አይሁድ በምርኮ ምድር

አይሁድ በ586 ዓ.ዓ. ከተማርኩበት ጊዜ ጀምሮ ሕዝቡ ከምርኮ እንዲመለሱ እስከተፈቀደበት እስከ 538 ዓ.ዓ. ድረስ ስለነበረው ሁኔታ የሚናገር የታሪክ መጽሐፍ የለም። በእነዚህ አምሳ ዓመታት ሁለት ዋና ዋና ነቢያት ነበሩ። አንዱ በባቢሎን መንግሥት ውስጥ የኖረውና የሠራው ዳንኤል ሲሆን፥ ሌላው በምርኮ ከነበሩት ወገኖቹ ጋር በባቢሎን የኖረው ሕዝቅኤል ነበር። በባቢሎን ስለኖሩባቸው ስለ እነዚህ 50 ዓመታት የምናውቀው ብዙ ነገር የለም። በባቢሎንና በመካከለኛው ምሥራቅ ተበትነው የኖሩ ይመስላሉ። ነገር ግን ይሁዳ ከተደመሰሰችበት ከ586 ዓ.ዓ. በኋላ ሕዝቡ በምርኮ ምድር ማረስና የንግድ ሥራ መሥራት ጀመሩ። በባቢሎናውያንም እጅ ክፉ ነገር አይደርስባቸውም ነበር። 

የባቢሎን መንግሥት 

ከአሦር መንግሥት መውደቅ በኋላ፥ የባቢሎን መንግሥት ዓለምን መምራት ጀመረ። ኃይላቸው እጅግ ታላቅ የነበረ ቢሆንም፥ መንግሥታቸው የቆየው ግን በሜዶንና በፋርስ እስኪተካ ድረስ ከ70 ዓመታት ጥቂት ለሚበልጥ ጊዜ ነበር። የባቢሎን መንግሥት ዋና ዋና መሪዎች የነበሩት ከዚህ እንደሚከተለው ተዘርዝረዋል፡-

  1. ናቦኋላሳር (626-605 ዓ.ዓ.) በባቢሎን መንግሥት የመጀመሪያ ንጉሥ የናቡከደነፆር አባት የነበረው ናቦቁላሳር ነበር። በአሦር ላይ የተደረገውን ዓመፅ በመምራት፥ የባቢሎንን ከተማ በ626 ዓ.ዓ. ያዘና ንጉሥ ሆነ። የአሦርን መንግሥት ሙሉ በሙሉ ለማጥፋት የቻለው በ609 ዓ.ዓ. ነበር። 
  2. ናቡከደነፆር (605-562 ዓ.ዓ.) በባቢሎን መንግሥት ውስጥ እጅግ ታላቅ የነበረው መሪ ናቡከደነፆር ነበር። አባቱ ከመሞቱ ከጥቂት ጊዜ በፊት፣ በከነዓን ላይ የተደረገውን ጦርነት በመምራት ይሁዳ ለባቢሎን መንግሥት እጅ እድትሰጥ አድርጎ ነበር። ናቡከደነፆር ራሱ እስከነበረበት ዘመን ድረስ ከነበሩ መንግሥታት ሁሉ የላቀ እጅግ ገናና መንግሥትን ያቋቋመው ታላቅ ጦረኛ ስለነበረ ብቻ ሳይሆን፥ ታላቅ ከተማና ሕንጻ ገንቢም ስለነበረ ነው። የባቢሎንን ከተማ በጠላት እንደማትደፈር አድርጎ ገነባት። ከጥንቱ ዓለም ሰባት አስደናቂ ነገሮች አንዱ የተባለውን የአትክልት ስፍራ ለሚስቱ ሠራላት። እርሱ ከሞተ በኋላ የባቢሎን መንግሥት ኃይል እየተዳከመ ሄደ። 
  3. ከናቡከደነፆር በኋላ ሌሎች አራት ነገሥታት ይኖሩ ነበር። በመጀመሪያው የነገሠው አቤል ሙርዱክ ወይም ኢቭል ሜሮዳክ በመባል የሚታወቀው ሰው (562-560 ዓ.ዓ.) ሲሆን፥ ሁለተኛ ኔርግሊሳር (560-556 ዓ.ዓ.) ቀጥሎም ናቦኒዱስ (556-539 ዓ.ዓ.) ነገሠ። ይህ ሰው ከፖለቲካ አመራር ይልቅ ትኩረቱ በሃይማኖታዊ ጉዳይ ላይ ነበር። ብሔራዊ እምነት የነበረውን የማርዱክን አምልኮ የሚያስፈጽሙትን ቀሳውስት ባስቀየመ ጊዜ ሕዝቡ ከሥልጣን አወረዱትና ልጁን ብልጣሶርን በምትኩ አነገሡበት። ናቦኒዱስም ለመኖር በዐረቢያ ወዳለ ቤተ መንግሥት ሄደ፡፡ የፋርስ ወታደሮች በ539 መጥተው የባቢሎንን መንግሥት ባሸነፉበት ጊዜ በሥልጣን ላይ የነበረው መሪ ብልጣሶር ነበር። እግዚአብሔር መንግሥትህ ተደምስሳለች ብሎ በግድግዳ ላይ በጻፈና ዳንኤልም በዚያ ምሽት መንግሥቱ እንደምትከፈል በተናገረ ጊዜ በሥልጣን ላይ ያለው መሪ ብልጣሶር ነበር (ዳን. 5)።

ሜዶንና ፋርስ 

የሜዶንና የፋርስ ንጉሠ ነገሥት ግዛት ከ539 አንስቶ የግሪክ ንጉሥ በነበረው ታላቁ እስክንድር እስከ ተሸነፈበት እስከ 331 ዓ.ዓ. ድረስ በገናንነት ቆይቷል። የመጽሐፍ ቅድስ ታሪክ ግን የፋርስ መንግሥት ከ539 – 400 ዓ.ዓ. የቆየበትን ዘመን ብቻ የሚሸፍን ነው። የፋርስ ዘመነ መንግሥት በዓለም ውስጥ ካሉት መንግሥታት ይልቅ በዚያን ጊዜ ላቅ ያለና ገናና ገዢ እንደ ነበረ የዓለም ታሪክ ይመሰክራል። ከዚህ በመቀጠል በፋርስ ዘመን መንግሥት እስከ 400 ዓመተ ዓለም ድረስ ይገዙ የነበሩት የንጉሦች ስም ተዘርዝረዋል። 

  1. ታላቁ ቂሮስ፡- (559-530 ዓ.ዓ.)፡- ፋርስን እስከዚያ ዘመን ድረስ ከነበሩ መንግሥታት ሁሉ የላቀች እጅግ ታዋቂ ያደረጋት የቂሮስ ወታደራዊ አመራር ነበር። ቂሮስ በሜዶን ቁጥጥር ሥር የሚኖር ንጉሥ ነበር፤ ነገር ግን በሜዶን መንግሥት ላይ ዓመፀ። በኋላም የሜዶንን ሕዝብ ከእርሱ ጋር እንዲተባበሩ አስገደዳቸውና የሜዶንና የፋርስ ንጉሠ ነገሥት ግዛት የተባለውን መንግሥት አቋቋመ። በጥምሩ ውስጥ ዋናውን ቦታ የያዘው የፋርስ መንግሥት ነበር፣ ስለዚህ ብዙ ጊዜ ይህ መንግሥት የፋርስ መንግሥት ይባል ነበር። የቂሮስ የንጉሠ ነገሥት ግዛት ከሜዶን ወደ ባቢሎን፥ እስከ ሕንድ ወሰን፥ እንዲያውም እስከ ግብፅ ድረስ ሰፋ።

አሦራውያንና ባቢሎናውያን ከተጠቀሙበት መንገድ በተለየ ሁኔታ፥ ቂሮስ በጎነትንና ርኅራኄን በማሳየት ሕዝቡ እንዲከተሉት አደረገ። አሦራውያንና ባቢሎናውያን ዋና የሆኑ ሰዎችን ማርኮ የመውሰድና በግዛታቸው ሁሉ ውስጥ የማሰራጨት ፖሊሲ (መመሪያ) ነበራቸው፤ ስለዚህ አሦር ከእስራኤል፥ ባቢሎን ደግሞ ከይሁዳ የወሰዷቸውን ሕዝቦች መንግሥታቸው ሁሉ ውስጥ አሰራጭተዋቸው ነበር። ፋርስ ግን በምርኮ ተይዘው የመጡትን እነዚህን ሰዎች ሁሉ ወደ አገራቸው እንዲመለሱና የአምልኮ ስፍራቸውንም እንደገና እንዲገነቡ ፈቀዱላቸው። ይህ ነገር የተፈቀደው ለአይሁድ ብቻ ባይሆንም፥ በመጽሐፈ ዕዝራ አይሁድ ይህንን ዕድል እንዴት እንደተጠቀሙበትና ወደ እስራኤል ተመልሰው ቤተ መቅደሳቸውን እንደሠሩ እንመለከታለን። – 

የውይይት ጥያቄ፥ ኢሳ. 45፡1፥ 13 አንብብ። ይህ ለኢሳያስ ትንቢት ፍጻሜ የሆነው እንዴት ነው? 

  1. ካምቢኤስ (530-522 ዓ.ዓ.)። ይህ ሰው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አልተጠቀሰም፤ ነገር ግን አይሁድ በቂሮስ ዘመነ መንግሥት ሊሠሩ የጀመሩትን ቤተ መቅደስ እንዳይሠሩ በዚህ ሰው ዘመን መንግሥት ተከልክለው ነበር። 
  2. ቀዳማዊ ዳርዮስ (522-486 ዓ.ዓ.)፡- ይህ ንጉሥ ታላቁ ዳርዮስ በመባል የሚታወቅ ሲሆን፥ አይሁድ ቤተ መቅደሳቸውን እንዲሠሩ እንደገና የፈቀደ ሰው ነው (ዕዝ. 6፡1-12፤ ሐጌ 1፡1)። የቤተ መቅደሱ ሥራ በ516 ዓ.ዓ. ተጠናቀቀ። ዳርዮስ ታላላቅ ከሚባሉት የፋርስ የጦር መሪዎች አንዱ ሲሆን፥ የፋርስን መንግሥት እስከ ግሪክ ድረስ ያስፋፋ ሰው ነበር። በሥሩ ላሉ መንግሥታት ሁሉ አንድ ዓይነት ሕግ ለመስጠት ስለሞከረ «ሕግ ሰጪ» በመባል ይታወቃል።
  3. ቀዳማዊ አርጤክስስ (486-425 ዓ.ዓ.)። ይህ ሰው በዕብራይስጡ መጽሐፍ ቅዱስ አህሳዊሮስ በመባል ይታወቃል። በአማርኛው መጽሐፍ ቅዱስ ግን አህሳዊሮስን ከአርጤክስስ በኋላ ከነገሠው ከአርጤክስስ ጋር የሚምታታ የተሳሳተ አተረጓጎም አለ። አርጤክስስ ወይም አህሳዊሮስ ብለን የምንጠራው አስቴርን ያገባው ንጉሥ ነው። በተጨማሪ በዕዝራ 4፡6 ተጠቅሷል። (ማስታወሻ፡- በዕዝራ 4፡7 ላይ የተጠቀሰው ግን የሚቀጥለው ንጉሥ አርጤክስስ ነው)። በዓለም ታሪክ የአርጤክስስ ዝና ካሸነፉት ከግሪኮች ጋር ባደረገው ጦርነት የታወቀ ነው። በተጨማሪ ትልልቅ ከተሞችን በመሥራት ችሎታው ይታወቃል። 
  4. ቀዳማዊ አርጤክስስ (464-425 ዓ.ዓ.)፡- አርጤክስስ በመጽሐፍ ቅዱሳችን የተጠቀሰው የመጨረሻው የፋርስ ንጉሥ ነው። በመጀመሪያ ዕዝራ፥ ቀጥሉም ነህምያ ወደ ይሁዳ እንዲመለሱ የተፈቀደላቸው በእርሱ ዘመነ መንግሥት ነበር።

የመጽሐፈ ዕዝራ፥ ነህምያና አስቴር ቅደም ተከተል

የመጽሐፈ ዕዝራ፥ ነህምያና አስቴር ታሪክ አፈጻጸም በጊዜ ቅደም ተከተል መሠረት አልቀረበም። በመቀጠል የእነዚህ መጻሕፍት ቅደም ተከተላቸውን እናያለን።

  1. የመጀመሪያዎቹ አይሁዳውያን ወደ ኢየሩሳሌም መመለስ፡- ዕዝራ 1-6 (539-515 ዓ.ዓ.) 
  2. የአስቴር ታሪክ፡- አስቴር 1-10 (በ480 ዓ.ዓ.ገደማ) 
  3. የተሐድሶው መሪ ዕዝራና ሁለተኛው የአይሁድ ቡድን ከምርኮ መመለስ፡- ዕዝራ 7-10 (457 ዓ.ዓ.) 
  4. የአስተዳዳሪው ነህምያና የሦስተኛው የአይሁድ ቡድን ከምርኮ መመለስ፡- ነህ. 1-13 (444-430 ዓ.ዓ.)

(ማስታወሻ፡- አንዳንድ ምሁራን ዕዝራ 7፡8ን በሚመለከት የአጻጻፍ ስሕተት አለ ይላሉ፤ ይኸውም በአርጤክስስ በሰባተኛው ዓመት የሚለው ቃል በሠላሳ ሰባተኛው ዓመት መሆን አለበት ብለው ያስባሉ። ይህም የዕዝራን መመለስ ወደ 428 ዓ.ዓ. በማራዘም ከነህምያ በኋላ ያደርገዋል። ይህንን ለማመን ግን በቂ ምክንያት የለም።)

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: