የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ክርስቲያኖች በመከራ ውስጥ በሚሆኑበት ጊዜ ስለ ዘላለማዊ መንግሥት መማር የሚያስፈልጋቸው ለምን ይመስልሃል? ለ) እግዚአብሔር ስለ መጨረሻው ዘመን ያለውን ዕቅድ የቤተ ክርስቲያንህ አባሎች ምን ያህል ተረድተውታል ብለህ ታስባለህ? ሐ) ስለ መጨረሻው ዘመን በተሻለ ሁኔታ ለማስተማር ምን ማድረግ ትችላለህ?
ክርስቲያኖች አስቸጋሪና አስጨናቂ በሆነ ሁኔታ ውስጥ በሚገኙበት ጊዜ እግዚአብሔር ስለ መጨረሻው ዘመን ያለውን ዕቅድ መረዳት ይጠቅማቸዋል። የምንወዳቸው በሞት ሲለዩን፥ በስደት ጊዜ ወይም ድርቅና ራብ ሲኖር እግዚአብሔር በመጨረሻው ዘመን ምን ዕቅድ እንዳለው መረዳት አስፈላጊ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ አንድ ቀን በጽድቅና በእውነተኛ ፍርድ በእኛ ላይ እንደሚነግሥ ማስታወስ አስፈላጊ ነው። በዚያ ድህነት፥ ሞት፣ ጦርነትና በሽታ አይኖርም። ክፉዎች ሁሉ ይደመሰሳሉ፤ የነገድና የጎሳ ጦርነትም ይቆማል። በመጀመሪያው ሰው በኃጢአት መውደቅ ምክንያት የተደመሰሰው ፍጥረት በአዲስ ሰማይና በአዲስ ምድር ይተካል። ዓይኖቻችንና አስተሳሰባችንን በእነዚህ ነገሮች ላይ ካደረግን፥ አስቸጋሪ በሆኑት በእነዚህ ጊዜያት እንኳ በታላቅ ደስታ ልንኖር እንችላለን። ጳውሎስ እንዳለው፡- «ስለዚህ አንታክትም፥ ነገር ግን የውጪው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል። የማይታየውን እንጂ የሚታየውን ባንመለከት፥ ቀላል የሆነ የጊዜው መከራችን የክብርን የዘላለም ብዛት ከሁሉ መጠን ይልቅ ያደርግልናልና የሚታየው የጊዜው ነውና፥ የማይታየው ግን የዘላለም ነው» (2ኛ ቆሮንቶስ 4፡ 16-18)።
ትንቢተ ኢሳይያስ ስለ መጨረሻው ዘመንና እግዚአብሔር ሊመሠርተው ስላቀደው ዘላለማዊ መንግሥት ብዙ የሚናገረው ነገር አለው። በእዚያ ስለሚኖረው ሰላምና ደስታ የሚናገሩ ብዙ ምሳሌዎችን ይጠቀማል። ከእነዚህ ምሳሌዎች አብዛኛዎቹ በዮሐንስ ራእይ ውስጥ ይገኛሉ። ክርስቲያኖች ስለ መጨረሻዎቹ ዘመናት የሚናገሩትን እነዚህን ምንባቦች በተለያየ መንገድ ቢተረጕሟቸውም እንኳ እግዚአብሔር አንድ ቀን በፍጹም በላይነት እንደሚነግሥና ኃዘንና ጦርነት፥ ኃጢአትም ፍጹም እንደሚደመሰሱ ይስማማሉ።
የውይይት ጥያቄ፥ ኢሳይያስ 50-66 አንብብ። ሀ) ስለ መጨረሻዎቹ ጊዜያት የሚናገሩ ናቸው ብለህ የምታስባቸውን በዚህ ክፍል የሚገኙ የተለያዩ ትንቢቶችን ጥቀስ። ለ) ስለዚያ ዘመን ለእስራኤል ሕዝብ በዚህ ክፍል የተሰጠው ቃል ኪዳን ምንድን ነው? ሐ) ክርስቲያን እንደመሆንህ መጠን በአስቸጋሪና በአስጨናቂ ጊዜ እነዚህ ትንቢቶች መጽናናት የሚሰጡህ እንዴት ነው? መ) «ስለ እግዚአብሔር አገልጋይ» በዚህ ክፍል የተነገሩ ትንቢቶች የትኞቹ ናቸው?
በዚህኛው የኢሳይያስ መጽሐፍ ክፍል ውስጥ አራት ዋና ዋና ርእሶች ይገኛሉ፡-
1. ይህ ክፍል በዘመኑ መጨረሻ ስለሚሆኑ ነገሮች እግዚአብሔር በሰጣቸው ታላላቅ ተስፋዎች የተሞላ ነው። ስለ እስራኤል ሕዝብ መዳንና ስለ አይሁድ እግዚአብሔርን ማምለክ የተሰጡ ተስፋዎች አሉ፤ ስለ አሕዛብ መዳን የተሰጡ ተስፋዎችም አሉ። ስለ አዲስ ሰማይና ምድር የተሰጡ ተስፋዎች አሉ፤ ክፉዎች እንደሚፈረድባቸው የተነገረ የፍርድ ተስፋም አለ።
2. የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት፥ በጽድቅ የሚኖረው ሊመጣ ያለው «የእግዚአብሔር አገልጋይ» ስለ ዓለም ኃጢአት ብሉ ማንም ያልተቀበለውን መከራ ይቀበላል (50፡4-9፤ 52፡13-53፡12)።
3. ለተጠሙና ኃጢአታቸው ይቅር እንዲባልላቸውና ከእግዚአብሔር ጋር እውነተኛ ግንኙነት ማድረግ ለሚፈልጉ ሁሉ የተደረገ የደኅንነት ጥሪ እናገኛለን (ኢሳይያስ 55)።
4. ለእግዚአብሔር የሚቀርብ እውነተኛ አምልኮ ባሕርይና ከእግዚአብሔር እውነተኛ በረከትን የመቀበያ መንገድ (ኢሳይያስ 58)፡- እግዚአብሔርን ማምለክ በቅድሚያ በከንፈሮቻችን በመዘመርና በመጸለይ የምንፈጽመው ተግባር አይደለም፤ ወይም ደግሞ በየዕለተ እሑድ በቤተ ክርስቲያን በመገኘት የምንፈጽመው ሥርዓት አይደለም። ይልቁንም እውነተኛ አምልኮ በእግዚአብሔር ፊት ከሚደረጉ ትክክለኛ ተግባራት የሚፈልቅ ነገር ነው። እውነተኛ አምልኮ ለጎረቤቶቻችን ቅንና አድልዎ የሌለበትን ተግባር ስንፈጽምና በአካባቢያችን ለሚገኙ ድሆች ርኅራኄንና ልግሥናን ስናሳይ ነው። ሌሎችን ለማገልገል ራሳችንን ስንሰጥ እግዚአብሔር ደግሞ በተራው በመንፈሳዊ ብርሃን ይባርከናል፤ ይመራናል፤ የሚያስፈልጉንም ነገሮች ሁሉ ይሰጠናል።
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔርን እያመለክህ የምትኖርባቸውን መንገዶች ግለጽ። ለ) ለጎረቤቶችህ ቅን ፍርድን እንዴት እንደምታሳይ የሚያስረዱ መግለጫዎችን ስጥ። ሐ) ባለህበት ኅብረተሰብ ውስጥ የሚገኙትን ድሆች ለመርዳት የጣርህባቸውን መንገዶች ግለጽ። መ) የዚህ ዓይነቱ ሕይወት በረከትን ያመጣልህና ለእግዚአብሔር ያለህን አምልኮ በጥልቀት ያሳደገው እንዴት ነው? ሠ) እግዚአብሔርን በእውነተኛ አምልኮ ታከብረው ዘንድ በዚህ ረገድ መሻሻል የምትችልባቸው መንገዶች ምንድን ናቸው?
የውይይት ጥያቄ፥ እግዚአብሔር ከእነርሱ ምን እንደሚፈልግ የቤተ ክርስቲያንህን ሰዎች ለማስተማር በትንቢተ ኢሳይያስ እውነቶች እንዴት ልትጠቀም ትችላለህ?
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)