Site icon

አስቴር 7-12

የውይይት ጥያቄ፡ ምሳሌ 21፡1 አንብብ። ሀ) እግዚአብሔር በምድር መሪዎች ላይ ስላለው ቁጥጥር ይህ ጥቅስ ምን ያስተምረናል? ለ) ክርስቲያኖች ከመንግሥት ጋር በሚሠሩበት ጊዜ ይህ ነገር እንዴት ማበረታቻ ይሆናቸዋል? ሐ) ይህ ነገር ሲፈጸም እንዴት እንዳየህ ምሳሌዎችን ስጥ።

እግዚአብሔር ስለ ሕዝቡ ብሎ ሁልጊዜ የሚሠራ መሆኑን አይተናል። ተአምራትን ባናይም እንኳ እግዚአብሔር በሥራ ላይ አይደለም ማለት አይደለም። እግዚአብሔር ብዙ ጊዜ የሚሠራው ሕዝቡ እንኳ በማያውቁት መንገድ ነው። ክርስቲያኖች ግን ዕድል ወይም አጋጣሚ የሚባል ነገር እንደሌለ መገንዘብ አለባቸው። ይልቁንም ጸጋን የተሞላው ሰማያዊ አባታችን ለክብሩ፥ ለመንግሥቱና ለሕዝቡ ሲል ነገሮችን ሁሉ እየተቆጣጠረ ይሠራል። 

መጽሐፈ አስቴር፥ እግዚአብሔር በአስቴር ዘመን ይህንን ለአይሁድ እንዴት እንዳደረገላቸው የሚገልጥ ሥዕላዊ ታሪክ ነው። የእግዚአብሔር ጠላቶች፥ የእርሱን ሕዝብ አይሁድን ለማጥፋት ቢወስኑም እንኳ እግዚአብሔር እነርሱን ለማዳን በአንዲት ሴት በመጠቀም በጸጥታ ሠራ።

የውይይት ጥያቄ፥ አስቴር 7-12 አንብብ። ሀ) አስቴር ሕዝቧን ከጥፋት ያዳነችው እንዴት ነው? ለ) በዚህኛው የአስቴር ታሪክ ክፍል የእግዚአብሔር እጅ የታየው እንዴት ነው? ሐ) ከዚህ ታሪክ የምንማረው መንፈሳዊ ትምህርት ምንድን ነው?

አስቴር 1-6 እስራኤላውያን ራሳቸውን ያገኙበትን አደገኛ ሁኔታ የሚገልጥ ሲሆን፥ አስቴር 7-12 ግን እግዚአብሔር የሐማና የጠላቶቹን ዕቅድ ለማፈራረስ እንዴት እንደሠራና ሕዝቡን እንደጠበቀ ይገልጣል። የሚከተሉትን ትምህርቶች ተመልከት፡-

  1. አስቴር፥ እርስዋንና ሕዝቧን ያለ ምንም ምክንያት ሊገድል ማሰቡን በመናገር ሐማን ከሰሰችው። በውጤቱም ሐማ መርዶክዮስን ለመስቀል ባዘጋጀው ግንድ ላይ ተሰቀለ (መዝ. (28)፡1-5 ተመልከት)።
  2. ንጉሥ አርጤክስስ በመንግሥቱ ሁሉ አይሁድን ለመዋጋት በሚያስቡ (ወይም በሚሞክሩ) ጠላቶቻቸው ሁሉ ላይ የመስቀል ሥልጣን ለአይሁድ እንደተሰጣቸው የሚገልጥ ትእዛዝ አስተላለፈ። ንጉሡም መርዶክዮስን የቅርብ አማካሪው አደረገው። በአንድ ወቅት በቤተ መንግሥት የሐማ የነበረውን የክብር ስፍራ መርዶክዮስ ወሰደ። 
  3. አይሁድ በጠላታቸው በሐማ ላይ ስላገኙት ድል የፉሪምን በዓል አከበሩ። ፉሪም የሚለው ቃል «ፉር» ከሚለው የዕብራይስጥ ቃል የተገኘ ሲሆን፥ ትርጉሙም ዕጣ ማለት ነው። ይህም የሚያመለክተው ሐማና ንጉሡ አይሁድን ስለሚያጠፉበት ቀን ለመወሰን ያወጡትን ዕጣ ነው (አስቴር 3፡7)። እስራኤላውያንን ለማጥፋት ሐማ ዕጣ ቢጠቀምም እግዚአብሔር ግን ሁኔታዎችን በመቆጣጠር ዕጣው በእግዚአብሔር ሕዝብ ጠላቶች ላይ ወደቀና ብዙ ሺህ አሕዛብ ተገደሉ። አይሁድ ዛሬም ይህንን በዓል በታላቅ ደስታ ያከብሩታል። በዚህ በዓል ዕለት መጽሐፈ አስቴር ለቤተሰቡ አባላት በሙሉ ይነበባል። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version