጸሐፊ ለዓላማው ምቹ ሆነው ያገኛቸውን የተለያዩ ታሪኮች ከተለያዩ መጻሕፍት በመጠቀም ሌሎቹን ታሪኮች ትቶአቸዋል። ለምሳሌ በ2ኛ ሳሙኤል የዳዊትንና የቤርሳቤህን የኃጢአት ታሪክ እናነባለን። የዜና መዋዕል ጸሐፊ ይህንን ታሪክ የሚያውቀው ቢሆንም የጻፈበትን ዓላማ ስለማያንጸባርቅ አላካተተውም። ቀጥሎ ጸሐፊው መጽሐፈ ዜና መዋዕልን ለመጻፍ ከተጠቀመባቸው ከምናውቃቸው መጻሕፍት አንዳንዶቹ ተዘርዝረዋል፡-

  1. የመጽሐፍ ቅዱስ የተለያዩ መጻሕፍት፥ እንደ ፔንታቱክ፥ ሳሙኤልና ነገሥት የመሳሰሉ 
  2. የተለያዩ የዘር ሐረግ የተተነተነባቸው ሌሎች መጻሕፍት (1ኛ ዜና 4፡33፤ 5፡17፤ 7፡9) 
  3. ደብዳቤዎችንና የታወቁ የመንግሥት መዛግብትን (1ኛ ዜና 28፡11-12፤ 2ኛ ዜና 32፡16-17) 
  4. በሌላ መዛግብት የተጻፉ ግጥሞችና ቅኔዎች፥ ጸሎቶች ንግግሮችና መዝሙሮች (1ኛ ዜና 16፡8-36፤ 29፡10-22፤ 2ኛ ዜና 29፡30፤ 35፡25) 
  5. እንደ እስራኤልና የይሁዳ ነገሥታት መጽሐፍ፥ የዳዊትንና የሰሎሞንን መመሪያዎች የያዙ ሌሎች የታሪክ መጻሕፍት (2ኛ ዜና 16፡11፤ 26፡22፤ 35፡4) 
  6. በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የማይገኙ የነቢያት ጽሑፎች፥ ማለትም (የሳሙኤል፥ የናታንና፥ የጋድ ዜና መዋዕል፥ የአሐያና የአዶ ትንቢተች የሻማያ፥ የኢዩና የኢሳይያስ ዘገባዎች ናቸው፤ 1ኛ ዜና 29፡29፤ 2ኛ ዜና 9፡29፤ 12፡15፤ 20፡34፤ 32፡32)። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: