የውሃ ጥምቀት

ኢየሱስ በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ በውኃ እንዲጠመቁ አዟል፡፡ “ኢየሱስም ቀረበና እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፦ ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ። እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ …” ማቴዎስ 28:18-20፣ በተጨማሪ ሐዋ. 2፡ 38-41 ተመልከት። 

“መጠመቅ” ማለት “ሙሉ በሙሉ መስመጥ ማለት ነው”። አንድ ሰው ሃጢአተኛ መሆኑን አውቆ ንስሐ ከገባ እና ኢየሱስ የሞተው ስለ እርሱ እንደሆነ ካመነ፣ ውሃ ወዳለበት ስፍራ ተወስዶ የሰው ምስክር ባለበት ስፍራ የውሃ ጥምቀት ሊያደርግ ይገባዋል፡፡ ለምን ይሆን አማኞች ይህን ስርአት እንዲፈጽሙ ኢየሱስ ያዘዘው? 

ሀ) የውሃን ጥምቀትን መረዳት

የውሃ ጥምቀት ምን እንደ ሆነ መረዳት ለአሸናፊ እና ነፃ የወጣ ክርስቲያናዊ ሕይወት ቁልፍ ነው፡፡ አማኙ ውኃው ውስጥ መግባቱ እና መውጣቱ በአማኙ ሕይወት ውስጥ ለተከናወነው መንፈሳዊ ነገር ስዕላዊ (አካላዊ) መግለጫ ነው፡፡ 

ለ) ክርስቶስ ያደረጋቸው አራት ታላቅ ሥራዎች በውሃ ጥምቀት ሲገለጡ

  • ኢየሱስ ሲሞት እኔም ከእርሱ ጋር ሞቻለሁ (በሞቱ ተካፍያለሁ)

“ከእንግዲህ የኀጢአት ባሮች እንዳንሆን፣ የኀጢአት ሰውነት እንዲሻር አሮጌው ሰዋችን ከእርሱ ጋር እንደ ተሰቀለ እናውቃለን፤ ምክንያቱም የሞተ ከኀጢአት ነጻ ወጥቶአል።”  (አ.መ.ት. ሮሜ 6፡6-7)

  • ኢየሱስ ሲቀበር እኔም ከእርሱ ጋር ተቀብሬአለሁ (በቀብሩ ተካፍያለሁ)

“ወይስ ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ የተጠመቅን ሁላችን ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ እንደ ተጠመቅን አታውቁምን? እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፥ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን።” (ሮሜ 6፡3-4)

  • ኢየሱስ ከሞት ሲነሳ እኔም ከእርሱ ጋር በአዲስ ሕይወት ተነስቻለሁ (በትንሳኤው ተካፍያለሁ)

“እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፥ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን። ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን፤”

  • ኢየሱስ ሲያርግ እኔም ከእርሱ ጋር አርጌያለሁ (በእርገቱ ተካፍያለሁ)

“በሚመጡ ዘመናትም በክርስቶስ ኢየሱስ ለእኛ ባለው ቸርነት ከሁሉ የሚበልጠውን የጸጋውን ባለ ጠግነት ያሳይ ዘንድ፥ ከእርሱ ጋር አስነሣን በክርስቶስ ኢየሱስም በሰማያዊ ስፍራ ከእርሱ ጋር አስቀመጠን።” ኤፌ 2፡6-7 በተጨማሪ ቆላስይስ 3፡1 ን ተመልከት

ሐ) የውሃ ጥምቀት፣

  • የቀብር ስነሥርዐትህ ነው!

የቀበር ስነሥርዐት የሚካሄደው ግለሰቡን ለመግደል አይደለም፡፡ ግለሰቡ አስቀድሞ ስለሞተ ለቀብር እንጂ፡፡

አሮጌው ማንነትህ በክርስቶስ ሆኖ “ስለሞተ” ይህን አሮጌ ሕይወት በ ውሃ ጥምቀት ምሳሌነት ትቀብረዋለህ ማለት ነው፡፡ 

  • በትንሳኤ ለተቀበልከው አዲስ ሕይወት ብስራት ነው፡፡

በክርስቶስ አዲስ ፍጥረት እንደሆንክ ከውሃው ውስጥ በመውጣትህ ትመሰክራለህ/ትገልጣለህ፡፡ 

“ነገር ግን ከክርስቶስ ጋር ከሞትን ከእርሱ ጋር ደግሞ በሕይወት እንድንኖር እናምናለን፤ ክርስቶስ ከሙታን ተነሥቶ ወደ ፊት እንዳይሞት ሞትም ወደ ፊት እንዳይገዛው እናውቃለንና። መሞትን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ለኃጢአት ሞቶአልና፤ በሕይወት መኖርን ግን ለእግዚአብሔር ይኖራል። እንዲሁም እናንተ ደግሞ ለኃጢአት እንደ ሞታችሁ፥ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ሆናችሁ ለእግዚአብሔር ሕያዋን እንደ ሆናችሁ ራሳችሁን ቁጠሩ።” ሮሜ 6፡8-11

መ) ሁለቱ መንግሥታት

“እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” ቆላስይስ 1፡13-14

በዚህች አለም ውስጥ የሚወለዱ ሰዎች ሁሉ በጨለማው አለም መንግሥት ውስጥ ነው የሚወለዱት፤ በፍጥረታቸው (በውልደታቸው) የአምባገነኑ ሰይጣን ባሪያዎች ናቸው፡፡ በሞት ካልሆነ በቀር በሌላ በምንም አይነት መንገድ ከዚህ የጨለማ መንግሥት ማምለጥ (በውጣት) አይቻልም፡፡ እንዲሁም፣ በዳግም ልደት ካልሆነ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግስት መግባት አይቻልም፡፡ ይህ እንዲሆን ክርስቶስ ሞታችንም ሕይወታችንም (ዳግም ልደታችንም) ሆኖልናል፡፡ ይህንን እውነት በጥምቀት እንመሰክራለን (እናውጃለን)፡፡  

ሠ) ሁለቱ ዘሮች

ሁለት መንግሥታት እንዳሉ ሁሉ በሁለቱ መንግሥታት ውስጥ የሚኖሩ ሁለት የሰው ዘሮች አሉ፡፡ የአዳም ዘር በጨለማው መንግሥተ ውስጥ የሚኖረው የሰው ዘር ሲሆን የአዲሱ ፍጥረት (የሰው የሰው ዘር) ደግሞ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ የሚኖረው ነው፡፡ 

  • ፊተኛው (የመጀመሪያው) አዳም

“ሁሉ በአዳም እንደሚሞቱ…” 1 ቆሮ 15፡22 በተጨማሪ ሮሜ 5:12 ን ተመልከት፡፡ አዳም የሰው ዘር ሁሉ አባት ነው፡፡ የአዳም ሃጢአት እርሱን እና ዘሩን (እኛን ሁላችንን) ከእግዚአብሔር ለይቶናል፡፡ በእርሱ መተላለፍ ምክንያት የእርሱን አመጸኛ እና የተበላሸ ተፈጥሮን ወርሰናል፤ ሞት ወደእኛ የደረሰውም በእርሱ በኩል ነው፡፡ የአዳም ዘሮች “አዳማውያን” ይባላሉ፡፡  

