Site icon

ኢየሱስ በኢየሩሳሌም ከተለያዩ ቡድኖች ጋር ተከራከረ (ሉቃስ 20፡1-47)

ሀ. ኢየሱስ ሥልጣኑን አስመልክቶ ከካህናት ጋር ተከራከረ (ሉቃስ 20፡1-19)። ሥልጣን አስፈላጊ ነገር ነው። አንድ ሰው ወደ አንተ መጥቶ ወደ ጦር ሜዳ መሄድ እንዳለብህ ቢነግርህ፣ የመጀመሪያው ጥያቄህ ሰውዬው ማን ነው? የሚል ይሆናል። ይህን ያለህ የመንግሥት ሥልጣን የሌለው ተራ ሰው ከሆነ፣ የሚነግርህን ችላ ብለህ ልትተው ትችላለህ። ነገር ግን ሌላ ሁለተኛ ሰው መጥቶ ቢናገርህ ሰውዩው የመንግሥት ባለሥልጣን ከሆነ፣ ከመጀመሪያው ሰውዩ ያነሰ ትምህርትና የአለባበስ ሁኔታ ቢታይበትም እንኳ አዎንታዊ ምላሽ ለመስጠት ትገደዳለህ። ለዚህ ሰውዬ ከመጀመሪያው የተለየ ምላሽ እንድትሰጥ ያደረገህ ወደ ቤትህ የመጣው ሰውዬ በራሱ ሥልጣን አይደለም። የመንግሥት ሥልጣን ሁሉ ከእርሱ ኋላ እንዳለ በመገንዘብህ እንጂ። ለዚህ ነበር የአይሁድ የሃይማኖት መሪዎች የኢየሱስን የሥልጣን ምንጭ ለማወቅ የፈለጉት። ኢየሱስ ተራ ሰው ነው ወይስ የእግዚአብሔር እንደራሴ? ኢየሱስ ቀደም ብሎ ይህንኑ እውነት የነገራቸው ሲሆን በሠራቸው ተአምራት ጭምር ሥልጣኑ ከእግዚአብሔር እንደሚመነጭ ገልጾላቸው ነበር፡፡ ነገር ግን የሚያዩትንና የሚሰሙትን ለማመን ስላልፈለጉ፣ ኢየሱስ ከእነርሱ ጋር እንደገና መከራከሩ አስፈላጊ መስሎ አልታየውም። በዚህ ፈንታ ኢየሱስ አይሁዶቹ የእግዚአብሔር ሥልጣን በየትኛውም መልክ ቢመጣ ለመቀበል ባለመፈለጋቸው በመጥምቁ ዮሐንስ አማካይነት የሠራውን የእግዚአብሔርን እጅ ለማመን አለመፍቀዳቸውን በመግለጽ፣ የራሳቸውን ጥያቄ ተጠቅሞ ሞገታቸው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ኢየሱስ ብቸኛ የደኅንነት መንገድ ነው የሚለው እሳብህቶ ሥልጣን ከየት እንደመነጨ ብትጠየቅ፣ ምላሽህ ምን ይሆናል?

ኢየሱስ ምሳሌ በመጠቀም ሊሆን ስላለው ነገር ለካህናቱ ብርቱ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷቸዋል። እንደ የወይን አትክልተኞች ሁሉ፣ እነርሱም ለእግዚአብሔር ሕዝብ ኃላፊነት ተሰጥቷቸው ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔርን ለመስማትና መልእክተኞቹን (መጥምቁ ዮሐንስንና ኢየሱስን)፥ ለመቀበል ባለመፈለጋቸው፣ የእግዚአብሔርን አገልጋይ ብቻ ሳይሆን፥ የእግዚአብሔርንም ልጅ አንቀበልም አሉ። ከዚህም የተነሣ እግዚአብሔር በቅርብ ጊዜ በእነርሱ ላይ በመፍረድ ወይኑን ለሌሎች ሠራተኞች ይሰጣል። ሌሎች፥ የተባሉት በኋላ መንፈሳዊ አመራሩን የተቀበሉት ሐዋርያት ሳይሆኑ አይቀሩም። ክፍሉ የሚያመለክተው ግን የእግዚአብሔር የወይን በረከት ወደ አሕዛብ እንደሚዞር ሳይሆን አይቀርም። አይሁዶች ሁሉ ይህ በእነርሱ ላይ የተሰነዘረ ጠንካራ ማስጠንቀቂያ መሆኑን ስለተገነዘቡ፣ እንዲህ ያለውንስ አያምጣው» ሲሉ ተቃወሙ። ኢየሱስ ብሉይ ኪዳን እንኳ አይሁዶች እንዴት የእግዚአብሔርን ድንጋይ ለመቀበል እምቢ እንደሚሉና፥ እግዚአብሔር ግን እነርሱ ያልተቀበሉትን ድንጋይ የማዕዘን ራስ እንደሚያደርገው የተናገረ መሆኑን ገለጸላቸው። የዚያ ድንጋይ ተምሳሌት የሆነው ኢየሱስ፥ ለእግዚአብሔር ሕዝብ አዲስ ሕንጻ አካል ይሆናል።

የውይይት ጥያቄ- እግዚአብሔር ሕዝቡ ንስሐ እንዲገባ ለዘላለም አይጠብቅም። አንዳንድ ጊዜ የበለጠ ትሑትና ተገዥ ለሆነው ሌላ ሰው ወይም ቤተ እምነት በረከቱን አሳልፎ እስከሚሰጥ ድረስ ታላቅ ፍርዱን ያመጣል። ይህ ምሳሌ ለእኛ በግልና በቤተ ክርስቲያን ደረጃ ማስጠንቀቂያ የሚሰጠን እንዴት ነው?

ለ. ስለ ቀረጥ መክፈል ከፖለቲካ መሪዎች ጋር የተካሄደ ክርክር (ሉቃስ 20፡20-26)። አይሁዶች በሁለተኛ ደረጃ ኢየሱስን ችግር ውስጥ ለመክተት የሞከሩት፥ ከሮም ባለሥልጣናት የሚጋጭበትን ሁኔታ በማመቻቸት ነበር። ኢየሱስ ቀረጥ አልከፍልም ቢል፣ በመንግሥት ላይ ዐመፅ ቀስቅሷል ተብሎ ይታሰር ነበር። ኢየሱስ ግን ሰዎች ታማኝነታቸውን ሊገልጹ የሚችሉባቸው ሁለት መንግሥታት እንዳሉ ገልጾአል። አንዱ ሮም የምትገዛበት ዐይነት ምድራዊ መንግሥት ነበር። እንዲሁም ደግሞ ሌላው ሰማያዊ የእግዚአብሔር መንግሥት ነበር። ሁለቱንም ማክበርና መታዘዝ ያስፈልጋል። የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይ ታዛዥ እንጂ ዐማጺ አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር ሕዝብ ከምድራዊ መንግሥት ትእዛዝ ይልቅ የሰማያዊውን መንግሥት ትእዛዝ የሚያስበልጡት፣ ከሰማያዊ መንግሥት ሥር ያለው ምድራዊ መንግሥት የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በሚጥስበት ጊዜ ብቻ ነው።

ሐ. ከሰዱቃውያን ጋር ስለ ጋብቻና ስለ ሙታን ትንሣኤ የተደረገ ክርክር (ሉቃስ 20፡27-40)። ኢየሱስን ለማጥመድ የተደረገው የመጨረሻው ጥረት ሥነ መለኮታዊ ክርክርን በመክፈት ነበር። ሥነ መለኮት እግዚአብሔር ስለ አንድ ርእሰ ጉዳይ የሚያስተምረውን እውነት ለመረዳት የሚደረግ ጥረት በመሆኑ ጠቃሚ ነው። ብዙውን ጊዜ ግን ነገረ መለኮት ትርጉም ወደማይሰጡ አለመስማማቶች ይመራል። ይህም ጊዜ ከማባከኑ በተጨማሪ፣ ሰዎች እርስ በርሳቸው ተጣልተው ኅብረት እንዲያቋርጡ በማድረግ ለኃጢአት ይዳርጋቸዋል። በዐበይት ቤተ እምነቶች ውስጥ የተፈጸሙት አብዛኞቹ መከፋፈሎች በእግዚአብሔር ዐይን ፊት ክርስቲያኖችን ሊያጣሉ በማይገቡ ነገረ መለኮታዊ ጉዳዮች ላይ ካለመስማማት የመነጩ ናቸው፡፡ ለእውነት መፋለም ያለብን የእግዚአብሔርን ቃል በግልጽ የሚያፋልስ ነገር ከተገኘ ብቻ ሊሆን ይገባል። ኢየሱስ ስለ ጋብቻ ሥርዓት በቀረበው ሙግት ውስጥ ለመሳተፍ ባለመፈለጉ፣ የሰዱቃውያን ዋንኛ ችግርና ውዥንብር ወደሆነው ጉዳይ አመራ። እነዚህ ሰዎች የመጽሐፍ ቅዱስ ዋነኛ አስተምህሮ የሆነውን የሙታን ትንሣኤ አይቀበሉም ነበር።

መ. ኢየሱስ ስለ ዳዊት ልጅ የሃይማኖት መሪዎችን ጠየቃቸው (ሉቃስ 20፡41-47)። አይሁዶች መሢሑን ታላቅ ሰብአዊ መሪ ብቻ አድርገው ያስቡ ነበር። ስለሆነም ኢየሱስ ዳዊት መሢሑን ጌታዬ ብሎ እንደጠራው በመጥቀስ፣ አምላክነቱን ገለጻላቸው ይህም የዳዊት ልጅ ከዳዊት የዘር ሐረግ የመጣ ሰው ከመሆኑም በላይ፥ የዳዊት አምላክ መሆኑን ያሳያል፡፡ እነዚህን ሁለቱንም መስፈርቶች የሚያሟላው ኢየሱስ ብቻ ነው። ኢየሱስ በዚህ አኳኋን በሰጠው ማብራሪያ፥ መልስና ትምህርት የተለያዩ የሃይማኖት መሪዎች እርሱን ለማጥመድ ያደርጉትን ጥረት ሁሉ ውድቅ አደረገ። ከሁሉም በላይ ያስቆጣው እርሱን ለማጥመድ መሞከራቸው ሳይሆን፣ በቀላሉ ሰዎችን የሚጎዳው የግብዝነት ሃይማኖታቸው ነበር። ስለሆነም ሕዝቡ እነዚህን የሃይማኖት መሪዎች በእግዚአብሔር ፊት እንዴት መመላለስ እንዳለባቸው የሚያሳዩ እንደ መልካም ምሳሌዎች አድርገው እንዳይመለከቱዋቸው አስጠነቀቃቸው። እነዚህ ሰዎች ሃይማኖታዊ መሪዎቻቸው ቢሆኑም እንኳ፥ እግዚአብሔርን የሚያስከብር ሕይወት አልነበራቸውም። መሪዎቹ ከሕዝቡ እየተደበቁ እንደ መበለቶች ያሉትን ሴቶች በመበዝበዝ የራሳቸውን ብልጽግና ያሳድዱ ነበር። ለእነዚህ ሰዎች ሃይማኖት በምኩራብ ውስጥ ወይም ሰዎች በሚያዩአቸው ስፍራ የሚያከናውኑት ተግባር ነበር። ሃይማኖት መሪዎቹ በሌላ ጊዜ የሚኖሩትን ሕይወታቸውን አልለወጠውም።

የውይይት ጥያቄ:- እኛም ግብዝ በመሆን እንዴት የፈሪሳውያንን አመለካከት ልንጋራ እንደምንችል የተለያዩ መንገዶችን በመጥቀስ አብራራ።

ነገሮችን ‹ሃይማኖታዊ› እና ‹ተራ› ብሎ መነጣጠሉ ቀላል ነው። በቤተ ክርስቲያን አምልኮ ወይም በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ላይ በምንሆንበት ጊዜ፥ ሃይማኖታዊ ተግባርን እያደረግን ነው ብለን እናስባለን። አንዳንድ ጊዜ እነዚህን ነገሮች ከልባችን በማንፈጽምበት ጊዜ እንኳ ሰዎች መንፈሳውያን እንደሆንንና ከልባችን እንዳደረግነው ያስባሉ። እርግጥ ነው ሁልጊዜ እግዚአብሔርን ለማምለክ የሚሻ እውነተኛ ፍላጎት ሊኖረን ይችል ይሆናል። ያም ሆኖ ከዚያ በኋላ በትምህርት ቤት፣ በሥራ ቦታ ወይም በቤታችን የምናከናውነው ተግባር እግዚአብሔርን የሚያሳስበው አይመስለንም። እንዲህ ስናደርግ በዚህም በአምልኮና እግዚአብሔር በሚያየው ሕይወት መካከል ክፍተት እንፈጥራለን። እውነተኛው አምልኮ ለድሆች ማሰብ እንደሆነ ከያዕቆብ መልእክት እንረዳለን (ያዕ. 1፡26-27)። ዝማሬያችንና አምልኳችን ብቻ ሳይሆን፣ እያንዳንዱን የሕይወት እርምጃችን እግዚአብሔርን በሚያከብር መንገድ ልንኖር ይገባናል። ስለዚህ በሥራ ቦታችሁ፣ በትምህርት ቤታችሁ ወይም በመኖሪያ ቤታችሁ እግዚአብሔርን ለማክበር ምን እያደረጋችሁ ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version