በትንቢተ ኢሳይያስ ውስጥ የሚገኙ ዋና ዋና አሳቦች

ትንቢተ ኢሳይያስን በምታነብበት ጊዜ፥ የሚከተሉትን ዋና ዋና አሳቦች መመልከት ጠቃሚ ነው። እነዚህ ዐበይት ዋና አሳቦች ሌሎች ትንቢቶችና ትምህርቶች የተመሠረቱባቸው የመጽሐፉ የጀርባ አጥንት ተደርገው የሚታዩ ናቸው።

1. የእግዚአብሔር ባሕርይ፡- ትንቢተ ኢሳይያስ ከሌሎቹ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ይልቅ የእግዚአብሔርን ታላቅነት፥ በተፈጥሮ፥ በሕዝቦችና በመንግሥታት ላይ ያለውን የበላይ ተቆጣጣሪነትን የሚገልጽ መጽሐፍ ነው። ይህ ባሕርይ ታላቅነትና ግርማን፥ ፍቅርና ምሕረትን፥ ፍርድና ቍጣን፥ ይቅርታና ተሐድሶን የሚጨምር ነው። እግዚአብሔር በዚህ መጽሐፍ ውስጥ እንዴት እንደተገለጠ ተመልከት።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ክርስቲያኖች ስለ እግዚአብሔር ማንነት ግልጽና ትክክለኛ ግንዛቤ ሊኖራቸው የሚያስፈልገው ለምንድን ነው? ለ) ይህ ነገር እንዴት ሊያበረታታቸው ይችላል? ሐ) እግዚአብሔርን በትሕትና ለማገልገል ይህ ሊረዳቸው የሚችለው እንዴት ነው?

2. እግዚአብሔር የእስራኤል ቅዱስ ነው፡- ኢሳይያስ በመጽሐፉ እግዚአብሔርን ለመጥራት የተጠቀመባቸው የተለያዩ ስሞች ቢኖሩትም፥ አንድ ልዩ የሆነ ስም ግን ነበረው፤ ያም ስም «የእስራኤል ቅዱስ» የሚል ነው። በሌሉች ብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ አልፎ አልፎ ከመጠቀሱ በቀር፥ ይህ የእግዚአብሔር ስም የሚገኘው በትንቢተ ኢሳይያስ ውስጥ ብቻ ነው። ቅዱስ በሆነው በእግዚአብሔር ባሕርይ ላይ ያተኩራል፤ እንዲሁም እግዚአብሔር ቅዱስ ብሉ ቢጠራቸውም እንኳ ከሕዝቡ ኃጢአተኝነት ጋር በንጽጽር የቀረበ ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ 1ኛ ጴጥ. 1፡15-16 አንብብ። ከእግዚአብሔር ቅድስና ጋር ሲነጻጸር የክርስቲያን ኃላፊነት ምንድን ነው?

3. እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ያዋርዳል (ኢሳይያስ 2፡11-17)፡

በእዚህ ስፍራ ትዕቢተኞች የተባሉት ሀ) ለእግዚአብሔርና ለሕዝቡ ተቃራኒ ሆነው የቆሙ ሕዝቦች፥ ለ) ራሳቸውን በእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ ለእግዚአብሔር ለመታዘዝ ፈቃደኛ ያልሆኑ የይሁዳ ወይም የሌሎች ሕዝቦች ነገሥታት ወይም ሐ) በታዛዥነት ሕይወታቸውን እግዚአብሔርን ለመስጠት ፈቃደኞች ባለመሆን ትዕቢተኝነታቸውን የሚገልጡ ማንኛቸውም ተራ ሰዎች ሊሆኑ ይችላሉ። እግዚአብሔር ትዕቢትን ስለሚጠላ ይፈርድበታል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ትዕቢትን በእነዚህ ሦስት የሕይወት ክፍሎች ያየኸው እንዴት ነው? ለ) እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ሲያዋርድ ያየኸው እንዴት ነው? ሐ) ይህ በተለይ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እንዳይታበዩ ማስጠንቀቂያ መሆን ያለበት እንዴት ነው?

4. እግዚአብሔር እስራኤልን የሚቤዥ ነው፡- እግዚአብሔር አይሁድን በኃጢአታቸው ምክንያት ተማርከው እንዲሄዱና ለአሕዛብ መንግሥት ባሪያዎች እንዲሆኑ ቢያደርግም፥ የሚቤዣቸውም ራሱ እግዚአብሔር ነው (ኢሳይያስ 41፡14፤ 43፡14፤44፡6 ተመልከት)። 

5. እግዚአብሔር ባዕዳን መንግሥታትን ይቆጣጠራል፡- በትንቢተ ኢሳይያስ ውስጥ ያለማቋረጥ የምናየው እግዚአብሔር በአጠቃላይ የአሕዛብ ሁሉ ተቆጣጣሪ መሆኑን ነው። ሕዝቡን ለመቅጣት አሦራውያንን ያስነሣው እግዚአብሔር ነው። የይሁዳን ሕዝብ ለማጥፋት ባቢሎንን ያስነሣው እግዚአብሔር ነበር። ባቢሎንን ለማጥፋትና የይሁዳን ሕዝብ ወደ እስራኤል ለመመለስ የእግዚአብሔር «አገልጋይ» የሆነውን ቂሮስን የተጠቀመበት እግዚአብሔር ነበር። እግዚአብሔር አንድን ሕዝብ ከፍ ያደርጋል፤ ሌላውን ያዋርዳል። እግዚአብሔር በእርሱ ላይ በሚያምፁት አሕዛብ ሁሉ ላይ ይፈርድባቸዋል።

6. የእስራኤል ቅሬታዎች፡- ትንቢተ ኢሳይያስ ካተኮረባቸው ነገሮች አንዱ ቅሬታዎችን የሚመለከት ነው። በኤልያስ ዘመን ለበኣል ያልሰገዱ 7000 ሰዎች እንደነበሩ ሁሉ (1ኛ ነገሥት 19፡18)። እግዚአብሔር ምንጊዜም ለእርሱ ታማኞች የሆኑ ቅሬታዎች አሉት። እግዚአብሔር እነዚህን ቅሬታዎች ነፃ ለማውጣትና ለማዳን ደግሞም ወደ ይሁዳ ምድር ለመመለስ ቃል ገብቶላቸው ነበር። ኢሳይያስ ለእነዚህ ቅሬታዎች የሚጽፍላቸው የማበረታቻ መልእክት ታላቅ ጥፋት በሚሆንበት ጊዜ እንኳ ለእግዚአብሔር ታማኞች እንዲሆኑ የሚያሳስብ ነበር። በእምነታቸው ጸንተው ቢቆዩና ለእግዚአብሔር ቢታዘዙ ከእግዚአብሔር ዘንድ ሽልማትን ያገኛሉ።

7. ስለ እስራኤል ሕዝብ ተሐድሶ፡- እግዚአብሔር በእስራኤልና በይሁዳ ላይ ፍርድን እንደሚያመጣ አስቀድሞ የተናገረ ቢሆንም ከምርኮ እንደሚመልሳቸውም አስቀድሞ ተናግሮ ነበር። እግዚአብሔር አሁንም ቢሆን ለይሁዳና ለኢየሩሳሌም ዕቅድ ነበረው። 

8. በይሁዳ ላይ ገዥ የሚሆነው የመሚሑ መምጣት፡- በብሉይ ኪዳን ውስጥ ከሚገኙት መጻሕፍት ሁሉ በላቀ ሁኔታ ትንቢተ ኢሳይያስ በመሢሑ መምጣት ላይ ትኩረት ያደርጋል። መሢሑ ንጉሥ ሆኖ ሊገዛ ከዳዊት የዘር ግንድ ይመጣል። ከድንግል ይወለዳል፤ ነገር ግን አማኑኤል ይሆናል። በሰዎች መካከል በሥጋ የሚኖር በባሕሪው ግን እግዚአብሔር ማለት ነው። በቤተልሔም ተወልዶ፥ በገሊላ ያገለግላል። የገዛ ወገኖቹ ይገድሉታል፤ እርሱ ግን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋል። እነዚህ ስለ መሢሑ ከተነገሩ ትንቢቶች ጥቂቶቹ ናቸው። አዲስ ኪዳን ከማንኛውም የትንቢት መጻሕፍት ይልቅ ከትንቢተ ኢሳይያስ ይጠቅሳል።

9. የእግዚአብሔር አገልጋይ፡- በትንቢተ ኢሳይያስ ሁለተኛ ግማሽ ክፍል ካሉት ልዩ አሳቦች አንዱ «የአገልጋይ መዝሙራት» ወይም ልዩ ስለሆነው የእግዚአብሔር አገልጋይ የሚናገረው መዝሙር ነው (ኢሳይያስ 42፡1-7፤ 49፡1-9፤ 52፡13-53፡12፤ 61፡1-3)። እስራኤል የእግዚአብሔር አገልጋይ እንደሆነች የተጠቀሰ ቢሆንም፥ እነዚህ ክፍሎች የሚናገሩት ግን ስለ አንድ ልዩ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው። እስራኤል ፈቃዱን የምትፈጽም አገልጋዩ እንድትሆን እግዚአብሔር የመረጣት ቢሆንም፥ እርስዋ ግን አልቻለችም። ሆኖም እግዚአብሔር ፈቃዱን ሙሉ በሙሉ የሚፈጽምና ታዛዥ የሆነ ልዩ አገልጋይ ነበረው፤ እርሱም መሢሑ ነበር። ስለ እስራኤል ሕዝብ ኃጢአት የሚሞትና የሚፈውሳቸው ይህ መሢሕ ነው። ከአዲስ ኪዳን በግልጽ እንደምንረዳው፥ ይህ መሢሕ የእግዚአብሔርና የሰው ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ኢየሱስ አምላክ ቢሆንም እንኳ ትሑት ሆኖ የእግዚአብሔርና የሰው ዘር አገልጋይ ሆነ (ማርቆስ 10፡45 ተመልከት)። በትሕትናና በመታዘዝ እስራኤልና ክርስቲያኖች ከእግዚአብሔር ጋር፣ እንዲሁም እርስ በርሳቸው ሊኖራቸው የሚገባ ግንኙነት ምን መምሰል እንዳለበት ገለጠ።

የውይይት ጥያቄ፡ ሀ) አምላክ የሆነው ኢየሱስ፥ አገልጋይ መሆኑ የሚያስገርመው ለምንድን ነው? ለ) ኢየሱስ አገልጋያችን የሆነው በምን መንገድ ነው? ሐ) እንዴት የእግዚአብሔር አገልጋዮች መሆን እንደምንችል ግለጽ። መ) የሌሎች አገልጋዮች መሆን የምንችልባቸው መንገዶች የትኞቹ ናቸው? ምሳሌዎችን ስጥ። ሠ) የእግዚአብሔርና የሌሉች አገልጋዮች ለመሆን የሚፈቅዱ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ቁጥር ያነሰው ለምንድን ነው?

10. መሢሑ የሚመሠርተው መንግሥት፡- ትንቢተ ኢሳይያስ መሢሑ ስለሚመሠርተው ዘለዓለማዊ መንግሥት ብዙ ሥዕላዊ መግለጫዎችን ይሰጣል። የዚህ መንግሥት ማዕከል ኢየሩሳሌም ትሆናለች። በዚህም ሰዎች ሁሉ አሕዛብም ሳይቀሩ መጥተው ለማምለክ በሚችሉበት ሁኔታ ሰላምና ብልጽግና ይሆናል። እግዚአብሔር፥ በዚያ የዳዊት ዘር በሆነው በልጁ በኩል ይገዛል (ኢሳይያስ 24፡23፣ 33፡22፤ 43፡15፤ 44፡6 ተመልከት)። ምንም እንኳ ምሁራን ከእነዚህ ትንቢቶች መካከል ቀጥተኛ የሆኑትና ተምሳሌታዊ በሆነ መንገድ የቀረቡት ምን ያህሉ እንደሆኑና ስለ አፈጻጸማቸው የማይስማሙ ቢሆንም፥ እነዚህ ትንቢቶች እግዚአብሔር በዘመኑ ፍጻሜ ስለሚመሠርተው የተከበረ መንግሥት እጅግ ውብ የሆኑ መግለጫዎችን የሚሰጡ ናቸው።

የውይይት ጥያቄ፥ እግዚአብሔር ስለ እነዚህ 10 ትምህርቶች ምን እንደሚል መረዳት ለክርስቲያኖች የሚጠቅመው ለምንድን ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “በትንቢተ ኢሳይያስ ውስጥ የሚገኙ ዋና ዋና አሳቦች”

Leave a Reply

%d bloggers like this: