2ኛ ቆሮ. 13:1-14

ሐዋርያው በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የመጨረሻ ሐሳቡን ይዘረዝራል። ይህ የጥናታችን መደምደሚያ ይሆናል፡፡ እግዚአብሔር በእነዚህ በሁለት መጽሐፎች ማለት በ1ኛና በ2ኛ ቆሮንቶስ ያስተማረን ብዙ ነገሮች አሉ። እነዚህን ራሳችን በሥራ ላይ እያዋልናቸው ለሌሎችም እንድናካፍል እግዚአብሔር ጸጋውን ይስጠን። 

ይህ የጥናታችን የመጨረሻው ነው። በዚህ ምዕራፍ ውስጥ ያሉት ሃሳቦች በፊት የተጠቀሱ ናቸው። ዋናው የምዕራፉ ነጥብ ሐዋርያው ለሦስተኛ ጊዜ ሊጎበኛቸው ሲሄድ ሁሉም ንስሐ ገብተው በጥሩ የክርስቲያን አቋም እንዲገኙ ማሳሰቢያ ነው። 

ጥያቄ 1 በቁጥር 3 ላይ “ክርስቶስ በእኔ አድሮ እንዲናገር ማስረጃ ከፈለጋችሁ” ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ አስረዳ። 

ጥያቄ 2. በቁጥር 5 ላይ “ወይስ ምናልባት የማትበቁ ባትሆኑ” ማለት ምን ማለት ነው? 

ከቁጥር 1-4:- የሐዋርያውን ሥልጣን የናቁትን ያስጠነቅቃቸዋል። የሐዋርያው ኃይል የራሱ ሳይሆን የክርስቶስ ኃይል ነው። ስለዚህ የሐዋርያውን ሥልጣን መናቅ የሾመውን የክርስቶስን ኃይልና ሥልጣን መናቅ ነው፡፡ ይህ ነጥብ አሁንም በቤተ ክርስቲያን ሊታወስ ይገባዋል። ክርስቶስ የሾማቸውን መናቅ ክርስቶስን መናቅ ነው። እርገግ አገልጋዮችም በሕዝቡ ፊት በትሕትና መገኘት አለባቸው። ሕዝቡንም በግል መብታቸው ሳይሆን በክርስቶስ ቃል መሠረት ማዘዝ አለባቸው። ይህ ሲደረግ ይህንን ዓይነት ሥልጣን መናቅ ክርስቶስን መናቅ ነው። 

እንግዲህ ሐዋርያው ሲሄድ ንስሐ ገብተውና ተስተካክለው ካላገኛቸው በእርሱ ውስጥ ያለውን የክርስቶስን ኃይል ያሳያቸዋል። ይህን ማድረግ አይፈልግም፤ ነገር ግን ወደዚያ እርምጃ እንዳያስገድዱት ይለምናቸዋል። 

ከቁጥር 5-10፡- በቁጥር 5 እያንዳንዳቸው እውነት በክርስቶስ ላይ እምነት እንዳላቸው ወይም እንደሌላቸው በግላቸው ማጣራት እንዳለባቸው ይናገራል። ብዙውን ጊዜ በቤተ ክርስቲያን መሪዎችን በመቃወም የጌታን ሥራ የሚከለክሉ በእርግጥ ጌታን አያውቁትም ይሆናልና ልባቸውን እንዲመረምሩ መናገር ተገቢ ይሆናል። 

ጥያቄ 3. በየጊዜው ሕይወታችንን መመርመሩ አስፈላጊ የሆነው ለምንድነው? 

በቁጥር 10 ላይ በመጣ ጊዜ በቁርጥ ሥልጣን በማሳየት ሐዋርያዊ ተግሣጽ ማምጣት እንዳያስፈልገው በሩቅ ሳለ በደብዳቤ ያስጠነቅቃቸዋል። በዚያን ጊዜ የቤተ ክርስቲያን ቅጣት ወዲያውኑ በዓይን የሚታይ መቅሰፍት ያስከትል ነበር። አሁን ብዙውን ጊዜ ይህ ስለማይታይ የቤተ ክርስቲያንን ተግሣጽ ሰዎች አይፈሩም። ነገር ግን በቤተ ክርስቲያን ቅጣት አሁንም ክርስቶስ ተባባሪ መሆኑን መዘንጋት የለብንም! እርግጥ የቤተ ክርስቲያን ቅጣት በመጽሐፍ ቅዱስ መሠረት መደረገ አለበት፤ ካለበለዚያ የቤተ ክርስቲያን ቅጣት ሊባል አይገባውም። ቤተ ክርስቲያን በትክክል የምታቀርበውን ቅጣት የናቁትን እግዚአብሔር  በሚታይ ተግሣጽ እንደሚገሥጽ መዘንጋት የለብንም። ስለዚህ የቤተ ክርስቲያንን ሥልጣን የናቀ የክርስቶስን ሥልጣን የናቀ መሆኑን መዘንጋት የለበትም። 

ጥያቄ 4. ይህንን በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ ተግባራዊ ልታዳርገው የምትችለው እንዴት ነው?

Leave a Reply

%d bloggers like this: