1. ለቃል ኪዳኑ ሕግ መታዘዝ በማይኖርበት ጊዜ ከእግዚአብሔር ጋር የገባነውን ቃል ኪዳን አንፈጽምም። ዳሩ ግን የገባነውን ቃል ኪዳን የምንፈጽመው መታዘዛችን ከንጹሕ ልብና ከትክክለኛ ዝንባሌ ሲሆን ነው። ለእግዚአብሔር የሚቀርብ እውነተኛ አምልኮ ትክክለኛ ድርጊቶችን (ተገቢ የሆኑ ሥርዓቶች) የሚያካትት ብቻ መሆን የለበትም። ነገር ግን ለእግዚአብሔር ከሚገዛ ልብ የሚመነጭ፥ ለእግዚአብሔር ሕግ የሚታዘዝ፥ ከኃጢአት የነጻ፥ ከቤተሰብና ከጎረቤቶች ጋር ትክክለኛ በሆነ ግንኙነት መኖርን ጭምር የሚያጠቃልል ነው።
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ሰዎች እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ ሳይሆን፥ ከአምልኮ ሥርዓት አንጻር ብቻ አምልኮአቸውን ሊያቀርቡ የሚችሉባቸውን ሁኔታዎች ግለጽ። ለ) ይህን ዝንባሌ ለማረም ምን ማድረግ ትችላለህ?
2. ጋብቻና ፍቺ (ሚልክያስ 2፡10-16)፡- ከሚስቶቻችን ወይም ከባሎቻችን ጋር በትክክለኛ ግንኙነት ውስጥ ካልሆንን ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ በሆነ ግንኙነት ልንኖር አንችልም። ሚልክያስ ስለ ጋብቻ ሁለት ዐበይት እውነቶችን ያስተምረናል፡-
ሀ) አንድ ሰው ማንን እንደሚያገባ ወይም ሴት ከሆነች ማንን እንደምታገባ ጠንቅቆ መወሰን አለበት ወይም አለባት። ኢየሱስ ክርስቶስን ለመከተል ካደረግነው ውሳኔ ቀጥሎ ያለን ከፍተኛ ውሳኔ ማንን እንደምናገባ መወሰን ነው። አንድን ሰው የማያምን ወይም ሥጋዊ ክርስቲያን ብቻ መሆኑን እያወቅን ለቤተሰብ ውርስ፥ ለመልክ፥ ለሀብት ስንል ብናገባ እጅግ አስቸጋሪና ከባድ በሆነ ሕይወት ውስጥ እናልፋለን። ዘይትና ውኃ ሊቀላቀሉ እንደማይችሉ ወይም ብርሃን ከጨለማ ጋር ሊስማማ እንደማይችል ሁሉ በዚህ ዓይነቱ ጋብቻ ውስጥ በፍጹም ስምምነት ሊኖር አይችልም (2ኛ ቆሮንቶስ 6፡14-16 ተመልከት)። በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ጋር የነበረን ግንኙነት ይለወጥና እግዚአብሔርን በምንፈልገው መንገድ ሳናገለግለው እንቀራለን። እግዚአብሔርን ሙሉ በሙሉ ሊያከብር በማይችል ቤተሰብ ውስጥ ስለሚያድጉ ጉዳቱ ለልጆቻችንም ይተርፋል። የእግዚአብሔር ቃል ግልጽ ነው፡- የማያምን ሰው ልናገባ አይገባም። ሚስትን ወይም ባልን ለመምረጥ ዋናው መመዘኛ መንፈሳዊ ሕይወታቸው ነው። ሥጋዊ የሆነ ክርስቲያን ብናገባ የሚያጋጥመን ችግር የማያምን ሰው በማግባት ከሚገጥመን ችግር የተለየ አይደለም። ዳሩ ግን እንደ እኛው እግዚአብሔርን ለማገልገልና ለመታዘዝ ጥማት ያለውን ሰው ካገባን፥ የቤተሰቡ ውርስ ወይም ውበት ወይም ሀብት ምንም ዓይነት ቢሆን በትዳራችን ውስጥ ስምምነት፥ ሰላምና ፍቅር ይኖራል።
ለ. አንድ ሰው ያገባውን ሰው መፍታት የለበትም። የሚያሳዝነው ነገር አይሁዶች ፍቺ ምንም ችግር የሚያስከትል አይመስላቸውም ነበር። እንዲያውም ኢየሱስ በኖረበት ዘመን አንዲት ሴት እንጀራ ወይም ወጥ ብታሳርር ወይም ጥሩ ምግብ ለማዘጋጀት ባትችል፥ ባሏ ሊፈታት ይችል ነበር። ፍቺ በሚፈልጉበት ጊዜ ሁሉ በዘዳግም 24፡1-4 የሚገኘውን ጥቅስ እንደ ይለፍ ፈቃድ አድርገው ይጠቀሙበት ነበር። ለእስራኤላውያን ፍቺ የሚፈቀደው በሕይወታቸው ውስጥ ባለ ኃጢአት ምክንያት ብቻ ነበር (ማቴዎስ 19፡8)። እግዚአብሔር የደገፈው አማራጭ አልነበረም። ጋብቻ ሴትና ወንድ በእግዚአብሔር ፊት የሚገቡት የተቀደሰ ቃል ኪዳን ነው። ይህም እግዚአብሔር የሚያከብረውና የሚባርከው ነው። ጋብቻ ማለት ፍጹም መጣመርና እግዚአብሔርን የሚፈሩ ልጆችን ማፍራት ማለት ነው። ሚልክያስ ሚስትን «ባልንጀራ» ብሎ ይጠራታል (ሚልክያስ 2፡14)። ይህንን አሳብ የሚገልጠው የዕብራይስጡ ቃል ሁለት እንጨቶች ሊለያዩ በማይችሉበት መንገድ በምስማር ማጣበቅን የሚያመለክት ነው። የእግዚአብሔር ፍላጎት ጋብቻን በምንመሠርትበት ጊዜ ከትዳር ጓደኛችን ጋር በአካል፥ በስሜትና በመንፈስ አንድ እንድንሆን ነው። ፍላጎቶቻችን አንድ ይሆናሉ። ዕቅዶቻችን አንድ ይሆናሉ። ኑሮአችን ፍጹም በሆነ መግባባት፥ በስምምነትና በፍቅር የተመሠረተ ይሆናል። ባል ለሚስቱ ምን ማድረግ፥ ምን ማመን ወይም ምን ማቀድ እንዳለባት ያዛታል ማለት አይደለም። በአንድነትና በኅብረት ይሠራሉ። የእስራኤልና የቤተ ክርስቲያን ባል በሆነው በእግዚአብሔርና ሚስት በሆነችው በእስራኤል ወይም በቤተ ክርስቲያን መካከል ያለው ግንኙነት ተምሳሌታዊ በሆነ መንገድ በሙላት ሊፈጸም የሚችለው የዚህ ዓይነቱ ኅብረትና ግንኙነት በተገቢው ሁኔታ ሲኖር ብቻ ነው (ኤርምያስ 2፡1-3፤ 31፡32፤ ሕዝቅኤል 16፤ ሆሴዕ 2፡1-9። እስራኤልና እግዚአብሔር የሚስትና የባል ግንኙነት እንዳላቸው የሚያሳዩ ጥቅሶች ስለሆኑ ተመልከታቸው)። አዲስ ኪዳን ፍቺ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንዳልሆነ ያስተምረናል (ማቴዎስ 5፡31-32፤ 19፡1-10፤ ማርቆስ 10፡1-10፤ ሮሜ 7፡13፤ 1ኛ ቆሮንቶስ 7፡10-16፥ 39)።
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ብዙ ክርስቲያኖች ሚስት ወይም ባል በሚመርጡበት ጊዜ የተሳሳተ መመዘኛ የሚጠቀሙት እንዴት ነው? ለ) ወንድ ወይም ሴት የትዳር ጓደኛ በሚመርጡበት ጊዜ ሊጠቀሙበት የሚገባ አንዳንድ መመዘኛዎችን ዘርዝር። ሐ) ከላይ የጠቀስነው እግዚአብሔር ለጋብቻ ያለው ዓላማ የሚፈጸመው በጥቂት ክርስቲያናዊ ጋብቻዎች ብቻ የሚሆነው ለምን ይመስልሃል?
3. ነቢዩ ኤልያስ (ሚልክያስ 4፡5-6)፡- ትንቢተ ሚልክያስ የሚጠቃለለው የነቢዩ ኤልያስን መምጣት እንዲጠባበቁ ለእስራኤል ሕዝብ በመንገር ነው። የዚህ ነቢይ መምጣት «የጌታን ቀን» የሚቀድም ሲሆን፥ የልጆችን ልብ ወደ አባቶች ይመልሳል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ኤልያስ የእግዚአብሔር ነቢይ ማለት ምን ማለት እንደሆነ የሚገልጽና ከሌሉች ነቢያት መካከል አብዛኛዎቹ የተከተሉት ዐቢይ ምሳሌ ነበር። ምክንያቱም፡-
ሀ) ኤልያስ የሃይማኖትና የፖለቲካ መሪዎችን በድፍረት በመቃወም፥ ከአባቶቻቸው እምነት ዞር በማለታቸው፥ በሥነ ምግባር ጉድለታቸውና ማኅበራዊ ፍትሕን በማዛባት ኃጢአታቸው ወቅሶአቸዋል።
ለ) ኤልያስ ንስሐ የመግባትን አስፈላጊነት፥ ይህ ካልሆነ ግን ሰው የእግዚአብሔር ፍርድ እንደሚጠብቀው በግልጽ አስተምሯል።
ሐ) የኤልያስ መልእክቶች እውነትነት በተአምራት የተረጋገጠ ነበር።
መ) ኤልያስ ከሃይማኖት መሪዎች አንዱ አልነበረም፤ ዳሩ ግን ከተመሠረተው ሃይማኖታዊ መዋቅር ውጭ ሆኖ ሕዝቡ ወደ እውነተኛ ሃይማኖት እንዲመለሱ ለማድረግ ሠራ። ኢየሱስ በተራራ ላይ በተለወጠ ጊዜ ከሙሴና ከኤልያስ ጋር ተገናኝቶ ነበር (ማቴዎስ 17፡1-8)። ሙሴ ሕግን፥ ኤልያስ ደግሞ ነቢያትን የሚወክሉ ሲሆን፥ ሁለቱም የመሢሑን መምጣት የሚያመለክቱ ነበሩ። የእነርሱ መገለጥ ኢየሱስ ከብዙ መቶ ዓመታት በፊት የነበሩት የሕግና የነቢያት ፍጻሜ መሆኑን ማሳየት ነበር።
ሚልክያስ በዚህ ስፍራ የተናገረው፥ አንድ ቀን ኤልያስን የሚመስል ሰው እንደሚመጣ ነው። የእርሱ መምጣት ከመጨረሻዎቹ ቀናትና ከመሢሑ መምጣት በፊት ይሆናል።
ሚልክያስ ይኖር በነበረበትና መጥምቁ ዮሐንስ በተነሣበት ዘመን መካከል በነበሩት 400 ዓመታት ውስጥ አይሁድ ስለዚህ ኤልያስ የነበራቸው ወግ ዕድገት እያሳየ መጥቶ ነበር። ይህ የኤልያስ ተምሳሌት ይሁን ወይም የኤልያስ ከሞት ተነሥቶ መምጣት የሚያውቁት ነገር አልነበረም። መጥምቁ ዮሐንስ በመጣ ጊዜ በአለባበስና በመልእክቱ እነርሱ የሚጠብቁትን ኤልያስ ይመስል ነበር። ብዙ ሕዝብ ወደ መጥምቁ ዮሐንስ የመጡበትና በእርሱ ያመኑበት አንዱ ምክንያት ይህ ነበር። በኋላ ጌታ ኢየሱስ መጥምቁ ዮሐንስ ይህን ትንቢት እንደፈጸመ ተናገረ (ማቴዎስ 11፡7-15)።
ብዙ ምሁራን ከዘመናት መጨረሻ ጥቂት ቀደም ብሎ የሚመጣ ሌላ “ኤልያስ” አለ ብለው ያስባሉ። ይህ ሰው ከዘመኑ ፍጻሜ በፊት ሕዝቡን ለንስሐ የሚጋብዝ የመጨረሻ መልእክተኛ ይሆናል። በራእይ 11፡1-12 ከምናያቸው ሁለት ነቢያት አንዱ ኤልያስን የሚመስል ነቢይ ነው ብለው ያስባሉ።
የውይይት ጥያቄ፥ ክርስቲያኖች እነዚህን እውነቶች ሊያውቋቸውና ሊታዘዟቸው አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድን ነው?
የውይይት ጥያቄ፥ ሚልክያስ 1-4 አንብብ። ሀ) አይሁድ ለእግዚአብሔር ያቀረቧቸውን የተለያዩ ጥያቄዎች ዘርዝር። ለ) እግዚአብሔር እነዚህን ጥያቄዎች የመለሰላቸው እንዴት ነበር? ሐ) ከእነዚህ ጥያቄዎችና ትምህርቶች አብዛኛዎቹ በዚህ ዘመን ላሉ ክርስቲያኖች ጠቃሚ የሚሆኑት እንዴት ነው?
እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች ከሰጣቸው ኃላፊነቶች አንዱ፥ ለእግዚአብሔር ሕዝብ «ነቢይ» የመሆን ኃላፊነት ነው። ይህን ስል የእግዚአብሔር ሕዝብ ኃጢአታቸውን እንዲያዩ ማድረግና የተሳሳተ ዝንባሌያቸውን ሁሉ በግልጽ መቃወም አለባቸው ማለቴ ነው። እግዚአብሔር በረከቱን ያለማቋረጥ እንዲሰጥ የእግዚአብሔር ሕዝብ ንጹሕ አምልኮና ኑሮ እንዲኖሩ የማስተማርና የማበረታታት ኃላፊነት አለባቸው። እግዚአብሔር የሕዝቡን ንጽሕና ጠብቆ ለማቆየት በቤተ ክርስቲያን መሪዎች እንዴት እንደሚጠቀም የሚያሳይ ጥሩ ምሳሌ ሚልክያስ ነው።
ሚልክያስ በሕዝቡ ሕይወት ውስጥ ያሉትን ችግሮች የሚጠቁሙ አጫጭር መልእክቶችን በመጽሐፉ ውስጥ አቅርቧል። ብዙ ጊዜ የሚጀምረው እውነታን ወይም ጭብጥን የያዙ አጫጭር ዐረፍተ ነገሮችን በማቅረብ ሲሆን፥ ሕዝቡ ከእነዚህ ዐረፍተ ነገሮች በመነሣት እግዚአብሔርን ይጠይቃሉ።
1.1ኛ ጥያቄ፥ እግዚአብሔር እኛን የወደደን እንዴት ነው? (ሚልክያስ 1፡1-5)
ሰዎች ሁሉ የኢኮኖሚ ችግር ወይም በሥጋቸው ላይ ጉዳት የሚያደርስ ነገር ሲገጥማቸው የሚሰጡት ምላሽ ከሚከተሉት ሁለት ነገሮች አንዱን ነው:- አንዳንዶች ትከሻቸውን በመስበቅ ይህንን ችግር በሕይወቴ ላይ ያመጣ እግዚአብሔር ስለሆነ ምንም ማድረግ አልችልም ይላሉ። ሌሎች ደግሞ ወደ አለማመንና የተጣመመ ትርጉም ወደ መስጠቱ በመቻኰል የእግዚአብሔርን ፍቅር በጥያቄ ምልክት ያስቀምጡታል። አይሁድ ተጠራጣሪና ጠማማ በሆን ልባቸው ወደ እግዚአብሔር በመመልከት፥ እርሱ በእርግጥ ይወዳቸው እንደሆነ መጠየቅ ጀምረው ነበር።
እግዚአብሔር ለእነርሱ ያለውን ፍቅር ለማረጋገጥ ለአይሁድ ታሪካዊ የሆነው የእስራኤልን ጥሪ ያስታውሳቸዋል። የያዕቆብ ዝርያዎች የሆኑትን እስራኤላውያንን የዔሳው ዝርያዎች ከሆኑት ከኤዶማውያን ጋር ያወዳድራቸዋል። ያዕቆብና ዔሳው ወንድማማቾች ቢሆኑም እንኳ እግዚአብሔር የጠራውና ቃል ኪዳን ያደረገው ከያዕቆብ (እስራኤል) ጋር ብቻ ነበር። የአይሁድ ታሪካዊ ጠላቶች የሆኑት ኤዶማውያን እንደሚበለጽጉ ቢያስቡም እንኳ እግዚአብሔር እንደሚፈርድባቸው ተናገረ። በሌላም በኩል እግዚአብሔር እስራኤልን እንደሚባርክ ተናገረ።
ክርስቲያኖችም የተጠሩት በእግዚአብሔር ነው (ሮሜ 8፡28-30)። እግዚአብሒር በዓለም ከሚኖሩ ሕዝቦች መካከል መረጣቸው። ይህ የእግዚአብሔር ፍቅር ልዩ ምልክት ነው።
2.2ኛ ጥያቄ፥ ካህናት የሆንን እኛ የእግዚአብሔርን ስም ያቃለልነው እንዴት ነው? (ሚልክያስ 1፡6-2፡9)
ከእንስሳት ወገን የሚመደቡት በሬ፥ አህያ ወይም ፍየል ባለቤታቸው ማን እንደሆነ በመረዳት ይታዘዙታል። ከእንስሳት ይልቅ ከፍተኛ የማሰብ ችሎታ ያለው ሰው ግን ፈጣሪው የሆነውን እግዚአብሔርን አላከበረም፤ አላወቀውምም። እስራኤላውያን ይህንን በተጠራጠሩ ጊዜ እግዚአብሔር ለእርሱ ያሳዩትን አክብሮት የጎደለው ሁኔታ ለካህናትና ለእስራኤላውያን አሳያቸው። ይህንን በተለያዩ መንገዶች ያደርጉ ነበር። በመጀመሪያ፥ ሕዝቡ በካህናት ትእዛዝ ለእግዚአብሔር ተገቢ ያልሆነ መሥዋዕት ያቀርቡ ነበር። ይኸውም ዕውርና ሽባ የሆኑ እንስሳትን ለመሥዋዕት በማቅረብ ነው። ለምድራዊ መሪዎች እንኳ የማይቀርበውን ለእግዚአብሔር ያቀርቡ ነበር። እግዚአብሔር ይህን የመሰለ እርሱ የማይከበርበት ሥርዓታዊ አምልኮ ከሚፈጸም ከቶውኑ ባይቀርብ መረጠ።
ሁለተኛ፣ ካህናት እግዚአብሔርን ለማገልገል በነበራቸው ዝንባሌ ውስጥ እርሱን አያከብሩም ነበር። ካህናት በቤተ መቅደስ ውስጥ ባለማቋረጥ የሚበራውን መብራት መለኮስ፥ በወርቅ መሠዊያው ላይ ዕጣን ማጠን ወይም እንስሳትን ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ ታክቶአቸው ነበር።
በሦስተኛ ደረጃ፥ ካህናት ለሕዝቡ የእግዚአብሔርን መንገዶች ለማስተማር ፈቃደኞች ባለመሆን እርሱን አያከብሩም ነበር።
የእስራኤል መንፈሳዊ መሪዎች የነበሩት ካህናት፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር የክህነት ቃል ኪዳን እንዳደረገው እንደ አሮን የልጅ ልጅ እንደ ፊንሐስ አልነበሩም (ዘኁልቁ 25፡10-13)። ስለዚህ እግዚአብሔር የእስራኤልን አምልኮ የመምራት መብት ከእነርሱ በመውሰድ ሊፈርድባቸው ግድ ነበር።
የውይይት ጥያቄ፥ ዛሬ ክርስቲያኖችና የቤተ ክርስቲያን መሪዎች የዚህ ዓይነት ተመሳሳይ ዝንባሌ ሊኖራቸው የሚችለው እንዴት ነው? ምሳሌዎችን ዘርዝር።
3. 3ኛ ጥያቄ፥ እኛ ሕዝቡ ለቃል ኪዳኑ ታማኞች ያልሆንነው እንዴት ነው? (ሚልክያስ 2፡10-16)
የእግዚአብሔር የቃል ኪዳኑ ሕዝብ መሆናችንን የምናረጋግጠው በምናምነው ወይም በምንናገረው ነገር ብቻ ሳይሆን፥ በምንኖረው ኑሮ ጭምር ነው። የክርስቶስ አካል የሆነው የእግዚአብሔር የቃል ኪዳን ሕዝብ አካል ክፍል በምንሆንበት ጊዜ እርስ በርሳችን የምናደርገውን ግንኙነት ለመለወጥ መቻል አለብን። ሁላችንም አንድ ቤተሰብ ነን። የመንፈሳዊ ቃል ኪዳን ሕዝብ ቤተሰብ ደግሞ በሥጋ ከተወለድንበት ቤተሰብ ይበልጥ የላቀና አስፈላጊ ነው።
አይሁድ እግዚአብሔርንና ቃል ኪዳኑን ያቃልሉ ነበር። ይህን ነገር በጋብቻ ሕይወታቸው ውስጥ እንዴት እንደፈጸሙት ለማስረዳት ሚልክያስ ሁለት ምሳሌዎችን ይጠቅሳል፡፡
ሀ) ሕዝቡ ጣዖታትን ከሚያመልኩ አሕዛብ መካከል ሚስቶችን አግብተው ነበር፤
ለ) ሕዝቡ በእግዚአብሔር ፊት ቃል ኪዳን የገቡላቸውን ሚስቶቻቸውን ፈትተው ነበር።
የሚልክያስ የመጨረሻ ክፍል በይበልጥ የሚያተኩረው በመጪው ጊዜ ላይ ነው። የእግዚአብሔርን ሕዝብ ክፋትና ኃጢአት የሚናገር ቢሆንም እንኳ መሚሑ ወይም ኤልያስ» በሚመጣበት ጊዜ ስለሚፈጸሙ ነገሮች ይናገራል።
4. 4ኛ ጥያቄ፥ እግዚአብሔርን ያሰለቸነው በምንድን ነው? (ሚል. 2፡17-3፡6)
ክፉ የሚያደርጉ ሰዎች በጥፋታቸው ላይያዙና ሳይቀጡ ሲቀሩ፥ የእግዚአብሔር ሰዎች የዓለምን ድርጊት መከተልና ተመሳሳይ ክፋት መፈጸም ይጀምራሉ። ጉቦ በመቀበልና በፈተና ጊዜ ከሌሎች መኮረጅ መልካም እንደሆነ በአፋቸው ባይናገሩም እንኳ እግዚአብሔር ክፉ ነው ያለውን ይህን ነገር በተግባር መልካም እንደሆነ ያህል ይለማመዱታል። «ይህን ነገር ሌሎች አድርገው ከተሳካላቸው እኔም ማድረግ አለብኝ። ስለዚህ ጉዳይ እግዚአብሐር ቢገደው ኖሮ ሊቀጣቸው ይገባ ነበር» ብለው ማሰብ ይጀምራሉ። ከዚህም የተነሣ የሥነ-ምግባር መመዘኛቸው የረከሰ ይሆናል።
እግዚአብሔር የዚህን ችግር መፍትሔ ለማግኘት «መልእክተኛውን» እንደሚልክ ይናገራል። መልእክተኛ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በፍርድ ሲመጣ ክፉ የሚያደርጉትን ሁሉ ይቀጣል። የገዝ ሕዝቡ ከዚህ ዓይነት አስተሳሰብና ተግባር ይነጹ ዘንድ በስደት ውስጥ በማሳለፍ ያጠራቸዋል። ከዚያም ሕዝቡ በቃልና በተግባር በመንጻት፥ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ያለው መሥዋዕት ያቀርባሉ።
ማስታወሻ፡- ሚልክያስ በንግግርና በማኅበራዊ ፍትሕ ኃጢአት ላይ ያተኮረበትን መንገድ ልብ ብለህ ተመልከት።
5. 5ኛ ጥያቄ፥ ወደ እግዚአብሔር እንዴት ልንመለስ እንችላለን? (ሚልክያስ 3፡7-12)
እግዚአብሔር ባሕርዩን ለሙሴ በገለጸበት ጊዜ መሐሪና ለቁጣ የዘገየ እንደሆነ ነግሮት ነበር (ዘጸአት 34፡6)። የእግዚአብሔር ባሕርይ ከቶውኑም ሊለወጥ አይችልም። እግዚአብሔር በሙሴ ጊዜ እንደነበረ፥ በሚልክያስም ጊዜ ነበር፤ በእኛ ጊዜም አለ። ስለዚህ እግዚአብሔር ከኃጢአታቸው ይመለሱ ዘንድ ሕዝቡን ጋበዛቸው።
ንስሐ በተለወጠ አካሂድ ራሱን መግለጥ አለበት። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ንስሐ ያለው አመለካከት የአስተሳሰብ ለውጥን ብቻ ሳይሆን፥ የተግባር ወይም የኑሮ ለውጥን ጭምር የሚመለከት ነው። ሚልክያስ ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ እንዴት መለወጥ እንዳለባቸው ለእስራኤላውያን ለማሳየት በሕይወታቸው ሊያከናውኑአቸው ከሚገባ ተግባራት አንዱን ጉዳይ ያነሣል፤ ይህም:- አሥራታቸውን ለእግዚአብሔር የመስጠት ጉዳይ ነበር። ሚልክያስ ሕዝቡ ከእግዚአብሔር ጋር የገቡትን ቃል ኪዳን በክበር፥ ከሚያገኙት ነገር ሁሉ ከምርቱና ከገንዘቡ አንድ አሥረኛውን ለእግዚአብሔር እንዲሰጡ ጠየቃቸው። ይህንን ካደረጉ እግዚአብሔር በሥጋ ሊባርካቸውና እነርሱም በሕዝቦች ሁሉ ዘንድ የተባረኩ እንደሚባሉ ቃል ገባላቸው።
6. 6ኛ ጥያቄ፥ በእግዚአብሔር ላይ ደፍረን የተናገርነው እንዴት ነው? (ሚልክያስ 3፡13-4፡3)
በሚልክያስ 2፡17-3፡6 እንዳየነው፥ እስራኤላውያን ክፉ የሚሠሩ እየበለጸጉ ሲሄዱ ጻድቅ መሆን የተሻለ ዋጋ አለውን? ብለው የጥርጥር ጥያቄ መጠየቅ ጀምረው ነበር። ስለዚህ ከጽድቅ አኗኗር ይልቅ በክፋት መኖር እንደሚሻል በመገመት ኃጢአተኞች ሆነው መኖር እንደሚገባቸው ማሰብ ጀመሩ።
እግዚአብሔር የሚያደርጉትን ሁሉ እንደሚያስታውስ በመንገር እስራኤላውያንን ያስጠነቅቃቸዋል። በቅድስና በመኖር እግዚአብሔርን ያከበሩ ሰዎች ያደረጉትን ነገር ሁሉ እግዚአብሔር በመዝገብ ጽፎታል፤ በጊዜውም ይሸልማቸዋል። እግዚአብሔርን አናከብርም ብለው ዓለምን የተከተሉትን ሁሉ እንደሚቀጣቸው ተናግሮአል።
«የጽድቅ ፀሐይ» የሆነው መሢሑ ሲመጣ፥ ክፉ ሰዎች ሁሉ በእሳት ውስጥ እንዳለ ገለባ ይቃጠሉና ጻድቃን ፈውስ አግኝተው ደስታና ሐሤትን ያደርጋሉ።
7. ለሕዝቡ የተሰጠ የመጨረሻ ምክር (ሚልክያስ 4፡4-6)
የብሉይ ኪዳን የሚጠቃለለው ሰዎች ለእግዚአብሔር ሕግጋት እየታዘዙ እንዲጓዙ በመምከር ነው። ከሙሢሑ አስቀድሞ የሚመጣውን ኤልያስን መጠባበቅ ነበረባቸው። ኤልያስ የሕዝቡን ልብ ወደ ቀደምት አባቶቻቸው በመመለስ የምድሪቱን መንፈሳዊ ሁኔታ ለመለወጥ ይፈልግ ነበር። በቤተሰብ መካከል አንድነትን ያመጣ ነበር። ዳሩ ግን ይህንን የማይቀበሉ ሁሉ ከባድ ፍርድ ያገኛቸዋል።
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በትንቢተ ሚልክያስ ውስጥ የሚገኙትን ዐበይት እውነቶች ዘርዝር። ለ) በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ ለሚገኙ ምእመናን መንፈሳዊ ትምህርት ለማስተማር፥ የትንቢተ ሚልክያስ ሰባት ክፍሎች እያንዳንዳቸው ሊጠቅሙ የሚችሉባቸውን ግልጽ መንገዶች ዘርዝር።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
የመመዘኛ ጥያቄዎችን ለማግኘት ከታች ያለውን ሊንክ (መስፈንጠሪያ) ይጫኑ፡፡