ሰው መንፈስ፥ ነፍስና ሥጋ (አካል) እንዲኖረው ሆኖ በእግዚአብሔር የተፈጠረ ልዩ ፍጡር ነው (ዘፍጥረት 1፡27፣ 1ኛ ተሰሎንቄ 5፡23)።
1. ሥጋችን (ውጫዊው ሰው)
ሥጋችን ማለትም “የውጭው ሰው”፥ በምንኖርበት ዓለም ውስጥ አካላዊ መኖሪያችን ነው። ሥጋችን ለመብላት፥ ለመጠጣትና ለመተኛት የሚያስችሉ ውስጣዊ ፍላጎቶችን በማሟላት በዋናነት በአምስቱ የስሜት ሕዋሳት አማካኝነት ይሠራል።
-
ሥጋችን በራሱ ክፉ አይደለም፤ ከእግዚአብሔር በስጦታ የተቀበልነው መልካም ስጦታ እንጂ።
-
ይህን ሥጋችንን (ብልቶቻችንን) ለእግዚአብሔር ሕያው መሥዋዕት አድርገን እንድናቀርብ መጽሐፍ ቅዱስ ይመክረናል (ሮሜ 12፡1-2)።
-
በክርስቶስ በኩል የእግዚአብሔርን የድነት (የደኅንነት) ስጦታ ስንቀበል፥ አካላችን (ሥጋችን) የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ ይሆናል (1ኛ ቆሮንቶስ 6፡19-20፣ 3፡16)።
2. ነፍሳችን (የስብዕና ማዕከል)
ነፍሳችን ደግሞ አእምሯችን (ዕውቀታችን)፥ ፈቃዳችን እና ስሜታችን የሚገለጡበት የስብዕናችን ማዕከል ነው።
-
የራሳችንን ሥጋዊ ፍላጎቶች ወይም የመንፈስ ቅዱስን ምኞቶች ለማዳመጥ እና ለመታዘዝ ምርጫችንን የምናደርገው በነፍሳችን አማካኝነት ነው (ገላትያ 5፡16-17፣ ሮሜ 8፡9 Fly፥ ማርቆስ 14፡38)።
-
ነፍሳችን የሕይወታችን ውሳኔዎች የሚደረጉበት የፍርድ ቤት ነው።
-
ነፍሳችን የማንነታችን (የእኔነታችን) መቀመጫ ስፍራ እና የተለያዩ ባሕርያቶቻችን ምንጭም ነው።
3. መንፈሳችን (ውስጣዊው ሰው)
መንፈሳችን የውስጡ ሰውነታችን ነው። የእግዚአብሔር መንፈስ የሚናገረውም ለውስጡ ሰውነታችን ነው። እኛም ለእግዚአብሔር የምናቀርበው ትክክለኛ እና እውነተኛ አምልኮ የሚመነጨው ከዚሁ ማንነታችን ውስጥ ነው። ኢየሱስ እንዲህ አለ፦ “እግዚአብሔር መንፈስ ነው፥ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል” (ዮሐንስ 4፡24)።
ጳውሎስ በመልዕክቶቹ “የውስጥ ሰውነት” የሚለውን ሐረግ በተደጋጋሚ ተጠቅሟል (2ኛ ቆሮንቶስ 4:16፣ ኤፌሶን 3:16)። ሮሜ 7፡22-23 እንዲህ ይላል፦ “በውስጡ ሰውነቴ በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለኛልና፥ ነገር ግን በብልቶቼ ከአእምሮዬ ሕግ ጋር የሚዋጋውንና በብልቶቼ ባለ በኃጢአት ሕግ የሚማርከኝን ሌላ ሕግ አያለሁ።”
-
“ውስጣዊው ሰው” የሚለው ሐረግ መንፈሳዊውን የሰው ገጽታ የሚገልጽ ሲሆን፥ “ውጫዊው ሰው” የሚለው ደግሞ በገሃድ የሚታየውን የሰው ገጽታ ያመለክታል።
-
ዳግም ልደት ያገኘነው በመንፈሳችን ነው (ዮሐንስ 3፡3-6)።
-
ይህ “ውስጣዊው ሰው”፥ መንፈስ ቅዱስ ስለ ኃጢአት ሊወቅሰው የሚያስችለውን ሕሊና ይዟል (ዮሐንስ 16:8፣ ሐዋርያት ሥራ 24:16)።
-
መንፈሳችን መልካምንና ክፉን የመለየት ማንነት ያለው እና እግዚአብሔርን የምንመስልበት መልካችን ነው (ሮሜ 2፡14-15)።
1ኛ ቆሮንቶስ 2፡11 እንዲህ ይላል፦ “በእርሱ ውስጥ ካለው ከሰው መንፈስ በቀር ለሰው ያለውን የሚያውቅ ሰው ማን ነው? እንዲሁም ደግሞ ከእግዚአብሔር መንፈስ በቀር ለእግዚአብሔር ያለውን ማንም አያውቅም።”