  • ኋለኛው (የመጨረሻው) አዳም

“ገና ደካሞች ሳለን ክርስቶስ ዘመኑ ሲደርስ ስለ ኃጢአተኞች ሞቶአልና” ሮሜ 5:6፡፡ እግዚአብሔር ሃጢአትን ለማስወገድ የወሰደው እርምጃ ይህን በሃጢአት የተበከለውን የአዳም ዘር ማሻሻል ሳይሆን ፈጽሞ በማጥፋት ሌላ አዲስ ዘርን ማምጣት ነበር፡፡ ኢየሱስ ኋለኛው አዳም ነው፡፡ ኢየሱስ ወደዚህች አለም የመጣው እንደ መጨረሻው የአዳም ዘር እና እንደመጀመሪያው አዲስ የሰው ዘር በመሆን ነበር፡፡ በመስቀል ላይ ሲሰቀል እንደመጨረሻው የአዳም ዘር ሆኖ ነበር የተሰቀለው፡፡ በመስቀል ላይ ሲሞት የአዳም ዘርና የዘሩ ሃጢአታዊ ተፈጥሮ አብሮ ሞቷል፡፡ እግዚአብሔር የወደቀውን የሰው ዘር በኢየሱስ ውስጥ ሆኖ እንዲሞት አድርጓል፡፡ የአዳም ዘር በክርስቶስ ሆኖ በመስቀል ላይ እንዲሞት ተደርጓል፡፡ 

  • ሁለተኛው ሰው

“ሁሉ በአዳም እንደሚሞቱ እንዲሁ ሁሉ በክርስቶስ ደግሞ ሕያዋን ይሆናሉና።” 1ኛ ቆሮ 15፡22 በእርሱ አዲስ ፍጥረት ይፈጠር ዘንድ ኢየሱስ ወደምድር የመጣው እንደ እግዚአብሔር ሁለተኛ ሰው ሆኖ ነው፡፡ ኢየሱስ ከሞት የተነሳው እንደ ኋለኛው (መጨረሻ) አዳም ሆኖ አይደለም፤ የአዲስ ፍጥረት ራስ እደሆነ ሁለተኛ ሰው እንጂ፡፡

“እንዲሁ ደግሞ፦ ፊተኛው ሰው አዳም ሕያው ነፍስ ሆነ ተብሎ ተጽፎአል፤ ኋለኛው አዳም ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ሆነ። ነገር ግን አስቀድሞ ፍጥረታዊው ቀጥሎም መንፈሳዊው ነው እንጂ መንፈሳዊው መጀመሪያ አይደለም። የፊተኛው ሰው ከመሬት መሬታዊ ነው፤ ሁለተኛው ሰው ከሰማይ ነው። መሬታዊው እንደ ሆነ መሬታውያን የሆኑት ደግሞ እንዲሁ ናቸው፥ ሰማያዊው እንደ ሆነ ሰማያውያን የሆኑት ደግሞ እንዲሁ ናቸው። የዚያንም የመሬታዊውን መልክ እንደ ለበስን የሰማያዊውን መልክ ደግሞ እንለብሳለን።” 1 ቆሮ 15፡45-49)

  • አዲሱ ፍጥረት

“ስለዚህ ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥረት ነው፤ አሮጌው ነገር አልፎአል፤ እነሆ፥ ሁሉም አዲስ ሆኖአል።” 2ቆሮ 5፡17 በተጨማሪ ኤፌ 2፡10 ን ይመልከቱ

በውሃ ጥምቀት ለወዳጆቻችንና ለእድምተኞቻችን ሁሉ የምናውጀው ነገር ከዚህ ቀን ጀምሮ የአዳም ዘር እና የጨለማው መንግሥት አካል አለመሆናችንን ነው፡፡ በክርስቶስ አዲስ ፍጥረት ነን፤ መኖሪያችንም በእግዚአብሔር መንግስት ውስጥ ነው፡፡ 

ውሳኔዪ

በዚህ ጥናት አማካኝነት፣ አሮጌ ሕይወቴ ከኃጢያቱ እና ከሚያስከትለው ፍርድ ጋር ከክርስቶስ ጋር እንደሞተ አውቂያለው፡፡ አሁን በኢየሱስ ትንሣኤ ምክንያት አዲስ ሕይወት እደተቀበልኩም ተረድቻለሁ። የውሃ ጥምቀት የእነዚህ መንፈሳዊ እውነቶች አካላዊ መገለጫ ስለሆነ በውሃ ለመጠመቅ እና ይህንን እውነት ለሌሎች ለማካፈል ቃል እገባለሁ።

ምንጭ፣ The Shepherd Staff

ትርጉም፣ አዳነው ዲሮ

2 thoughts on “የውሃ ጥምቀት”

  1. የውኃ ጥምቀት በማን ስም መከናወን አለበት? የምታደርጉትን ሁሉ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አድርጉ ማለቱን ልብ በሉ። የውኃ ጥምቀት ለምን? መጠመቅ በምንባቡ ውስጥ የተገለጹት እንዳለ ሆኖ ሌሎች ያልተጠቀሱ ግን አሉ ለምሳሌ ሐዋ 2:-38,,ሐዋ22:-16 ከኃጢአት ለመታጠብ እንደሆነ ተጽፏል። 1ጴጥ3:-21 ለመዳን መሆኑ ተጽፏል የተጻፈውን መቀበል ግድ ነው። የምንቀበልውና የማንቀበለው የምናምንበት እና የማናምንበት የእኛና የእነርሱ የምንለው የለም።

    1. ጥምቀት የዘላለምን ሕይወት ለማግኘት (ለመዳን) አስፈላጊ ነው ወይ?

      የውሃ ጥምቀት ክርስቲያን በምድራዊ ሕይወቱ ሳለ ሊደርጋቸው ወይም ሊታዘዛቸወ ከሚገባቸው መንፈሳዊ ትዕዛዛት መካከል አንዱ እንደሆነ ብናምንም በውሃ ጥምቀት የሃጢአት ስረየት ይገኛል፣ ወይም በዚህ መንገድ የዘላለም ሕይወት ይወረሳል የሚለውን ሃሳብ ግን አጥብቀን እንቃወማለን። የውሃ ጥምቀት አማኝ ከክርስቶስ ሞት፣ መቀበርና መነሳት ጋር በእግዚአብሔር ልዩ አሰራር እንደተባበር የሚገልጥበት ማሳያ ነው። የሮሜ መልክት እንዲህ ይላል፦”ወይስ ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ የተጠመቅን ሁላችን ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ እንደ ተጠመቅን አታውቁምን? እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፥ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን።” (ሮሜ 6:3-4)። አንድ አማኝ በጥምቀት ወቅት በውሃው ውስጥ ሲጠልቅ ከክርስቶስ ጋር አብሮ መሞቱንና መቀበሩን ሲያመለከት ከውሃው ሲወጣ ደግሞ ከክርስቶስ ጋር አብሮ መነሳቱን ያሳያል።

      መዳን ወይም የሃጢአት ይቅርታን ማግኘት ወይም የእግዚአብሔር ልጅ ለመሆን ዳግም ልደት ማግኘት በቀጥታ ክክርስቶስ የቤዛነት ስራ ጋር የተገናኘ ነው። ከመዳን ጋር በተያያዘ የሰው ልጅ ዋንኛና ብቸኛ ችግር ሃጢአት ነው። ለዚህ መፍትሄው ደግሞ የሃጢአት ስረየት ማግኘት ነው። ለሃጢአት ስረየት ብቸኛው መፍትሄ ነውር የሌለበት ፍጹም መስዋእት (ደም) መሆኑን ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስ ከጫፍ እስከ ጫፍ የሚመሰክርልን መንፈሳዊ እውነት ነው (ዕብራውያን 9:22)። እናም የዘላለምን ሕይወት ወይም የሃጢአትን ይቅርታ ከዚህ የክርስቶስ የመስዋዕት ደም ውጪ እንደሚገኝ ማሰበ የዘላለምን ሕይወት በራሳችን ጥረት (በስራችን) ለማግኘት ከመሞከር ውጪ ሌላ ትርጉም ሊኖረው አይችልም። የውሃ ጥምቀትም ሆነ ሌሎች በራሳቸው መልካም የሆኑ ነገሮች፣ ከእግዚአብሔር ጋር እርቅን ፈጽመን የዘላለም ሕይወት ለማግኘት ከክርስቶስ የመስቀል ስራ ጋር ተደምረው የሚያስፈልጉ እነደሆኑ ማሰብ መጽሐፍ ቅዱሳዊ አለመሆኑ ብቻ ሳይሆን የክርስቶስን ሞት ከንቱ ማድረግም ጭምር ነው (ገላቲያ 2:21)። የክርስቶስ ሞት ብቻውን (ያለምንም ሌላ ተጨማሪ ነገር) ለሃጢአታችን አስፈላጊ የሆነውን ክፍያ ሁሉ ፈጽሟል (ሮሜ 5:8፤ 2ቆሮንቶስ 5:21)። ይህንን በክርስቶስ ስቃይ የተገኘ የእግዚአብሔር ነጻ ስጦታ ያራሳችን የምናደርግበት ብቸኛ መንገድ ደግሞ ማመን እንደሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ ማእከላዊ ትምሕርት ነው (ዮሐንስ 3:16፤ የሐዋሪያት ስራ 16:31፤ ኤፌሶን 2:8-9)። እናም የውሃ ጥምቀት አማኝ ይህን የእግዚአብሔርን ስጦታ በእምነት ተቀብሎ የሃጢአት ይቅርታን ካገኘና የዘላለም ሕይወትን ከተቀበለ በኋላ ያሚፈጽመው የመታዘዝ ተግባር እንጂ ለመዳን ብሎ ያሚያደርገው ስርዐት አይደለም (ሐዋሪያት ስራ 8:36-37)።

      በእርግጥ በአንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ላይ ጥምቀት ለመዳን የምንፈጽመው ተግባር እንደሆነ የሚመስሉ አገባቦችን እናይ ይሆናል። ሆኖም ግን፣ መጽሐፍ ቅዱስ መዳን የሚገኝበትን መንገድ በአጠቃላዩ አውድ ውስጥ በግልጽ ስለጠቆመን (ዮሐንስ 3:16፤ ኤፌሶን 2:8-9፤ ቲቶ 3:5)፣ እነኚህ ጥቅሶች ከምናስበው ውጪ የተለየ ትርጉም እንዳላቸው ማሰብ ይኖርብናል፤ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ እርስ በእርሱ አይጋጭምና።

      የውሃ ጥምቀት ለመዳን አስፈላጊ ቢሆን ኖሮ ቅዱስ ጳውሎስ ለምን “…ከቀርስጶስና ከጋይዮስ በቀር ከእናንተ አንድን እንኳ ስላላጠመቅሁ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ” ይላል? (1ቆሮንቶስ 1:14)። ለምን “ለማጥመቅ ክርስቶስ አልላከኝምና፥ ወንጌልን ልሰብክ እንጂ…” ይላል? (1ቆሮንቶስ 1:17)። የውሃ ጥምቀት ለመዳን አስፈላጊ ነገር ከሆነ እንዴት ቅዱስ ጳውሎስ ባለማጥመቁ እግዚአብሔርን ያመሰግናል? እንዴትስ “ክርስቶስ ለማጥመቅ ስላልላከኝ አመሰግናለሁ” ይላል? እንዴትስ ወንጌል ማለት ምን ማለት እንደሆነ ባብራራበት በዚሁ መልክቱ ላይ ጥምቀትን ሳያካትት ሊያልፍ ይችላል (1ቆሮንቶስ 15:18)? ቅዱስ ጳውሎስ የውሃ ጥምቀት ለመዳናችን አስፈላጊ መሆኑን እያወቀ እነዚህን አረፍተ ነገሮች ተናግሮ ከሆነ፣ እያለ ያለው “ስላልዳናችሁ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ” ነው። ይህ ከአንደበቱ እንደማይወጣ ሁላችንን የሚያስማማ ሃሳብ ከሆነ እንግዲያው ቅዱስ ጳውሎስ እየተናገረ ያለው ከእግዚአብሔር ፍርድ አምልጠን የዘላለም ሕይወት ለማግኘት ጥምቀት አስፈላጊ ነገር አለመሆኑን ነው።

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading