ጥያቄ 1. ቁጥር 7ን አብራራ።
ጥያቄ 2. በቁጥር 12 ላይ ጳውሎስ ራሱን ከአንዳንዶች ጋር ማወዳደር አልደፍርም ሲል ምን ማለቱ ነው? ከእነርሱ አንሳለሁ ማለቱ ነው? አብራራ።
ቁጥር 7:- “በፊታችሁ ያለውን ተመልከቱ”። በቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ሾልከው የገቡት ሐሰተኛ አስተማሪዎች ጳውሎስን ሐሰተኛ ነው በማለት ይናገሩ ነበር። ለእነርሱ መልስ ሲሰጥ «ማንም በእርግጥ የክርስቶስ ከሆነ እኔ ደግሞ በክርስቶስ እንደሆንሁ ያውቅ ነበር፤ ነገር ግን እኔን ሐሰተኛ ነው ካለ እኔ በእርግጥ በክርስቶስ ስለሆንሁ እርሱ ራሱ ሐሰተኛ መሆኑን በራሱ ፍርድ ይመሰክራል» ይላል። ይህ ለእኛም ትምሕርት ይሁነን። ሃሰተኛ አስተማሪዎች ሁልጊዜ ከእነርሱ በስተቀር መንፈሳውያን ወይም ከእነርሱ በስተቀር እውነተኛ ክርስቲያን እንደሌለ አድርገው ሌሎችን በማንገዋለል ራሳቸውን ከፍ ከፍ ያደርጋሉ፡፡
ጥያቄ 3. የዚህ ዓይነት ፀባይ ያላቸውን ክርስቲያን ነን ባዮች ታውቃለህ? ጥቀሳቸው።
ቁጥር 8፡- ሐዋርያው ቤተ ክርስቲያንን ለመገንባት ጌታ ስጦታ እንደሰጠው የመሠረታት የቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ማረጋገጫ ናት። ስለዚህ ሐዋርያው ሥልጣን ያለው መሆኑ እንደሐሰተኛ አስተማሪዎች በወሬ ብቻ አልነበረም።
ከቁጥር 9-11:- ሐዋርያው በዚህ ክፍል ለተሰነዘረበት ሐሜት መልስ ይሰጣል። ክርስቶስ የሰጠው ኃይል በሩቅ በደብዳቤ ብቻ ሳይሆን በቅርብ ፊት ለፊት ያው ነው ይላል። መሆኑንም በእርግጥ በመካከላቸው ተገኝቶ በደብዳቤ የነገራቸውን ፊት ለፊት ሊነግራቸው ዝግጁ መሆኑን ያረጋገጥላቸዋል።
ቁጥር 12፡- ራሳቸውን ከሚያመሰግኑ ጋር ራሱን ሊያወዳድር የማይደፍር መሆኑን ሲናገር በአሽሙር መናገሩ ነው። በእርግጥ ከእነርሱ ያስሁ ነኝ ማለቱ አይደለም። በዚሁ ቁጥር ላይ ዝቅ ብሉ ራሳቸውን የሚያመሰግኑት ራሳቸውን በራሳቸው በማስተያየት ብቻ ነው ይላል። ሐዋርያው ግን ጥሪውን በክርስቶስ ቃልና በአገልግሎቱ ፍሬ ነበር ይመዝን የነበረው። እንግዲህ በዚህ ቃል መሠረት በግል ቡድን ብቻ ፈጥረን በዚያው በቡድናችን እርስ በርስ እየተመሰጋገንን መኩራራት አደገኛ እንደሆነ አንዘንጋ፡፡ ከግል ቡድናችን ወጣ ብለን ጌታ በሌሎችም ዘንድ በሌሎች ውስጥ የሚሠራውን ማመዛዘን ይኖርብናል።
ጥያቄ 4. ሀ/ በዚህ ትምህርት ላይ ስለ ሐሰተኛ መምህራን የተሰጡትን ባሕርያት በዝርዝር ጻፍ። ለ/ ይህንን ዓይነት ባሕርይ የያዙ ሐሰተኛ መምህራን በቤተ ክርስቲያንህ ወይም በሌላ ቦታ ያየኸው በእንዴት ዓይነት ሁኔታ ነው?