ነህምያ 11-13

ሕዝቡ ስለ ኃጢአታቸው ሕዝባዊ ኑዛዜ በማድረጋቸውና ለእግዚአብሔር ሕግጋት ለመታዘዝ በግልጽ ቃል ኪዳን በመግባታቸው ብቻ ይህ ውሳኔ ለረጅም ጊዜ ይቆያል ማለት አይደለም። ቤተ ክርስቲያንን በሚመለከት የሚያሳዝነው ነገር እግዚአብሔርን ለመከተልና ለእርሱም ለመታዘዝ ብዙ ጊዜ በርካታ ቃል ኪዳን ብንገባም፥ ወዲያውኑ ባለመታዘዝ መመላለሳችን ወይም ቤተ ክርስቲያን ብዙውን ጊዜ መልሳ በኃጢአት ስለምትወድቅ፥ ሕዝቡ ለእግዚአብሔር የተስፋ ቃል ከመግባታቸው በፊት በነበሩበት ሁኔታ መኖር መጀመራቸው ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ ሰዎች ለእግዚአብሔር የሚያደርጓቸውን አንዳንድ የተስፋ ቃሎች ዘርዝር። ለ) ከእነዚህ ተስፋዎች አብዛኛዎቹ ሳይፈጸሙ የሚቀሩት እንዴት ነው? ሐ) ለእግዚአብሔር የገባሃቸው አንዳንድ የተስፋ ቃሉችን ጥቀስ። መ) ከገባሃቸው የተስፋ ቃሎች መካከል የፈጸምሃቸው የትኞቹ ናቸው? ሀ) ያልፈጸምሃቸውስ የትኞቹ ናቸው? ረ) ልትፈጽማቸው ያልቻልክበት ምክንያት ምንድን ነው? 

የውይይት ጥያቄ፥ ነህምያ 11-13 አንብብ። ሀ) ነህምያ ኢየሩሳሌምን እንደገና በሕዝብ ለመሙላት ምን አደረገ? ለ) የኢየሩሳሌም ቅጥር ለእግዚአብሔር አልፎ የተሰጠበትን ሥርዓት ግለጥ። ሐ) ነህምያ ከፋርስ ከተመለሰ በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ያመጣቸውን የተለያዩ መንፈሳዊ መነቃቃቶች ዘርዝር።

አሁን የኢየሩሳሌም ቅጥር ተሠርቶ ስላለቀ ነህምያ ሌሉች ሁለት ዓላማዎች ነበሩት። በመጀመሪያ፥ በኢየሩሳሌም የሚኖሩ በርካታ ሰዎችን መፈለግ ሲሆን፥ ይህም ከተማይቱ ባዶ እንዳትሆን ለማድረግ ነበር፤ ስለዚህ ነህምያ ሕዝቡ ዕጣ እንዲጥሉና ከየአሥሩ ሰው አንድ ሰው በኢየሩሳሌም እንዲኖር ወሰነ።

ሁለተኛ፥ ነህምያ የቅጥሩን መሠራት ምክንያት በማድረግ በሚኖረው መንፈሳዊ በዓል ላይ የሚያገለግሉ መዘምራንና የሃይማኖት መሪዎችን አደራጀ። ቅጥሩን ለመጨረስ የቻሉት በእግዚአብሔር እርዳታ መሆኑን ተገንዝበው ስለ ነበር ምርጫውን ለእግዚአብሔር አሳልፈው ሰጡት። ነህምያ ሕዝቡንና መዘምራኑን በሁለት ቡድን በማደራጀቱ ከቅጥሩ ጫፍ አንሥቶ በኢየሩሳሌም ቅጥር ዙሪያ እየዘመሩ እግዚአብሔርን ያመሰግኑ ነበር። ለሕዝቡ ሁሉ ይህ ታላቅ በዓል ነበር።

ነህምያ የይሁዳ ገዢ ሆኖ ለ12 ዓመታት ከሠራ በኋላ ወደ ፋርስ በመመለስ ከንጉሥ ጋር መሥራት ጀመረ። በዚያ የቆየው ስንት ጊዜ እንደነበር ባናውቅም፥ በመጨረሻ ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሶ እንዲኖር ተፈቀደለት። የሕዝቡ መንፈሳዊ ሕይወት በከፍተኛ ሁኔታ ስለቀነሰና በኃጢአት ስለ ወደቁ፥ ነህምያ ለተወሰነ ጊዜ ከእነርሱ ርቆ እንደ ነበር በግልጥ ያሳየናል።

ነህምያ ወደ ኢየሩሳሌም በተመለሰ ጊዜ ሕዝቡ በኃጢአት ወድቀው አገኛቸው። ነህምያ በፈሪሀ እግዚአብሔር ላይ የተመሠረተ የኃጢአት ጥላቻ ነበረው። ሕዝቡ በቅድስና መኖር እንዳለባቸው የወሰነ ሰው ነበር፤ ስለዚህ ወዲያውኑ እርምጃ ወሰደ፡፡ በመጀመሪያ፥ እንግዶች (ባዕዳን) የሆኑ ሰዎች በሙሉ ወደ ቤተ መቅደስ እንዳይመጡ አገለላቸው (ነህ. 13፡1-3)።

ሁለተኛ፥ የእግዚአብሔር ሕዝብ ጠላት የነበረውንና ካህኑ ኤልያሴብ በቤተ መቅደሱ አጠገብ አንደኛው ክፍል ውስጥ እንዲኖር የፈቀደለትን ጦቢያን አባረረ። ነህምያ የጦቢያ ክፋት ሕዝቡን እንዲበክል አልፈለገም፤ ስለዚህ የጦቢያ የሆኑትን ንብረቶች ሁሉ አውጥቶ በመንገድ ላይ በተናቸው። 

ሦስተኛ፥ ነህምያ ሕዝቡ አሥራት ለሌዋውያን መስጠት ማቆማቸውና በዚህም ምክንያት ሌዋውያን የአምልኮ ፕሮግራም የመምራት አገልግሎታቸውን አቋርጠው፥ ሥራ ፍለጋ በይሁዳ ሁሉ ለመበተን እንደተገደዱ ተገነዘበ። ነህምያ ሕዝቡ አሥራት እንዲሰጡና ሌዋውያንም አምልኮ ወደ መምራት አገልግሎታቸው እንዲመለሱ አደረገ።

አራተኛ፥ ነህምያ ሕዝቡ አናደርግም ብለው ቃል ከገቡት ነገሮች መካከል፥ በሰንበት የመሸጥና የመግዛት ነገር ሲለማመዱ ተመለከተ፤ ስለዚህ የከተማይቱ በሮች ዓርብ ማምሻውን ተዘግተው ሰንበት (ቅዳሜ) ካለቀ በኋላ ብቻ እንዲከፈቱ አዘዘ። ነጋዴዎቹንም ከእንግዲህ በሰንበት ቀን ቢመጡ እንደሚቀጡ በመንገር አስጠነቀቃቸው።(ማስታወሻ፡- ለአይሁድ ሰንበት የሚጀምረው ዓርብ ማምሻውን ከ12 ሰዓት በኋላ ሲሆን፥ የሚያበቃው ቅዳሜ ከ12 ሰዓት በኋላ ወደ ማታ ነው።)

አምስተኛ፥ ሕዝቡ ከአሕዛብ ጋር መጋባት ጀምረው ነበር። እንደምታስታውሰው፥ ይህንን አናደርግም ብለው ቃል ከገቡ ብዙ ዓመታት አላለፉም ነበር (ዕዝራ 10፡2፥ 10-14)። ነህምያ በታላቅ ቁጣ ሕዝቡን ተራገመ፤ ጠጉራቸውን ነጨ፤ ባዕዳን ሚስቶቻቸውንም እንዲያባርሩ አደረገ።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የምናደርጋቸውንና ከእነርሱ መንጻት የሚገባንን ተመሳሳይ ነገሮች ዘርዝር። ለ) የነህምያን ምሳሌነት በመከተል ቤተ ክርስቲያንህን እንዴት ልታነጻ ትችላለህ? ሐ) ከነህምያ ሕይወትና ለኃጢአት ከነበረው ጥላቻ የምንማረው ምንድን ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: