የክርስቶስ ተልዕኮ (2ኛ ቆሮ.5፡18-21)

በዚህ አንቀጽ ውስጥ ቁልፉ አሳብ ዕርቅ ነው። ሰው ከዓመፁ የተነሣ፥ የእግዚአብሔር ጠላትና ከእርሱ ጋር ከሚኖረው ኅብረት የራቀ ነበር። ከመስቀሉ ሥራ የተነሣ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ ሰውንና እግዚአብሔርን ወደ አንድነት አመጣ። እግዚአብሔርም ከሰው ጋር በመታረቅ፥ ፊቱን በፍቅር ወደ ጠፋው ዓለም መለሰ። የዕርቅ መሠረታዊ ትርጉም «ሙሉ ለሙሉ መለወጥ» የሚል ሲሆን፥ በእግዚአብሔርና በጠፋው ዓለም መካከል የተደረገውን የግንኙነት ለውጥ ያመለክታል። 

የዕርቅ ሥራ በመስቀል ላይ ስለ ተፈጸመ፥ ለእግዚአብሔር ከሰው ጋር ዕርቅን ማድረግ አያሻውም። ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ያለበት ኃጢአተኛው ሰው ነው። «ሃይማኖት» ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ለመታረቅ የፈጠረው ደካማ ዘዴና ከንቱም ልፋት ነው። ከእግዚአብሔር ጋር የሚያስታርቀን አካል ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን፥ የመታረቂያ ቦታውም ከመስቀሉ ሥር ነው። 

በዚህ ክፍል ውስጥ ሌላው ቁልፍ አሳብ መቁጠር የሚለው ሲሆን (ለምሳሌ የእኛ ኃጢአት በክርስቶስ ላይ ተቆጠረ)፥ አሳቡ በባንክ ቤት ውስጥ ገንዘብ ከማከማቸት ጋር የሚዛመድ ነው። «በአንድ ሰው የሂሳብ ደብተር ውስጥ ገንዘብ ማስቀመጥን» ያመለክታል። ገንዘብ በባንክ ቤት ውስጥ ስታስቀምጥ፥ ኮምፒውተሩ (ወይም ሠራተኛው) ያንኑ የገንዘብ መጠን በሂሳብ ደብተርህ ውስጥ ይመዘግባል። ኢየሱስ በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ፥ ኃጢአታችን በሙሉ ወደ እርሱ ተላለፈ – በርሱ ደብተር ላይ ተመዘገበ። እግዚአብሔርም እነዚያን ሁሉ ኃጢአቶች ክርስቶስ ራሱ እንደ ፈጸማቸው አድርጎ ቆጠረ። 

ውጤቱስ? ክርስቶስን እንደ አዳኛችን አድርገን ስላመንን፥ እግዚአብሔር የእነዚያ ሁሉ ኃጢአቶች ዋጋ እንደ ተከፈለ በመቁጠር፥ ከእንግዲህ በእኛ ላይ ኃጢአቶችን አይዝም። ከዚህም በላይ፥ እግዚአብሔር በእኛ መዝገብ ውስጥ የክርስቶስን ጽድቅ አስቀምጦታል! «እኛ በእርሱ ሆነን የእግዚአብሔር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ኃጢአት ያላወቀውን እርሱን [ክርስቶስን] ስለ እኛ ኃጢአት አደረገው» (ቁ 21)። 

ዕርቅ [ኃጢአትን በመሸከም ላይ የተመሠረተ ነው፡- ምክንያቱም የእግዚአብሔር ቅዱስ ሕግ መጠይቆች በመስቀሉ ላይ ሙሉ ለሙሉ ስለ ተፈጸሙ፥ እግዚአብሔር ከኃጢአተኞች ጋር ሊታረቅ ይችላል። ኢየሱስ ክርስቶስን አዳኛቸው አድርገው የሚያምኑ ሰዎች፥ ኃጢአታቸውን ዳግም አይቆጥርባቸውም [ሮሜ. 4፡1-8፤ መዝ. (32):1-2]፡ መዝገባቸውንም በተመለከተ፥ የኢየሱስ ክርስቶስን ጽድቅ ለመጋራታቸው ተረጋግጦላቸዋል። 

ጳውሎስ ለወዳጁ ለፊልሞና በጻፈው አነስተኛ መልእክት ውስጥ ይህንኑ እውነታ የሚያብራራ ግሩም መግለጫ አለ። የፊልሞና ባሪያ የነበረው አናሲሞስ ከጌታው ዘንድ ገንዘብ ሰርቆ ወደ ሮም ሸሽቶ ነበር። በዚህ ወንጀሉም ሊገደል ይችል ነበር። ይሁንና እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ፥ አናሲሞስ ከጳውሎስ ጋር ተገናንና ደኅንነትን ተቀበለ። ከዚያም ጳውሎስ አናሲሞስን ይቅር ብሎ ወደ ቤት ያስገባው ዘንድ ለማበረታታት ለወዳጁ ለፊልሞና ደብዳቤ ይጽፍለታል። ጳውሎስ፥ «እንደ እኔ አድርገህ ተቀበለው …ብድር ያለበት እንደ ሆነ፥ ይህን በእኔ ላይ ቁጠር» (ፊልቁ 17 ና 18) ይለዋል። ጳውሎስ አናሲሞስና ፊልሞና እንዲታረቁ ዕዳውን ለመክፈል ፈቃደኛ ነበር። 

ይህ አስደናቂ የዕርቅ ትምህርት ክርስቶስን እንድናገለግል እንዴት ያነሣሣናል? እኛ መልእክት ያለን አምባሳደሮች ነን። እግዚአብሔር የዕርቅን አገልግሎት (2ኛ ቆሮ. 5፡18) እና የዕርቅን ቃል (ቁ. 19) ሰጥተናል። 

በሮም መንግሥት ውስጥ ሴናተሪያልና ኢምፔሪያል የሚባሉ ሁለት የግዛት ዓይነቶች ነበሩ። ሴናተሪያል የሚባሉት ከሮም ጋር መዋጋትን አቁመው በሰላም የሚኖሩቱ ናቸው – እጃቸውን በመስጠት ተገዝተው የሚኖሩ ጻሩ ግን ኢምፔሪያሎቹ አቅሙ ከፈቀደላቸው በሮም ላይ ለማመፅ ይፈልጉ ስለ ነበር፥ አደገኞች ነበሩ። በመሆኑም ዓመፁ እንዳይነግሣ ሮም ወደ ኤምፔሪያል ግዛቶች አምባሳደሮችን መላክ ያስፈልጋት ነበር። 

በዚህ ዓለም ውስጥ ክርስቲያኖች የክርስቶስ አምባሳደሮች ስለ ሆኑ፥ ዓለም በእግዚአብሔር ላይ በማመፅ ላይ ነች ማለት ነው። ይህች ዓለም ለእግዚአብሔር «የኢምፔሪያል ግዛት» ነች። እርሱም አምባሳደሮቹን ወደ ዓለም የላከው ጦርነትን ሳይሆን፥ ሰላምን እንዲያውጁ ነው። «ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ! » ብለን ኢየሱስ ክርስቶስን እንወክላለን (2ኛ ቆሮ. 4፡5፤ የሒ20፡21)። ኃጢአተኞች እኛንና መልእክታችንን ቢገፉ፥ በመሠረቱ የተገፋው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ለዚህ ዓለም ዕመፀኛ ኃጢአተኞች የሰማይ አማባሳደር ሆኖ መሾም ምንኛ ታላቅ ዕድል ነው! 

ገና ወጣት መጋቢ በነበርሁበት ጊዜ፥ ሰዎችን ለመጎብኘትና ስለ ክርስቶስ አዳኝነት ለመመስከር ኃፍረት ይሰማኝ ነበር። በኋላ ግን የነገሥታት ንጉሥ አማባሳደሩ ሆኘበመሾም፥ ዕድለኛ መሆኔን ተረዳሁ። ምንም የሚያሳፍረኝ ነገር አልነበረም። እንዲያውም፥ የምጎበኛቸው ሰዎች፥ ከክርስቶስ አምባሳደሮች አንዱ ሊጠይቃቸው በመምጣቱ መደሰት ነበረባቸው። 

እግዚአብሔር በዓለም ላይ ጦርነትን አላወጀም፤ ይልቁንም በመስቀሉ ላይ ሰላምን አውጇል። ይሁንና አንድ ቀን ጦርነትን ያውጃል፤ በዚያን ጊዜም አዳኙን ለገፉት ሰዎች ጊዘው ይመሽባቸዋል (2ኛ ተሰ. 1፡3-10)። ሰይጣን በዓለም ውስጥ ነገሮችን ሁሉ ለመበታተን እየጣረ ነው፤ ዳሩ ግን ክርስቶስና ቤተ ክርስቲያኑ ነገሮችን ወደ አንድነት በማምጣቱና ወደ እግዚአብሔር ዘንድ በመመለሱ የዕርቅ አገልግሎት ላይ ተሰማርተዋል። 

አገልግሉት ቀላል አይደለም። በአገልግሎታችን ስኬታማ ለመሆን ከፈለግን፥ አነሣሽ ምክንያታችን ፈሪሃ-እግዚአብሔር፥ አፍቅሮተ-ክርስቶስና እንዲሁም እርሱ የሰጠን ተልዕኮ መሆን አለበት። እርሱን ማገልገል ምንኛ መታደል ነው!

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading