2ኛ ቆሮ. 10፡13-18

ጥያቄ 5. “እስከ እናንተ እንኳ እንደሚደርስ እንደ ክፍላችን ልክ እንጂ ያለልክ አንመካም” ማለት ምን ማለት ነው? 

ጥያቄ 6. በቁጥር 16 ላይ “በሌላው ክፍል ስለተዘጋጀው አንመካም» ማለት ምን ማለት ነው? 

ቁጥር 13:- ሐዋርያው አገልግሎቱን ለሩጫ እሸቅድድም እንደተሰለፈ ሰው ይመስላል፡፡ በሩጫ ሕጋቸው ለእያንዳንዱ ሯጭ መሥመር ይደለደል ነበር። በመሥመሩ ብቻ መሮጥ ነበረበት እንጂ በሌላ ሰው መሥመር ውስጥ ሾልኮ ቢገባ ከሩጫው ውድድር ይወጣ ነበር። እንዲሁም ጳውሎስ እግዚአብሔር የሥራ መስክ እንደዘረጋለትና በዚያው መሥመር «ሕጉን» ጠብቆ እንዳለ፥ እነዚያ በቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ግን ሾልከው የገቡት እግዚአብሔር ባልሰጣቸው የሥራ መሥመር ጣልቃ ገብ መሆናቸውን ይናገራል። ሌሎች ወደ ክርስቶስ የመሩአቸውን አማኞች እየሰረቁ ቤተ ክርስቲያንን ማስፋፋትና አዲስ ቤተ ክርስቲያን እያሉ በሌሎች ድካም ላይ መንጠልጠል የሐሰተኛ አስተማሪዎች ፀባይ መሆኑን በዚህ ቃል እንገንዘብ፡፡ 

ጥያቄ 7. ይህን መሰል ጣልቃ ገብ ሠራተኞች ታውቃለህ? እነማን ናቸው? ጥቀሳቸው! የእነርሱንም ፀባይ ለምእመናን በማስረዳት ከእነርሱ እንዲጠበቁ አስጠንቅቃቸው!! 

ቁጥር 14:- ሐዋርያው በተዘረጋለት የአገልግሎት መሥመር እስከ ቆሮንቶስ ደርሷል። ስለዚህ በሌሎች ሥራ ገብቶ አይደለም የተመካው። ሐሰተኞቹ አስተማሪዎች ግን እርሱ በደከመበት ወይም እርሱ በሠራበት ጣልቃ ገብተው ነበር ይመኩ የነበረው። 

ከቁጥር 15-16፡- ከላይ የጀመረውን ሃሳብ በመቀጠል የወንጌል ሥራውን ከቆሮንቶስ አልፎ ለመቀጠል አንደተዘጋጃ ይናገራል። በራሱ በተሰጠውና ባገለገለበት መሥመር እንጂ ሌሎች በሠሩት ላይ ጣልቃ በመግባት ለመመካት እንደማያስብ ይገልጻል፡፡ ይህን የሚያደርጉት ሐሰተኞች አስተማሪዎች እንደሆኑም በእጅ አዙር ይናገራል። የጳውሎስ ምኞት የቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን በእምነት ጎልምሳ አድጋ ቤተ ክርስቲያን ወዳልደረሰበት ቦታ ወንጌልን ይዞ የማሰራጨቱን ሥራ እንድትረዳው ነበር። በትዕቢት ተነፍተው ስለ ራሳቸው ብቃት ከሚያስቡ፥ የጠፉትን ሰዎች በመመለስ መንፈሳዊነታቸውን ማሳየት ነበረባቸው። በዚህ ዓይነት እነርሱ «የሚመኩበት» ነገር ይኖራቸው ነበር። ሐሰተኛ መምህራን ብዙ ጊዜ ክርስቲያኖችን አባል ከሆኑበት ቤተ ክርስቲያን ለማፈናቀል ነው የሚሞክሩት። ወንጌልን ወዳልተዳረሰበት ሥፍራ ይዘው አይሄዱም። አንድ በደንብ ያደገች ቤተ ክርስቲያን የምትለይበት አንዱ ባሕሪዋ ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አዳኛቸው ለማያውቁት ሰዎች ወንጌልን ለማድረስ ባላት ሸክም ነው። 

ጥያቄ 8. በአካባቢህና በመላው ኢትዮጵያ ያልዳኑትን ሰዎች ለማምጣት የአንተ ቤተ ክርስቲያን የምታደርገውን ጥረት አብራራ። 

ከቁጥር 17-18፡- ሐዋርያው ስለራሱ አገልግሎት እንዲናገር ሁኔታው አስገደደው እንጂ በዚህ ዓይነት ንግግር ከሐሰተኛ አስተማሪዎች ጋር እንካ ስላንቲያ መለዋወጥ አልፈለገም። ይህንንም ያደረገው የቆሮንቶስን ቤተ ክርስቲያን ከሐሰተኞች እጅ ለማውጣት አስፈላጊ ስለሆነበት ብቻ ነው። ሆኖም እንዲህ እውነትን በመመርኮዝ ስለራሱ ሥራ ይናገር እንጂ መመኪያው የእርሱ ሥራ ሳይሆን የእግዚአብሔር ጸጋ እንደሆነ ይናገራል። 

ጥያቄ 9. ሀ/ ስለ ሐሰተኛ መምህራን የተሰጡትን ተጨማሪ ባሕሪያት ዘርዝረህ ጻፍ። ለ/ ቤተ ክርስቲያናችሁን ሊያፈርሱ የሚሞክሩትን ሐሰተኛ መምህራን ቤተ ክርስቲያንህ የምትዋጋቸው በእንዴት ዓይነት ሁኔታ ነው? ሐ/ መወሰድ ይገባቸዋል ብለህ የምትገምታቸው እርምጃዎች ምን ምንድናቸው? 

Leave a Reply

%d bloggers like this: