እንደ አብዛኛዎቹ የትንቢት መጻሕፍት ሁሉ የትንቢተ ኢሳይያስንም አስተዋጽኦ ማዘጋጀት አስቸጋሪ ነው። ምክንያቱም አብዛኛዎቹ የትንቢተ ኢሳይያስ ክፍሎች ዝርዝር ጉዳዮችን ያላካተቱ ተከታታይ መልእክቶችና ትንቢተች ናቸው። ኢሳይያስ ከፍርድ መልእክት አጽናኝና ተስፋ ሰጭ ወደሆነ መልእክት፥ እንደገና ደግሞ ወደ ፍርድ መልእክት የሚመላለስ ይመስላል፡፡ ይህ ዑደት በመጽሐፉ ውስጥ በተደጋጋሚ ሲፈጸም የሚታይ ነው። ከዚህ ቀጥሉ ያለው ከመጽሐፉ አስተዋጽኦ ውስጥ አንዱ ሊሆን ይችላል።
የውይይት ጥያቄ፥ የሚከተለውን የትንቢተ ኢሳይያስ አስተዋጽኦ የመጽሐፉን ዋና ዋና ክፍሎችና በእያንዳንዱ ክፍል ውስጥ የሚገኙትን ዐበይት ትምህርቶች አጠቃላይ ገጽታ ለማግኘት በሚያስችል መንገድ አጥና።
ክፍል 1፡- በእስራኤል፥ በይሁዳና በአሕዛብ ሁሉ ላይ የመጣ የፍርድ መልእክት መጽሐፍ (ኢሳይያስ 1-39)
1. የትንቢተ ኢሳይያስ መግቢያ-እግዚአብሔር በሕዝቡ ላይ በሚደርሰው ነገርና በወደፊት ሁኔታቸው ሉዓላዊ ነው (ኢሳይያስ 1-6)፡-
ሀ. ይሁዳ ከእግዚአብሔር ጋር ያደረገችውን ቃል ኪዳን በማፍረሷ እንደተወቀሰች (ኢሳይያስ 1)፥
ለ. እግዚአብሔር ወደፊት የሚመሠርተው መንግሥት (ኢሳይያስ 2፡1-5)።
ሐ. እግዚአብሔር በይሁዳ ላይ ስለሚያመጣው ፍርድ (ኢሳይያስ 2፡6-4፡1)፥
መ. ስለ ይሁዳ የወደፊት ተሐድሶ (ኢሳይያስ 4፡2-6)፥
ሠ. እግዚአብሔር በይሁዳ ላይ የሰጠው ፍርድና የሚመጣው ምርኮ (ኢሳይያስ 5)፥
ረ. የኢሳይያስ ራእይና ለነቢይነት መጠራቱ (ኢሳይያስ 6)።
2. በአንድ ሕዝብ ላይ አገር አቀፍ የሆነ መከራና ችግር በሚደርስበት ጊዜ እግዚአብሔር ሉዓላዊ ነው-እስራኤልና ሶርያ ይሁዳን በወረሩበት ወቅት የተነገረ ትንቢት (ኢሳይያስ 7-12)፡-
ሀ. ይሁዳ በእስራኤልና በሶርያ እጅ እንደማትወድቅ በመግለጽ የተነገረ ትንቢት (ኢሳይያስ 7)፡
ለ. ስለ ኢሳይያስ ወንድ ልጆችና የዳዊት ልጅ ስለሆነው ስለ መሢሑ የተነገረ ትንቢት (ኢሳይያስ 8-9፡7)።
ሐ. የእግዚአብሔር ፍርድ በእስራኤል ላይ (ኢሳይያስ 9፡8-10፡4)፥
መ. የእግዚአብሔር ፍርድ በአሦር ላይ (ኢሳይያስ 10፡5-34)።
ሠ. መሢሑና የወደፊት መንግሥቱ (ኢሳይያስ 11-12)።
3. እግዚአብሔር በሕዝቦች ሁሉ ላይ ሉዓላዊ ነው-በተለያዩ ሕዝቦች ላይ የተነገሩ ትንቢቶች (ኢሳይያስ 13-23)፡-
ሀ. በአሦር ላይ (ኢሳይያስ 13፡1-14፡27)፥
ለ. በፍልስጥኤም ላይ (ኢሳይያስ 14፡28-32)፥
ሐ. በሞዓብ ላይ (ኢሳይያስ 15-16)።
መ. በደማስቆና በእስራኤል ላይ (ኢሳይያስ 17)፥
ሠ. በኢትዮጵያ ላይ (ኢሳይያስ 18)፥
ረ. በግብፅና በኢትዮጵያ ላይ (ኢሳይያስ 19-20)።
ሰ. በባቢሎን ላይ (ኢሳይያስ 21፡1-10)።
ሸ. በኤዶም ላይ (ኢሳይያስ 21፡11-12)።
ቀ. በዐረብ ላይ (ኢሳይያስ 21፡13-17)።
በ. በኢየሩሳሌም ላይ (ኢሳይያስ 22)፥
ተ. በጢሮስ ላይ (ኢሳይያስ 23)።
4. እግዚአብሔር በይሁዳ ሕዝቡ ላይ ሉዓላዊ ነው-ስለ ፍርድና ስለሚመጣው መንግሥት የተተነበዩ የተስፋ ቃላት (ኢሳይያስ 24-27)።
5. እግዚአብሔር በፍርድ ላይ ሉዓላዊ ነው-በእስራኤልና በአሦር ላይ የተነገሩ ስድስት የዋይታ ትንቢቶች (ኢሳይያስ 28-33)።
6. እግዚአብሔር ሉዓላዊ ነው-የፍርድ መልእክቶችና የበረከት ተስፋዎች (ኢሳይያስ 34-35)።
7. እግዚአብሔር በዓለም ላይ ባሉ ታላላቅ ኃያላን ላይ ሉዓላዊ ነው-እግዚአብሔር ነፃ እንደሚያወጣ የተነገረ ታሪክና ወደፊት ይሁዳ በባቢሎን እንደምትማረክ የተነገረ ትንቢት (ኢሳይያስ 36-39)።
ክፍል 2፡- የማጽናናት መጽሐፍ (ኢሳይያስ 40-66)
8. በአይሁድ ሕዝብ ነፃ መውጣትና መመለስ ላይ እግዚአብሔር ሉዓላዊ ነው (ኢሳይያስ 40-48)።
9. አገልጋይን ወደ ሕዝቡ በመላክ እግዚአብሔር ሉዓላዊ ነው (ኢሳይያስ 49-57)።
10. በመጨረሻዎቹ ዘመናት ጉዳይ፥ ሕዝቡን ነፃ በማውጣት፥ በክፉዎችና በኃጢአተኞች ላይ በመፍረድና ሊመጣ ባለው ዘላለማዊ መንግሥት ጉዳይ እግዚአብሔር ሉዓላዊ ነው (ኢሳይያስ 58-66)
የውይይት ጥያቄ፥ ከላይ በተሰጠው አስተዋጽኦ ላይ የተንጸባረቁ ትምህርቶች በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ የሚፈለጉባቸውን መንገዶች ዘርዝር።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)