ጥያቄ 15. በቁጥር 22 እስከ 26 ባለው ክፍል ውስጥ በአካል መካከል መተሳሰብ እንዲኖር ካለ በቆሮንቶስ ምእመናን መካከል ግን ምን እንደነበር እንረዳለን?
ጥያቁ 16. ከቁጥር 28-31 ያለውንና ከቁጥር 8-11 ያለውን አወዳድረህ መመሳሰልም ሆነ ልዩነት ጻፍ።
ከቁጥር 14 – 26 ባለው ክፍል ውስጥ ሐዋርያው እንዴት የክርስቶስ አካል እንደ ሰውነት በአንድነት መስራት እንዳለበት ያስተምራል። በቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እግዚአብሔር የተለያየ ሥጦታን ስለሰጣቸው ይህ በመካከላቸው መለያየትን፥ መናናቅን፥ መቀናናትን ፈጠረ። ምንም እንኳ የመንፈስ ቅዱስ ሥጦታዎች በብዛት የሚታዩበት ቤተ ክርስቲያን ቢሆንም “መለያየት” የተባለው የሥጋ ሥራ ነግሶባቸው እንደነበር እንረዳለን። አሁንም በዘመናችን የመንፈስ ቅዱስን ሥጦታዎች አሉን በሚሉ መካከል እንዲሁ ከባድ መለያየት እንዳለ እንመለከታለን። ስለዚህ የመንፈስ ቅዱስን ሥጦታዎች በመንፈስ ቅዱስ ፍሬ በሆነው በፍቅር መስራትን አንዘንጋ ( 1ኛ ቆሮ.13፤ ገላ.5፡22-26)።
ስለ ቤተ ክርስቲያን ማወቅ የምንችለው ዋነኛ የሆነውን የክርስቶስን አካል ትምህርት በመረዳት ነው። ልክ እንደ ሰው አካል ቤተ ክርስቲያን አንድ ራስ ነው ያላት። ይህም የቤተ ክርስቲያን ራስ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ (ኤፌ.1፡22-23)። ራስ የሆነው ከሁሉ የበላይ ሆና ይመራል፤ ከእርሱም ምሪት ሥር ደግሞ በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ያመኑት የተለያዩ አማኞች በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነትም ከአካሉ ጋር ይገናኛሉ። የመንፈስ ቅዱስ ሥራ በዚህ ብቻ አይወሰንም፤ እያንዳንጹን ሰው ተገቢውን ቦታ አስይዞ ሥሪውን የሚፈጽምበትን ሥጦታ ይሰጠዋል። የሚሰጣቸው አንዳንዶቹ ሥጦታዎች በጣም የከበሩ ይመስላሉ! በዚህም ምክንያት የበለጠ ክብር የሚያስገኙት ለሰውየው እንደሆነ ይገመታል። ሌሎች ሥጦታዎች ደግሞ የተደበቁ ናቸው፤ ነገር ግን አካካሉ ጤንነትና ሥራ ትልቅ አስተዋፅኦ አላቸው። በዚህ ምክንያት የክርስቶስ አካል አባል የሆነ ሰው ሁሉ በጣም አስፈላጊ ነው። አንዱ ከሌላው ጋር አብሮ ስለሚሠራ ኃላፊነት ካለባቸው ከመሪዎች አንሥቶ እስከ ተራ አባል ድረስ ያለው በሙሉ ጥቅም የሚሰጥ ነው። በእግዚአብሔር አይን ሁሉም እኩል ናቸው። እንደ አንድ አካል ጤነኛ ሆነን እንሠራለን የምንለው እያንዳንዱ የአካሉ ክፍል የተሰጠውን መንፈሳዊ ስጦታ በተገቢው መንገድ ሲጠቀምበት ነው። ስለዚህ አንዱ የአካሉ ክፍል ሥጦታውን የማይጠቀምበት ከሆነ ልክ እግሩ እንደተቆረጠና አይነ ስውር እንደሆነ ሰው፥ አካሉ በአጠቃላይ አካል ስንኩል ሆኗል ማለት ነው። በዚህም ምክንያት ሌሎች አባላት እንደ እኛ ሥጦታ የላቸውም ብለን ገለልተኛ ማድረግ የለብንም። እያንዳንዱ አባል ሥጦታውን አውቆ፥ ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት እንዲጠቀምበት የማድረግ ኃላፊነት የተሰጠው ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች ነው።
ጥያቄ 17. ሀ/ የቤተ ክርስቲያንህ መሪዎች እንዴት አድርገው ነው እያንዳንዱ አባል መንፈሳዊ ሥጦታውን አውቆ እንዲ ያገለገል የሚያደርጉት? ለ/ ከዚህ ከሚያደርጉት ሌላ የተሻለ፥ አባላቱን በአንድነት ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት እንዲሠሩ የሚረዳ ምንድነው ብለህ ትገምታለህ?
በዚህ ክፍል ውስጥ ደግሞ ሌላ የምናየው ዋና ትምህርት አለ። ይህም፡- “አንድ ብቸኛ የክርስቶስ አካል” መናሩን ነው። ይህም ማለት እውነተኛው የክርስቶስ አካል የተሠራው በኢየሱስ ክርስቶስ በሚያምኑት ክርስቲያናት ነው ማለት ነው። አጥቢያ ቤተ ክርስቲያኖች ያንን እውነት በከፊል የሚያንፀባርቁ መሆን አለባቸው። ይህም በሰዎች የተለያየ ስም የተሰጣቸው ቤተ ክርስቲያና (ቃለ ሕይወት፥ መካነ ኢየሱስ፥ ወዘተ) የዚህ አካል አባል ናቸው ማለት ነው። በዚህም ምክንያት ለክርስቶስ አካል ዕድገት አብረን መሥራት ይኖርብናል እንጂ በአካሉ ላይ ብዙ ክፍፍልን መፍጠር የለብንም።
ጥያቄ 18. ዓለም አቀፍ ስለሆነው የክርስቶስ አካል ያለን ግንዛቤ እንዴት አድርጎ ነው ከሌሎች ከእኛ ከተለዩ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያኖች ጋር ሊኖረን የሚገባውን ግንኙነት የሚወስነው?
ከቁጥር 27-31 ባለው ክፍል ውስጥ እንደገና ስለ መንፈስ ቅዱስ ሥጦታዎች ይናገራል። በዚህ ላይ አጥብቀን መመልከት ያለብን በመጀመሪያ ሁሉም አንድ ዓይነት ሥራ የላቸውም። ሁለተኛ በሥጦታዎች መካከል እኩል ቤተ ክርስቲያንን የማነጽ ኃይል የለም። አንዳንድ ሥጦታዎች ከሌሎች ሥጦታዎች የበለጠ ቤተ ክርስቲያንን የመገንባት ኃይል አላቸው። ቃሉን የማስተላለፍ ሥጦታዎች ከሌሎች ሥጦታዎች የበለጠ ጥቅም አላቸው።
በኤፌሶን 2:20-22 ላይ ሐዋርያትና ነቢያት የቤተ ክርስቲያን መሠረቶች ናቸው። ቤተ ክርስቲያን በዚያን ጊዜ በነበሩት ሐዋርያትና ነቢያት ትምህርት ላይ ቆማለች እንጂ በየጊዜው በሚነሡ ነቢያት አማካይነት አዲስ ትምህርትን አትቀበልም፡፡
ጥያቄ 19. ሀ/ ጳውሎስ «ነገር ግን የሚበልጠውን የጸጋ ሥጦታ በብርቱ ፈልጉ» ይላል። እነዚህ ሥጦታዎች የትኞቹ ናቸው?