ኢሳይያስ 40-49

የትንቢተ ኢሳይያስ ሁለተኛ ግማሽ ክፍል ለብዙ ክርስቲያኖች እጅግ ተወዳጅ ከሆኑት ቅዱሳት መጻሕፍት ክፍል መካከል የሚመደብ ነው። ስለ ፍርድ የሚናገሩት ባለፉት መልእክቶች አብቅተዋል። ኢየሩሳሌምን የሚያጠፋው የባቢሎን ፍርድ በእርግጥ የሚፈጸም መሆኑን ኢሳይያስ አውቋል፤ ስለዚህ ምርኮው እንደተፈጸመ አድርጎ በመቍጠር ይጽፋል። ራሳቸው በምርኮ ውስጥ የሚገኙ ሰዎችን በሚያጽናና መንገድ ይጽፋል።

ኢሳይያስ ሕዝቡን በሦስት መንገዶች ለማበረታታት ይፈልጋል፡-

በመጀመሪያ፥ የእግዚአብሔርን ታላቅነትና እግዚአብሔር በአሕዛብ በምድር ነገሥታት፥ በአሕዛብ አማልክትና በሕዝቦቹ ሕይወት ውስጥ በሚፈጸሙ ድርጊቶች ሁሉ ላይ ያለውን ሉዓላዊ ሥልጣን ያለማቋረጥ በማመልከት ያበረታታቸዋል።

ሁለተኛ፡ ኢሳይያስ በምርኮ አገር ያሉ አይሁድ ወደገዛ ምድራቸው እንደሚመለሱ በማመልከት ያበረታታቸዋል። እግዚአብሔር ያኔም ቢሆን ለይሁዳ ሕዝብ ዓላማ ነበረው፤ ስለዚህ የአይሁድ ሕዝብ በሙሉ እንዲጠፉ አይፈቅድም። ሁልጊዜ ለእግዚአብሔር ታማኝ የሆኑ ቅሬታዎች ይኖራሉ። እግዚአብሔርም ከእነዚህ ቅሬታዎች ጋር ይሠራል፤ ይጠብቃቸዋል፤ እንዲሁም ወደ ምድራቸው ይመራቸዋል።

ሦስተኛ፥ ሊመጣ ወዳለው «የእግዚአብሔር አገልጋይ» በማመልከት ያበረታታቸዋል። በዚህ የትንቢተ ኢሳይያስ የመጨረሻ ክፍል ሊመጣ ወዳለው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያመለክቱ በርካታ ትንቢቶች ይገኛሉ። የእግዚአብሔር ሌላዋ አገልጋይ ከሆነችው ከእስራኤል በተቃራኒ፥ ይህ እውነተኛ አገልጋይ በእግዚአብሔር መንፈስ ኃይል ይመጣል፤ ጽድቅን ያደርጋል፤ ሕዝቡን ነፃ ያወጣል ስለ ኃጢአታቸውም ይሞታል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እነዚህ ከላይ የተመለከትናቸው ሦስት እውነቶች በዚህ ዘመን ላለን ክርስቲያኖች ማበረታቻ የሚሆኑት እንዴት ነው? ለ) ከእነዚህ ሦስት ርእሶች፥ በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ የሚገኙትን ሰዎች ለማበረታታት መልእክት ልታቀርብ የምትችልባቸውን መንገዶች ዘርዝር። 

የውይይት ጥያቄ፥ ኢሳይያስ 40-49 አንብብ። ሀ) በእነዚህ ቍጥሮች ውስጥ የእግዚአብሔር ታላቅነት የታየባቸውን የተለያዩ መንገዶች ዘርዝር። ለ) በእነዚህ ቍጥሮች ውስጥ እግዚአብሔር በምርኮ ላይ ላሉት ሕዝቡ የሰጣቸውን የተለያዩ የማበረታቻ ተስፋዎች ዘርዝር። ሐ) በእነዚህ ምዕራፎች ውስጥ ስለሚመጣው «የእግዚአብሔር አገልጋይ» የተጠቀሱትን የተለያዩ እውነቶች ዘርዝር።

በእነዚህ ምዕራፎች ውስጥ ያለማቋረጥ የምናያቸው ሁለት ዐበይት አሳቦች አሉ። በመጀመሪያ፥ እግዚአብሔርን ለማወቅ በሚመለከት ዋና አሳብ እናገኛለን። ዳንኤል 11፡32 እንዲህ ይላል፡- «…ነገር ግን አምላካቸውን የሚያውቁ ሕዝብ ይበረታሉ፥ ያደርጋሉም» (ሐሰተኛ ክርስቶስን ይቃወማሉ)። እኛ ክርስቲያኖች በታላቅ መከራና ችግር በተሞላችው በዚህች ዓለም ውስጥ በሙሉ ልብነትና በደስታ ልንመላለስ የምንችለው እግዚአብሔር ማን እንደሆነ፥ ምን እንደሚመስል፥ ምን እንደሚፈልግና የሰጠን ቃል ኪዳን ምን እንደሆነ በምናውቅበት ጊዜ ነው። ችግሩ ግን እግዚአብሔር ማን እንደሆነ፥ ምን ያህል ታላቅ እንደሆነና ምን ያህል እንደሚወደን ግልጽ የሆነ መረዳት ያላቸው ጥቂት ክርስቲያኖች ብቻ መሆናቸው ነው። እነዚህ እውነቶች ይበልጥ ግልጽ በሆኑልን ቍጥር፥ የምንቀበለው መጽናናትና መበረታታትም እየጨመረ ይሄዳል። ኢሳይያስ በምርኮ የነበሩት እስራኤላውያን ዓይኖቻቸውን ወደ እግዚአብሔር እንዲመልሱ ያበረታታቸዋል። እግዚአብሔር በፍጥረታት፥ በአሕዛብ፥ በነገሥታት፥ በአሕዛብ የውሸት አማልክት ላይ እንኳ ታላቅ እንደሆነ ይነግራቸዋል። እግዚአብሔር ለእነርሱ ያለውን ፍቅርና የወደፊት ዓላማ ይነግራቸዋል። ተስፋ በምንቈርጥበት በማንኛውም ጊዜ ወደ ትንቢተ ኢሳይያስ ሁለተኛ ክፍል ብንመለስና ትኩረታችንን በእግዚአብሔር ላይ ብናደርግ እንጽናናለን፤ ብርታትንም እናገኛለን።

ሁለተኛው ዋና አሳብ፥ «የእግዚአብሔር አገልጋይ» የሚለው ነው። በክፍሉ የተጠቀሱ ሁለት የተለያዩ አገልጋዮች አሉ፡-

1. የእግዚአብሔር አገልጋይ የሆነው የእስራኤል ሕዝብ (ኢሳይያስ 41:8-10)፡- የእግዚአብሔር አገልጋይ የሆነችው እስራኤል ብዙ ጊዜ ብትወድቅም፥ እግዚአብሔር ግን አልተዋትም። ይልቁንም እግዚአብሔር በምድር ላይ ከሚገኙ አሕዛብ ሁሉ መርጦ እስራኤልን ጠራት፤ ከእርሷ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ፤ ምንጊዜም እንደማይተዋት ተስፋ ሰጣት። እግዚአብሔር እስራኤልን ይጠብቃታል፤ ይመራታል፤ የሚያስፈልጋትን ሁሉ ያደርግላታል። ወደ ቀድሞ ክብሯም ይመልሳታል። ቂሮስ የተባለ ሌላ አገልጋዩን በማስነሣት፥ ሕዝቡን ወደ ነፃነቱ ይመራዋል። እንደ ቤልና ኔቦ ያሉትን የባቢሎናውያን አማልክትና ባቢሎናውያንን ይደመስሳል። 

2. የእግዚአብሔር አገልጋይ የተባለው ሊመጣ ያለው የእስራኤል መሪ፡- ይህ አሳብ በቀሪው ኢሳይያስ ክፍል ውስጥ በሙሉ በመቀጠል የሚገኝ ነው (ኢሳይያስ 42፡1-7፤ 49፡1-7፤ 50፡4-9፤ 52፡13-53፡12)። ይህ እንደ ልቡ የሆነው የእግዚአብሔር አገልጋይ በመንፈስ ቅዱስ የሚሞላና በጽድቅ የሚነግሥ ነው። የዕውሮችን ዓይን በማብራትና ምርኮኞችን ነፃ በማውጣት፥ ለአሕዛብ ብርሃን ይሆናል። ከእግዚአብሔር የተማረና ሌሎችንም የሚያስተምር ይሆናል። በዚህም ዓይነት ለደከሙት ብርታትን ይሰጣቸዋል። ቤሌላ በኩል ደግሞ ሰዎች ያሳድዱታል ይገድሉታልም። በዚህ መልኩ ደግሞ ለብዙዎች ደኅንነትን ያመጣል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ለእግዚአብሔር እንደ ልቡ ስልሆነው አገልጋይ የተነገሩትን እነዚህን እውነቶች ኢየሱስ ክርስቶስ የሚፈጽመው እንዴት ነው? ) እኛስ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር እንደ ልቡ አገልጋይ እንደሆነው እንዴት እንሆናለን? ሐ) እኛም የእግዚአብሔር አገልጋዮች መሆን አለብን (2ኛ ጢሞቴዎስ 2፡24 ተመልከት)። ይህ ማለት ምን ማለት ነው? ይህ የዕለት እርምጃችንን የሚለውጠው እንዴት ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: