ከመጽሐፈ ኢዮብ የምናገኛቸው ልዩ ትምህርቶች

1. የሰይጣን ሥራ፡- ቀደም ሲል በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ ሰይጣን በእባብ ተመስሉ ሔዋንን እንዳታለላትና ወደ ኃጢአት እንደመራት የሚያሳየውን የሰይጣንን ሥራ ተመልክተናል፤ ዳሩ ግን በዚያ ታሪክ ውስጥ አይሁድ ከምርኮ እስኪመለሱ ድረስ ስለ ሰይጣን የተገለጠው ነገር እጅግ አነስተኛ ነበር። በዘካርያስ መጽሐፍ ውስጥ አይሁድ ስለ ሰይጣን አካላዊ ህልውና የነበራቸው እውቀት እያደገ መምጣቱን መመልከት እንጀምራለን። በኢሳይያስ 14ና በሕዝቅኤል 28 ስለ አንድ ታላቅ የክፋት ኃይል የሚናገር ፍንጭ እንመለከታለን፤ ዳሩ ግን እነዚህ ጥቅሶች በግልጽ ወደ ሰይጣን አያመለክቱም። በመጽሐፈ ኢዮብ የዚህ የክፋት ኃይል ማንነት ተገልጾልናል። ከዚያም በኋላ በከፍተኛ ደረጃ በሚታወቅበት «ሰይጣን» በተባለ ስሙ ተጠርቶ እናገኛለን። ሰይጣን ማለት «ባላጋራ» ማለት ነው። ሰይጣን የእግዚአብሔርና የልጆቹ ባላጋራ ነው። ሰይጣን ከእግዚአብሔርና ከዕቅዱ በተቃራኒ የሚሠራ ነው፥ በተለይ ቅዱሳንን በእግዚአብሔር ፊት የሚከስ ሆኖ ተገልጾአል። 

2. የእግዚአብሔር ልጆች ጠበቃ አላቸው (ኢዮብ 5፡1፤ 9፡33፤ 16፡19-21)። ኢዮብ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ባያውቅም እንኳ እግዚአብሔርን ግን ያውቅ ነበር። ስለ እግዚአብሔር የነበረው እውቀት እግዚአብሔር ጠበቃው እንደሚሆንለት ዋስትና ሰጠው። ኢዮብ በሰማይ ስላለ የፍርድ ቤት ችሎት ያስብ ነበር። በዘላለማዊው ፈራጅ ፊት ጠበቃ ሆኖ ከማንኛውም ጥፋት ነፃ በማድረግ ጻድቅ መሆኑን እንደሚያረጋግጥለት እርግጠኛ ነበር። በአዲስ ኪዳን እውነተኛው ጠበቃ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ ግልጽ ሆኖአል (1ኛ ጢሞቴዎስ 2፡5 ተመልከት)። ፍጹም ሰውና ፍጹም አምላክ እንደመሆኑና የኃጢአታችንን ዋጋ በመስቀል ላይ በመሞት ሙሉ በሙሉ በመክፈሉ፥ ዘላለማዊ ዳኛ በሆነው በእግዚአብሔር ፊት ለመቆምና እኛን ለማጽደቅ የሚችል ኢየሱስ ብቻ ነው። እግዚአብሔር «በደለኞች አይደላችሁም» የሚለውን ቃል ስለ እኛ መናገሩ የሚረጋገጥልን ኢየሱስ በመስቀል ላይ በሠራው ሥራ ብቻ ሳይሆን፥ ጠበቃችን እንደ መሆኑ መጠን ያለማቋረጥ በሚሠራው ሥራ ጭምር ነው። ኢዮብ ስለ ጠበቃ ያቀረበው ጩኸት በኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት ተፈጽሟል። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ኢየሱስ ክርስቶስ ጠበቃችን መሆኑን መገንዘባችን ማበረታቻ የሚሆነን እንዴት ነው? ለ) በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ በምናልፍበት ጊዜ ኢዮብ በመከራ ውስጥ ሲያልፍ ካሳየው ዝንባሌ የምንማራቸው ነገሮች ምንድን ናቸው? ኢዮብ ከፍተኛ ጽናትን አሳይቷል። እንደ እውነቱ ኃጢአት እንደሠራና በኃጢአቱ ምክንያትም እንደተቀጣ ለወዳጆቹ ቢናገር እጅግ ይቀለው ነበር፤ ነገር ግን ኢዮብ ንጹሕ እንደሆነ ያውቅ ስለነበር ከወዳጆቹ ንትርክ ለመዳን ብሎ ለመዋሸት ፈቃደኛ አልሆነም። ዛሬም ቢሆን ራሳቸውን በሚገባ የሚያውቁ፡ በማንኛውም ሰው ፊት በማስመሰል የማይቆሙና እውነትን በግልጽ የሚናገሩ ወንዶችና ሴቶች ያስፈልጉናል።  

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “ከመጽሐፈ ኢዮብ የምናገኛቸው ልዩ ትምህርቶች”

Leave a Reply

%d bloggers like this: